Print this page
Wednesday, 12 June 2013 14:06

ዊል ስሚዝ በ“አፍተር አርዝ” አልተሳካለትም

Written by 
Rate this item
(0 votes)

ባለፈው ሳምንት በዓለም ዙርያ በ60 አገራት መታየት የጀመረው የዊል ስሚዝ ፊልም‹አፍተር አርዝ› ገበያው እንዳልተሳካለት ተገለፀ፡፡ የፊልሙን አከፋፋይ ሶኒ ኩባንያ ለተፈጠረው የገበያ መዳከም ከዊል ስሚዝ ብቃት ይልቅ ዘንድሮ እየወጡ ያሉ ፊልሞች በገበያው የሚያሳዩት ከፍተኛ ፉክክር እንደሆነ ገልጿል፡፡‹ አፍተር አርዝ› በመጀመርያ ሳምንቱ ያስገባው 34.6 ሚሊዮን ዶላር በዊል ስሚዝ የሚሰሩ ፊልሞች አማካይ የመጀመርያ ሳምንት ገቢ በእጥፍ ያነሰ ነው፡፡ አምና ለእይታ የበቃው ‹ሜን ኢን ብላክ 3› እንዲሁም በ2008 እኤአ የታየው ‹ሃንኮክ› በመጀመርያ ሳምንታቸው 54.6 ሚሊዮን ዶላር እና 62.6 ሚሊዮን ዶላር እንደቅደምተከተላቸው አስገብተው ነበር፡፡

ከአዲሱ ፊልሙ የገበያ መቀዛቀዝ በኋላ ዊል ስሚዝ ለዲጂታል ስፓይ በሰጠው አስተያየት የደለበ ገቢ በሚያስገኙ ፊልሞች የመስራት ፍላጎት እንደሌለው ተናግሯል፡፡ ከዚሁ የዊል ስሚዝ አስተያየት በኋላ በከፍተኛ በጀት በመሰራት ጠቀም ያለ ገቢ የሚኖራቸው አይሮቦት 2፤ ሃንኮክ 2 እና ባድቦይስ 3 የተባሉት የቀድሞ ፊልሞቹ መሰራት አጠያያቂ ሆኗል፡፡ በ130 ሚሊዮን ዶላር በጀት የተሰራውን ‹ አፍተር አርዝ› የ44 ዓመቱ ዊል ስሚዝ ከ14 አመት የበኩር ልጁ ጄደን ስሚዝ ጋር የሰራው ሳይንሳዊ ልቦለድ ፊልም ሲሆን በመጀመርያ ሳምንቱ ያስገባው ገቢ ዘንድሮ ከወጡ ፊልሞች ደካማው ተብሏል፡፡

ዊል ስሚዝ በሚተውንባቸው ፊልሞች የቦክስ ኦፊስ የገበያ ደረጃዎችን በመቆጣጠር፤ ለተከታታይ ክፍል ስራዎች ምክንያት በመሆን የሚታወቀውና የ100 ሚሊዮን ዶላር ተዋናይ ይባል ነበር፡፡ ከአፍተር አርዝ በፊት ዊል ስሚዝ የተወነባቸው ያለፉት 10 ፊልሞች በአማካይ በመላው ዓለም እያንዳንዳቸው 150 ሚሊዮን ዶላር ያስገቡ ነበሩ፡፡ ዊል ስሚዝ በትወና ዘመኑ ከ20 በላይ ፊልሞች ሰርቶ ከ6.4 ቢሊዮን ዶላር በላይ በመላው ዓለም በማስገባት የተሳካለት ነበር፡፡

Read 2023 times
Administrator

Latest from Administrator