Monday, 27 May 2013 15:26

የዮሃንስ ግጥሞች መዓዛ!

Written by  ደረጀ በላይነህ
Rate this item
(16 votes)

በዘመናችን ህይወት የሚላወስባቸው፣ እንደመብረቅ የሚያስደነግጥ መልእክትና ውበት ያላቸው ጥቂት ገጣሚያን ተወልደው ፣በአበባ ሳቅ፣በእምባ ጉንጉን አስደምመውናል፡፡በተዘለዘለ የእምባ ቋንጣ አስለቅሰው፣ትኩስ የውበት ወንዞችን በልባችን መልካዎች አፍስሰዋል፡፡ ምንም እንኳ በገዛ ዘመናቸው ኖረው በኛም ዘመን የሚኖሩ ገጣሚያን መጥረቢያ የማይነካቸው የአድባር ዛፎች ተደርገው፣ በአዲሱ ትውልድ ላይ በር ቢዘጋም፣ወደኋላ ሄደን ስናይ ግን አንዳንዶቹ ብዙ ሊገረዙ የሚገባቸው ጭራሮዎች ያንጨፈረሩ፣ከዛሬዎቹ የሚያንሱት ብዙ ስራዎቻቸው በፍርሃት ገደል ውስጥ እንዲደበቁ ተደርጓል፡ዛሬ በሃሳብ ልቀት የትኛውም ያለፈው ዘመን ገጣሚን የሚያስንቁ እጅግ ጥቂት ገጣሚያን አሉን፡፡ግን አንዱ በቋንቋ፣ሌላው በሃሳብ ይበላለጣል እንጂ ሰበብ ተጠቅሞ በዚሀ ዘመን ግጥም የለም የሚለው ጤናማነት የጎደለው በሽታ ነው፡፡

ምናልባትም የቀደሙት ገጣሚያን ግጥሞች በወጣትነታቸው ምን ይመስል እንደነበር ለማስታወስ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን የ50ኛ ዓመት የኮሌጅ ግጥሞች ማንበብ ጥሩ ነው፡፡እኔ ጆን ድራይደን እንደሚል “እያንዳንዱ ዘመን የየራሱ ጂኒየስ አለው ብዬ አምናለሁ፡፡ትናንት ገጣሚ ከነበረ፣ዛሬ የማይኖርበት ምንም ምክንያት የለም፡፡ ይሁንና ገጣሚያንን አናወዳድርም፤ምክንያቱም መልካቸውና ፍሰታቸው ስለሚለያይ፡፡እንግሊዛዊው ሳሙኤል ጆንሰን እንደሚለው አሌክሳንደር ፖፕ ከ ጆን ድራይደን የሚለይባቸው መልኮች አሉት፤ፖፕ ለህዝብ ቅርብ ልብ አለው፤ድራይደን ደግሞ የጠለቀ ምሁራዊነት ለድራይደን አለው፡፡ድራይደን የውስጡን ድምጽ ወጀብ ሲያዳምጥ፤ፖፕ ደግሞ ስለ አጻጻፍ ህግ ያምጣል፡፡ሁለቱም በየመንገዳቸው ሃሳቦችን እንደጧፍ ያቀጣጥላሉ፡፡ ሎረንስ ፔሬኒ እንደሚሉት የታወቁ ገጣሚያንን ማውራት ጣጣ የለውም፤ግን ኣዳዲሶቹን እንዲህ ናቸው ብሎ ማለት ያስቸግራል፡፡

ስለዚህ ደፋር እንድንሆንና ትክክለኛ ግምት እንዲኖረን ጥሩ አንባቢና መመዘኛ ያለን ልንሆን ይገባል፡፡አዲስ ሰው መቀበል ልበሙሉነት ለጎደላቸው በጣም ዳገት ነው-በተለይ ለፈሪዎች፡፡በምክንያት ለማያምኑ ባይተዋሮች፡፡ አሁን የዮሃንስን ግጥሞች ስናይ በዚህ ስሜት ሊሆን ይችላል፡፡እኔ ግን እንዳየሁት፤ደጋግሜም እንዳነበብኩት ዛሬ የጀመረውን ከቀጠለ ረጂም መንገድ በውበት ይጓዛል፡፡ቋንቋው፣ሃሳቡ፣ፍሰቱ ፣ዜማው ሁሉ ለግጥም የተመቸ ነው፡፡ አንዳንዶቹ ግጥሞቹ ሲነበቡ የገጣሚው መልክና ዕድሜ ከሃሳቡ ጋር አልጣጣም ይልና እንዴት ይህን ነን ያህል አሰበ፡፡እንዴት ይህን ያህል የሚብከነከን ሆነ? ያሰኛል በርግጥ አንዳንድ ቦታ ወረድ ይላል፡፡ግን ያልወረደ ገጣሚ በምድር ላይ ማን አለ?…ያለቃላት በስሜት ብቻ ለሚያነብቡት በሳሎች ውስጥን ያንሾካሹካል የሚባለው ሼክስፒር እንኳ ትንንስ ቁልቁለቶች አሉበት፡፡

