Saturday, 06 July 2013 10:32

“አዲስ ጉዳይ” መጽሔት የዓለም አቀፍ ጋዜጠኞች ማዕከል ሽልማት አሸናፊ ሆነ

Written by 
Rate this item
(6 votes)

“አዲስ ጉዳይ” መጽሔት በታፈኑ ዕውነቶች አምድ ላይ ለንባብ ባበቃው “ቀናት የሚታደጓቸው እድሜ ልኮች” የሚል ተንታኝ ሃተታ (ፊቸር ስቶሪ) የዓለም አቀፉን የጋዜጠኞች ማዕከል (ICFJ) የሁለተኛ ደረጃ ቀዳሚ ሽልማት አሸነፈ፡፡ ማዕከሉ ከአፍሪካ የጤና ጋዜጠኞች ማህበር እና ከአረብ ሚዲያ ፎረም ጋር በመተባበር ባዘጋጀው በክትባት ጉዳይ ላይ የሚያተኩር የዘገባ ውድድር ላይ 200 የእስያ፣ የአፍሪካና ስድስት የባህረሰላጤው አገራት ሚዲያዎች እንደተሳተፉ ታውቋል፡፡
መጽሔቱ በኢትዮጵያ የክትባት ተደራሽነት አናሳ መሆኑን አስመልክቶ የሰራው ተንታኝ ሃተታ፤ ከመላው አፍሪካ፣ ከእስያና ከባህረሰላጤው ሀገራት ሚዲያዎች ጋር ተወዳድሮ ነው ያሸነፈው፡፡
ከ14 ሀገራት በተውጣጡ በሙያው አንቱ በተባሉ ጋዜጠኞች በተዋቀረው ኮሚቴ በተሰጠው ዳኝነት ከ200 ዘገባዎች ውስጥ የአዲስ ጉዳይ “ቀናት የሚታደጓቸው እድሜ ልኮች” ከሁለተኛ ደረጃ ተሸላሚዎች የአንደኝነት ደረጃን ለማግኘት ችሏል፡፡
“ኢትዮጵያን ወክለን መወዳደራችንና ማሸነፋችን ዝግጅት ክፍሉን በጣም አስደስቶታል፡፡ በተለይም በአሁኑ ወቅት አዲስ ጉዳይን በአዲስ መልክ ለአንባቢያን ለማቅረብና በይዘቱ ላይ መጠነኛ ማሻሻያ አድርገን በባለሙያዎች የሚሰራ መጽሔት ለማድረግ ከልዩ ልዩ ዘርፎች ባለሙያዎችን እና አማካሪዎችን ቀጥረን እየተንቀሳቀስን ባለንበት ወቅት ይህ ውጤት መገኘቱ ሞራላችንን ገንብቶታል፡፡ ለበለጠ ስራም አነሳስቶናል” ብሏል የመጽሔቱ ዋና አዘጋጅ አቶ ዮሐንስ ካሳሁን፡፡
የውድድሩ ዋና አላማ በክትባት ማጣት ሳቢያ በየዓመቱ ህይወታቸውን የሚያጡ ህጻናትን ቁጥር ለመቀነስና ለከፍተኛ የአካል ጉዳት የሚዳረጉ ዜጐችን ጤና መታገድ የሚያስችል እውቀት መፍጠር ሲሆን የመጽሔቱ ዘገባ ኢትዮጵያ ያለችበትን ወቅታዊ ሁኔታ በማሳየት ህብረተሰቡ ግንዛቤ እንዲኖረውና መንግስትም ክፍተቶቹን እንዲደፍን መረጃ የሚያስጨብጥ ነው ተብሏል፡፡
ቢሮውን ዋሽንግተን ዲሲ ያደረገው የአለምአቀፉ ጋዜጠኞች ማህበር ፕሬዚዳንት ጆይስ ባርናታን አሸናፊዎቹ ይፋ በተደረጉበት ስነስርዓት ላይ እንደተናገሩት፤ “አሸናፊዎች ያቀረቧቸው ስራዎች እንደ ፖሊዮ ያሉ ከፍተኛ ጉዳት አድራሽ የሆኑ ነገር ግን በቀላሉ መከላከል የሚቻሉ በሽታዎችን መቋቋምና ማሸነፍ የሚቻልባቸውን መንገዶች ያመላከቱ ትምህርት ሰጪ ዘገባዎች ናቸው፡፡ ለህዝባቸው እና ለጤና ባለሙያዎቻቸው እንቅፋትን አስወግደው ስኬትን የሚያገኙባቸውን መንገዶችም የጠቆሙ ናቸው” ብለዋል፡፡
በውድድሩ አንደኛ የወጡት የናይጀሪያ “ቲቪሲ ኒውስ” ቴሌቪዥን ጣቢያ፣ የፓኪስታኑ “ኒውስ ዋን” ቴሌቪዥን ጣቢያ፣ የኮትዲቩዋሩ “አቬኑ 225 ኒውስ ሳይት” ድረገጽ እና የተባበሩት አረብ ኢምሬቶች “ፊላንትሮፒ ኤጅ ማጋዚን” ሲሆኑ ጽሑፎቹ አንደኛ የወጡት ሚዲያዎቻቸው ሰፊ ተደራሽነት ያላቸው የቴሌቪዥን ኔትወርኮች በመሆናቸውና በኢንተርኔት ቴክኖሎጂ በታገዘ ስርጭታቸው አህጉራዊ ሽፋን በመፍጠራቸው መሆኑን የውድድሩ አዘጋጆቹ ተናግረዋል፡፡ ዋና አዘጋጁ አቶ ዮሐንስ እንዳለው፤ አዲስ ጉዳይ መጽሔት ከነዚህ ታዋቂ አህጉራዊ ሚዲያዎች ጋር ተወዳድሮ በ2ተኛ ደረጃ ተሸላሚነት ከተመረጡት የዩጋንዳው “ኤንቲቪ”፣ የፓኪስታኑ “ሳውዝ ኤሺያን ሜጋዚን”፣ እና የሳውዲአረቢያው “ሳውዲ ኒውስፔፐር ቱዴይ” ጋር የላቀ ውጤት በማስመዝገብ አንደኛ ደረጃ አግኝቷል፡፡ ይህ ውጤትም ኢትዮጵያውያን ሚዲያዎች በቴክኖሎጂ ቢታገዙና መልቲሚዲያ ቢሆኑ አህጉራዊ ተደራሽነትና ከየትኛውም አገር ጋር የሚፎካከር ሥራ መሥራት እንደሚችሉ ያመላከተ ነው፡፡

Read 16292 times