Saturday, 29 June 2013 10:56

ካናዬ ዌስት ካስቲቭ ጆብስን እተካለሁ አለ የህፃን ልጃቸው ፎቶ 10ሚ.ዶላር ያወጣል ተባለ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

ከሁለት ሳምንት በፊት 36ኛ ዓመት ልደቱን ያከበረው እና “ጄይዙስ” የተባለ አዲስ አልበሙን ከሰሞኑ ለገበያ ያቀረበው ካናዬ ዌስት፤ የዘመኑ ስቲቭ ጆብስ እኔ ነኝ ሲል ተናገረ፡፡ በሌላ በኩል ካናዬ ዌስት እና ፍቅረኛው ኪም ካርዴሽያን ከሳምንት በፊት የመጀመርያ ሴት ልጃቸውን የወለዱ ሲሆን ኖርዝ ኖሪ ዌስት የሚል ስምም አውጥተውላታል፡፡ ሁለቱ ዝነኞች ለሴት ልጃቸው ያወጡት ስም ለብራንድ አይመችም ተብሎ ቢተችም ከተወለደች ወር ያልሞላትን ህፃን የመጀመርያ ፎቶ ለማግኘት የመገናኛ ብዙሃን እሽቅድድም ላይ እንደሆኑ የጠቀሱት ዘገባዎች፤ የህፃኗ ፎቶ እስከ 10 ሚሊዮን ዶላር ሊያወጣ እንደሚችል ተገምቷል፡፡ ሰሞኑን ሁለት ሚዲያዎች የኖርዝ ኖሪ ዌስት የመጀመርያ ፎቶን አግኝተናል በማለት ህትመታቸውን ቢያሰራጩም ፎቶው ሃሰተኛ እንደሆነ መታወቁን ቲኤምዜድ ዘግቧል፡፡

“ፒፕል ማጋዚን” የብራድ ፒት እና አንጀሊና ጆሊ ሁለት መንታ ልጆችን የመጀመርያ ፎቶ በ14 ሚሊዮን ዶላር ገዝቶ ማተሙን ያስታወሰው ዘገባው፤ ቤተሰቡ ይህን ገንዘብ ለበጎ አድራጎት እንደለገሱ እና ካናዬ እና ፍቅረኛውም ተመሳሳይ ነገር እንደሚፈጽሙ ይገመታል ብሏል፡፡ የመጀመርያ ሴት ልጁን ባገኘ በማግስቱ “ቀጣዩ ስቲቭ ጆብስ እኔ ነኝ” ሲል የተናገረው ካናዬ ዌስት፤ “በኢንተርኔት፤ በሙዚቃ፤ በፋሽንና በባህል የምፈጥረው ተፅእኖ እንደ ስቲቭ ጆብስ አብዮተኛ ያደርገኛል” ብሏል፡፡

በራፐርነቱ የሚታወቀው ካናዬ ዌስት፤ 100 ሚሊዮን ዶላር ሃብት ሲኖረው፤ በቴሌቭዥን ሪያሊቲ ሾው እና በፋሽን ኢንዱስትሪው አውራነቷን ያስመሰከረችው ፍቅረኛው ኪም ካርዴሽያን 40 ሚሊዮን ዶላር ሃብት አስመዝግባለች፡፡ ካናዬ ዌስት ከ7ኛ አልበሙ “ጄይዙስ” በፊት አስቀድሞ ባሳተማቸው ስድስት አልበሞች በመላው ዓለም 15 ሚሊዮን ቅጂዎች የተሸጡለት ሲሆን 14 የግራሚ ሽልማቶችን ጨምሮ ከ47 በላይ የተለያዩ ሽልማቶች በማግኘት ከፍተኛውን ስኬት የተቀዳጀ ራፐር ነው፡፡

Read 2727 times