እኔ የማምነው ግን አክሱም ሃውልት አጠገብ ሄዶ ምን አይነት ጥበብ ነው እያሉ ረጂሙን በማየት ልካቸውን መለካት እንጂ ትንንሾቹን እያዩ እነዚህ ግን ቀሽሞች ናቸው በማለት አይደለም፡፡ሰማይ ነኩ ግጥሞች ያለው ገጣሚ ያንን ያህል ማሰቡ አቅሙን ያሳያል፡፡ልኩ ያ ነውና! የዮሃንስ ግጥሞች አጫጭርም ረጃጅምም ናቸው።… ረጃጅሞቹ የመንገዱ ርቀት አቅም አልነሳቸውም፤ ትንፋሽ ጠብቀው ፈስሰዋል፤ ሳይንገዳገዱ ደርሰዋል፡፡ቃላት አያጥረውም፤ሃሳቡ አይደርቅም፡፡ ብዙ የፍቅር ግጥሞቹ ረዘም ይላሉ፡፡ አንዳንዶቹም ስነ ቃላዊ ግንድ ያላቸው፣ህዝባዊ ግጥሞች ናቸው፡፡ገጣሚው ብዙ ጊዜ ይህንን ዘይቤ ይጠቀማል፡፡ለምሳሌ ግርማ ሞገሳሟ‹ቴ‹፣”የኔ ፍቅር ላንቺ”…(ትንሽ ቢረዝምም) ምናልባት ለሃገራዊ እሴቶች ጆሮና ልብ የመስጠት ዝንባሌ ይሆናል ብዬ ገምቻለሁ፡፡ለውረንስ ፔረኒ እንደሚከፍሉት ይህ ዘይቤ በ3 ይከፈላል፡፡ ….1. ታሪክ ጠቃሽ 2. ስነ-ጽሁፍ ጠቃሽ 3. መጽሃፍ ቅዱስ ጠቃሽ ናቸው፡፡ እስቲ “ጥምቀትና ሎሚ”ን እንይ፡-(ስለዚህ ስነ-ቃል የቃል ስነ ጽሁፍ ስለሆነ በዚህ ይካተታል፡፡) ከአሲድ፣ከዱላ፣ ከጥፊ፣ከቢላ፣ የተረፈ ገላ…. በሎሚ ታክሞ፣ጃንሜዳ ተበላ፤ ዳግም እስኪታመም፤-- …እስኪያገኘው ሌላ፡፡

                                 * * *

በ‹ስሟ ለማርያም ከደጅሽ ታድሜ፤ ቁራሽ ልማጸንሽ ፣ከበራፍሽ ቆሜ፤ ካ‹የሁሽ ጀምሮ፣… ፍቅርሽ ሰቅዞኛል፣ልብሽ ልቤ ገብቶ፤ ሐሳቤ ካንቺው ነው፣ከደብሩ ሸፍቶ፤ ፍቀጅ እመቤቴ!... ሎሚ መግዣ የለኝ፣ውርወራ አላውቅ ከቶ፣ ጥምቀት ብዬ፣ልንካሽ በ‹ስክሪፕቶ፤ ይህ ግጥም የአሁኑን የፍቅር መግለጫ አሲድና የቀደመውን “ሎሚ ጣሉባት በደረትዋ፣የጌታ ልጅ ናት መሰረትዋን” ያስታውሳል፡፡ዮሃንስ የሁለቱም ትውልድና ቅርስ አድናቂ እንጂ ናቂ አይደለም፡፡ ውበትን አገላብጠው የሚስሙ ድንቅ የተቃራኒ ጾታ ፍቅር ግጥሞችም ቢኖሩት ከምስኪኖች ጋር ተቆራምደው የሚያለቅሱ የጉበኛ ልቦች አሉ፡፡አንዳንዴ ከደሃውና ከተጠቃው ምስኪን፣ወይም ከመላው ምስኪን ጋር ታገኙታላችሁ፡፡ ….ግርማ ሞገሳሟ ቴ ዛሬ እናን ባየሽን… እንኳን ስሙን ጠርተን፣ደርሰን ከሰፈሩ፣ ልኩን አስታጥቀነው፣ገጥመን ከግንባሩ፣… እንዲሁም እንዲሁ ነን፣ትርጁማን አናጣ፣ ያልነውን ተርጉሞ፣ባላልነው ሚቀጣ፡፡ ብናለቅስ--“አበዱ!”፤ጥለን ብንሄድ”ፈሩ!”፣ ብንጠይቅ “ጠገቡ!”፤ብናውቅ--“አሸበሩ!”፤ የሚለን ብዙ ነው፣ሚከሰን ዘርዝሮ፣ እንኳንስ ሊሸኘን፣ካሳ ድርጎ ሰፍሮ፡፡ “ስንብት”አንዱ ራሮት ነው፤አንዱ የሩቅ ድምጽ፣ የሰቀቀን ዜማ ነው፡፡

