በየሁለት ሳምንቱ በመፃሕፍት ላይ የንባብ እና የውይይት መድረክ በማድረግ የሚታወቀው ሚዩዚክ ሜይ ዴይ የመወያያ ሥፍራውን ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየም ሬዲዮ ፋና አካባቢ ወደሚገኘው ብሔራዊ ቤተመፃሕፍትና ቤተመዛግብት ድርጅት (ወመዘክር) አዛወረ፡፡ ነገ ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ቤተመፃሕፍትና ቤተመዛግብት አዳራሽ ለውይይት የሚቀርበው መጽሐፍ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ በ1993 ዓ.ም ያሳተመው የኮሌጅ ቀን ግጥሞች” የተሰኘ የግጥም መድበል እንደሆነ ታውቋል፡፡
በመጽሐፉ ከተሰነዱት ግጥሞች መካከል የኃይሉ ገብረዮሐንስ (ገሞራው) “በረከተ መርገም” እና የዮሐንስ አድማሱ “እስቲ ተጠየቁ” ይገኙበታል፡፡ መነሻ ሃሳብ በማቅረብ ለሶስት ሰዓታት የሚዘልቀውን ውይይት የመሻ ሃሳብ በማቅረብ የሚመሩት የሥነጽሑፍ ባለሙያው የዶክትሬት ዲግሪ ተማሪ ገዛኸኝ ፀጋው ናቸው፡፡