Wednesday, 12 June 2013 14:51

ቅዱስ ጊዮርጊስ ፈርቀዳጅ እና አስደናቂ ስኬት አስመዝግቧል

Written by 
Rate this item
(2 votes)

የኢትዮጵያው ክለብ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከአፍሪካ ስምንት ምርጥ ክለቦች ተርታ የገባበት ብቃት አስደነቀ። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ሰሞኑን ለዝግጅት ክፍላችን ባደረሰው መልእክት የቅዱስ ጊዮርጊስ እግር ኳስ ክለብ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ ወደ ኮንፌደሬሽን ካፕ የምድብ ማጣሪያ ያለፈ የመጀመርያ ክለብ በመሆኑ ለሀገራችን እግር ኳስ እድገት ተምሳሌት መሆኑን አረጋግጧል በማለት ብሏል፡፡ ዘንድሮ በአፍሪካ ሁለት የክለብ ውድደሮች ሻምፒዮንስ ሊግ እና ኮንፌዴሬሽን ካፕ አስደናቂ ተሳትፎ ያደረገው ክለቡ ስምንት ጨዋታዎች አድርጎ አራቱን ሲያሸንፍ በ3 አቻ ተለያይቶ እና 1 ጨዋታ ብቻ የተሸነፈ ሲሆን 17 ግብ ተጋጣሚዎቹ ላይ ሲያስቆጠር፤ሰባት ጎሎች ደግሞ ተቆጥረውበታል፡፡ የውድድር ዘመኑን በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ በመሳተፍ የጀመረው ቅዱስ ጊዮርጊስ በውድድሩ ቅድመ ማጣርያ የተገናኘው ከዛንዚባሪ ጃምሁሪ ጋር የነበረ ሲሆን በሜዳው 3ለ0 ከዚያም ከሜዳው ውጭ 5ለ0 በማሸነፍ ብድምር ውጤት 8ለ0 አሸንፎ ወደ የመጀመርያው ዙር ማጣርያ ገብቷል፡፡ በሻምፒዮንስ ሊጉ የመጀመርያ ዙር ያገኘው ክለብ የማሊው ዲጆሊባ ነበር፡፡

በሜዳው 2ለ0 አሸንፎ ከሜዳው ውጭ አንድ እኩል አቻ በመለያየት በድምር ውጤት ዲጆሊባን 3ለ1 በመርታት ወደ ሁለተኛው ዙር ገብቷል፡፡ በሁለተኛው ዙር ደግሞ ከግብፁ ክለብ ዛማሌክ ጋር የመጀመርያ ጨዋታውን ከሜዳው ውጭ 1ለ1 አቻ ቢለያይም በሜዳው 2ለ2 አቻ በመለያየቱ በድምር ውጤት 3ለ3 ቢሆንም የግብፁ ክለብ ዛማሌክ ከሜዳው ውጭ ባገባቸው ጎሎች በልጦት ወደ ሻምፒዮንስ ሊጉ የምድብ ድልድል የሚገባበት እድል አምልጦት ነበር። ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሻምፒዮንስ ሊጉ ከተሰናበተ በኋላ በኮንፌዴሬሽን ካፕ ጥሎ ማለፍ የሚሳተፍበትን እድል አግኝቶ ከሌላው የግብፅ ክለብ ኤን.ፒ.ፒ.አይ ጋር ተገናኘ።

በሜዳው ኢኤንፒፒአይን 2ለ0 በማሸነፍ ለመልስ ጨዋታ ወደ ካይሮ በመጓዝ 3ለ1 ከተረታ በኋላ የደርሶ መልስ ውጤቱ 3ለ3 ቢሆንም ከሜዳው ውጭ ባስቆጠረ በሚለው ደንብ በኢትዮጵያ ክለቦች ታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ወደ ኮንፌደሬሽን ካፕ የምድብ ድልድል በመግባት ታሪክ ሰርቷል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ በአፍሪካ ኮንፌዴሬሽን ካፕ ኢትዮጵያን ወክሎ ለመጀመሪያ ጊዜ በመሳተፍ ፈርቀዳጅ የነበረ ክለብ ነው፡፡ የመድን እግር ኳስ ክለብ በኮንፌደሬሽን ካፕ ከኢትዮጵያ ክለቦች አምስት ጨዋታዎችን በማሸነፍ ግማሽ ፍፃሜ መድረስ የቻለበትን ክብረወሰን ዘንድሮ የተጋራው ቅዱስ ጊዮርጊስ ለምድብ ድልድል የደረሰ የመጀመርያው ኢትዮጵያዊ ክለብ በመሆን በፈርቀዳጅነት ቀጥሏል፡፡ የ2013 ኮንፌደሬሽን ካፕ በምድብ ጨዋታዎች ከ6 ሳምንት በኋላ ሲጀምር በምድብ 1 ከአንድ የሰሜን አፍሪካ እና ከሁለት የምዕራብ አፍሪካ ክለቦች ጋር የተገናኘው ቅዱስ ጊዮርጊስ ለዋንጫ ጨዋታ ሊደርስ እንደሚችል ግምት ወስዷል፡፡ በኮንፌደሬሽን ካፑ የምድብ ድልድል በምድብ 1 የኢትዮጵያው ቅዱስ ጊዮርጊስ፤ የማሊው ስታድ ደማሌይን፤ የናይጄርያው ኢኑጉ ሬንጀርስ እና የቱኒዚያ ኤትዋል ደሳህል ሲገኙ፤ በምድብ 2 የዲ ሪ ኮንጎው ቲፒ ማዜምቤ፤ የቱኒዚያው ሲኤ ቤዛርቲን፤ የአልጄርያው ኢኤስ ሴቲፍ እና የሞሮኮው ኢፍሲ ራባት ተደልድለዋል፡፡ በምድብ ድልድሉ በመግባት ለዋንጫው ጨዋታ መድረስ እና በየምድቡ በሚገኝ የደረጃ ውጤት መሰረት ለእግር ኳስ ክለቦቹ ብቻ ሳይሆን ለወከሉት አገር የእግር ኳስ ኮንፌዴሬሽንም የገንዘብ ሽልማት ይከፋፈላል፡፡

ከሁለቱ ምድቦች መሪ ሆነው የሚጨርሱት ለኮንፈደሬሽን ካፑ ዋንጫ ሲጫወቱ አሸናፊው ክለብ 625ሺ ዶላር ሲያገኝ የወከለው ፌደሬሽን 35ሺ ዶላር እንዲሁም 2ኛ ደረጃ ያገኘው ክለብ 432ሺ ዶላር ሲታሰብለት የወከለው ፈደሬሽን ደግሞ 30ሺ ዶላር ይሰጠዋል፡፡ በኮንፌደሬሽ ካፑ የምድብ ድልድል በየምድባቸው 2ኛ ደረጃ የሚያገኙት 239ሺ ዶላር ለወከሉት ፌዴሬሽን 25ሺ ዶላር፤3ኛ ደረጃ የሚያገኙት 239ሺ ዶላር ለወከሉት ፌዴሬሽን 20ሺ ዶላር እንዲሁም 4ኛ ደረጃ የሚያገኙት 150ሺ ዶላር ለወከሉት ፌዴሬሽን 15ሺ ዶላር እንደሚበረከትም ታውቋል፡፡

Read 3329 times