ስንቱን የቀለም ቀንድ፣ ችኩል ጅብ ነካክሶ፣ ቀለሙን ደፋፍቶ፣ጥበብን አራክሶ፤ አድርባይ ጤፍ ቆዪው፣በዝቶ በመንደሩ፣ ጥራዝ-ነጠቅ እውቀት፣ተስፋፍቶ ባገሩ፣ ብራና በረቀ፤…መቃ ብ‹ር ነጠፈ፤ሊቃውንት ሰፈሩ፤ ፀሃፍት አንገት ደፉ፤አበው ተሸበሩ፤ጠቢባንም ፈሩ፡፡ ድጓ ጾመ ድጓ፣ተሰቃቅለው ቀሩ፤ --እንደተደጎሱ…

                           * * *

ደጅ ሁሉ ተዘጋ፣ሆድ ሁሉ ተከፋ፣ በግ ሁሉ ተነዳ፣በተኩላ ተበላ፤…ቆዳው ሳይቀር ጠፋ፤ ወስፋቱን ሊያስተኛ፣ደበሎሊደርብ፣ተሜ ላይ ታች ለፋ፡፡ ምጣድ ይጥድ ሳይኖር፣”የዕለት እንጀራዬን ስጠኝ”ባዩ በዛ፤ የበሰለ እንጀራም በበዮች ተከብቦ፣በየጥጋጥጉ ሻገተ ጠነዛ፡፡…..

* * *

መንገድ እንዳትባክን፣ልቤ ካለ ልብዋ፣ “ይቅናህ ልጄ!”በይኝ!...ደህና ሁኝ እመዋ! ደህና ሁን አስኳላ !ደህና ሁን መምህሩ! ደህና ሁን ባልንጀር! ደህና ቆይ መንደሩ! --ጋራው ሸንተረሩ፤አድባሩ፣ደብሩ፣ ደህና ሁኑ እንግዲህ!...በችጋር ተገፋ፣ልቤማ ሰነፈ፤ ኑሮውን ሊረታ፣ለከንቱ ብልጭልጭ ውበት ተሸነፈ፡፡ እዚህ ላይ የምናያቸው በርካታ ቃላት እማሬያዊ ብቻ ሳይሆኑ ፍካሬያዊም ፍቺ ያላቸው ናቸው፡፡…እነዚህ ደግሞ ለልብ የልብ ለመናገር ይሆናሉ፡፡ እስቲ እጅግ ከሚመስጡት የፍቅር ግጥሞቹ ጥቂት ስንኞች ልውሰድ፡- መዋስዕት፣ምዕራፍ፣ድጓ፣ጾመ ድጓ፣ አቋቋም፣ዝማሬ፣--ቀልብ እንደሚያረጋ፣ እንደ ነፍስ ወጌሻ፣እንደ ሥጋ አለንጋ፣ እንደምትቃርመው፣መንፈሴ አደግድጋ፣ ሥጋ እንደሚሸሻት፣ቤቱ ስትጠጋ፣ ካንቺ ከውዴ ጋ…ከስሜቴ ሲሳይ፤….እያለ ይቀጥላል፡፡የቓላቱን ውበት እዚህ ጋ ማየት ይቻላል። አሻም ቴ እጅግ መሳጩና አስደኛቂው ግጥም ነው፡

፡--ለኔ!ገጽ 19… የዮሃንስ መጽሃፍ ውበት ከሽፋኑ ይጀምራል።…ቋንቋው በዚህ ዘመን ላለው የቃላት ድህነት እንደማስታገሻ ነው ማለት ይቻላል፡፡በዚያ ላይ አዳዲስ ቃላትን ኮይን ሊያደርግ የሚከረበት መንገድ የሚያበረታታ ነው፡፡….እንደ ችግር እንይ ካልን፣ አንዳንዶቹየግርጌ ማስታወሻዎች ብዙም ጠቃሚ ስላልሆኑና ባብዛኛው የሚታወቁ ስለሆኑ ቢቀሩ ጥሩ ነበር የሚል ሃሳብ አለኝ፡፡ከዚያ በተረፈ ባብዛኛው የተጠቀማቸው ጠቃሽ ዘይቤዎች አንዳንድ ቦታ ዝቅ ማለታቸው አይወደድም፡፡ለምሳሌ በህዝብ ዘንድ እጅግ የተለመዱት፤ግርማ ሞገሳሟ ቴ..ግጥሙን አጋምሶታል፡፡ ይህ ዘይቤ ታዲያ ከፍታው ጨምሮ ወደ ላይ ሲያንጠራራም፣ወደ ታች ዝቅ ብሎ ሲያስጎነብስም ጥሩ አይደለም፡፡ብቻ--ብቻ ዮሃንስ ትልቅ ልብ፣ትልቅ ምናብ አለው፡፡ይህንን አይውሰድበት!! ምሁራዊ ከፍታቸው ጨምሮ ማንጠራራት ዝቅ ብሎ ሲያስጎነብስ አይወደድም፡፡ Over intellectualization

Read 9361 times