Print this page
Saturday, 29 June 2013 11:15

ደደቢት የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ‹መለስ ዋንጫ›ን ተቀዳጀ

Written by 
Rate this item
(3 votes)

የደደቢት የእግር ኳስ ክለብ የ2005 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ‹መለስ ዋንጫ› አሸናፊ መሆኑን አረጋገጠ፡፡ የውድድር ዘመኑ ሊጠናቀቅ የሁለት ሳምንት ጨዋታ እየቀረው ደደቢት ሻምፒዮን መሆኑን ያረጋገጠው ባደረጋቸው 24 ጨዋታዎች 17 አሸንፎ፤ በአራቱ አቻ ተለያይቶ እና በ3 ተሸንፎ 55 ነጥብ እና 35 የግብ ክፍያ በማስመዝገብ ነው፡፡ ደደቢት በአንድ ጨዋታ በአማካይ የሚያገባው 2.39 ጎሎች ሲሆን ይህም በሜዳው 2.91 ጎሎች ከሜዳው ውጭ ደግሞ በ1.92 ጎሎች የሚመነዘር ነው፡፡ ባደረጋቸው 24 ጨዋታዎች በተጋጣሚዎቹ ላይ 59 ጎሎች አስቆጥሮ 24 ጎሎችን ያስተናገደው ክለቡ ጎል ማግባት ያቃተው በ1 ጨዋታ ብቻ ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮንነቱም በ2014 በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የሚሳተፍ ይሆናል፡፡

የደደቢት እግር ኳስ ክለብ መሥራችና ፕሬዚዳንት ኮሎኔል አወል አብዱራሂም ለስፖርት አድማስ እንደገለፁት ክለቡ የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን የሆነው ዕቅዱና አላማውን መሠረት አድርጐ በመንቀሳቀሱ ነው ብለው፤ በተገኘው ውጤት የትኩረት አቅጣጫው ለአገሪቱ እግር ኳስ ሙሉ አስተዋጽኦ ማበርከት መሆኑን አስመስክሮበታል ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ክለቡ በ2002 ዓ.ም ፕሪምየር ሊጉን ለመጀመሪያ ጊዜ ሲቀላቀል ለብሔራዊ ቡድን አንድ ተጨዋች ብቻ ማስመረጡን ያስታወሱት ፕሬዝዳንቱ፤ ከአራት የውድድር ዘመን በኋላ ግን በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በተሳተፈው ብሔራዊ ቡድን 8 ቋሚ ተሰላፊዎችን ከማስመረጡ በላይ ከአፍሪካ ዋንጫውም በኋላ ከክለቡ 11 ተጨዋቾች ተመልምለው 9ቱ በቋሚነት ተሰላፊነት ማስመረጥ መቻሉ ዓለማውን ያንፀባረቀ ነው ሲሉ አስረድተዋል፡፡

ደደቢት ፕሪሚዬር ሊግን መሳተፍ በጀመረ በ4ኛ የውድድር ዘመኑ ላይ የመጀመሪያውን የሻምፒዮንነት ክብር መጐናፀፉ በክለቡ ታሪክ አበይት ምዕራፍ የሚከፍት ነው ያሉት የክለቡ ፕሬዝዳንት ኮሎኔል አብዱራሂም፤ዘንድሮ ውድድሩ ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ መታሰቢያነት ተዘጋጅቶ ደደቢት ዋንጫውን መውሰዱ ልዩ ታሪክ እና ትርጉም ሰጥቶታል ብለዋል፡፡ ለዚህ ውጤት መገኘት ከክለቡ ባለድርሻ አካላት ባሻገር ለኢትዮጵያ እግር ኳስ እድገት ሞተር ሆነው ወሳኝ ሚና በመጫወት፤ የክለቡን ሞራል በመገንባትና የሚሰራን በማነሳሳት መመስገን ያለባቸው እግር ኳስ አፍቃሪያን ናቸው፤ በማለትም ኮሎኔል አወል ለስፖርት ቤተሰቡ ያላቸውን አድናቆት ገልፀዋል፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማኅበር ለደደቢት የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮናነት የእንኳን ደስ ያላችሁ መልዕክት ወዲያውኑ በማድረስ የፈፀመው ተግባር በጣም እንደማረካቸው የሚናገሩት ኮሎኔል አብዱራሂም ከከፍተኛ ፉክክር በኋላ ለአሸናፊው ወገን አድናቆት መስጠት በአርአያነት ሊታይ የሚገባው ነው፤ ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ከአመት ወደ አመት የፉክክር ደረጃው እያደገ መጥቷል የሚሉት ኮሎኔል አወል አብዱራሂም፤ ክለቦች ለመሸናነፍ በጥሩ ፉክክር መወዳደራቸው፣ በደረጃ ሰንጠረዥ ላይ ተቀራራቢ ነጥቦች መስተዋላቸው እንደሚበረታታ አስገንዝበው በየመካከሉ ኢንተርናሽናል ውድድሮች በዝተው በውድድር ፕሮግራሞች ላይ በሚፈጠሩ መዛባቶች ከሚያመጡት የመቀዛቀዝ ችግር በስተቀር ጠንካራና ፈታኝ የውድድር ዘመን አሳልፈናል ብለዋል፡፡ ከ4 የውድድር ዘመን በፊት ደደቢት ፕሪሚዬር ሊጉን ለመጀመርያ ጊዜ ሲቀላቀል ባልተጠበቀ ሁኔታ ከባድ ፉክክር በማሳየት የፕሪሚዬር ሊጉን የመጀመርያ ዙር በመሪነት ቢያጠናቅቅም የውድድር ዘመኑን በ2ኛ ደረጃ ነበር የጨረሰው፡፡ በዚሁ የውድድር ዘመን ግን ክለቡ በኢትዮጵያ የክለቦች ውድድር ከፍተኛ ደረጃ ባለው የጥሎ ማለፍ ውድድር ሻምፒዮን ለመሆን በቅቷል፡፡ ካች አምና በኮንፌደሬሽን ካፕ እየተወዳደረ በመጀመርያ ዙር ማጣርያ ከውድድር የተሰናበተው ክለቡ በፕሪሚዬር ሊጉ ደግሞ ከቡና እና ጊዮርጊስ በመቀጠል በሶስተኛ ደረጃ አጠናቅቋል፡፡ አምና በፕሪሚዬር ሊጉ ለ3ኛ ጊዜ ተሳትፎ በሁለተኛ ደረጃ ያጠናቀቀው ደደቢት በአፍሪካ ክለቦች ኮንፌደሬሽን ካፕ የመሳተፍ እድል አግኝቶ እስከ ሁለተኛ ዙር የመልስ ጨዋታ በመጓዝ ተስፋ ሰጭ ውጤት አሳይቷል፡፡

Read 4790 times
Administrator

Latest from Administrator