Print this page
Monday, 27 May 2013 14:36

ሴቶች ከፍቅረኛቸው ጀርባ እንዲመለከቱ የሚገፋፉ 5 ምክንያቶች

Written by 
Rate this item
(104 votes)

ወንዶች ከፍቅረኛቸውና ከትዳራቸው ውጭ እየሄዱ እንዳመጣላቸው ለመተኛት ብዙም ምክንያት አያስፈልጋቸውም ይባላል። ኮስሞፖሊታን ረቡዕ እለት ያሰራጨው ፅሁፍ ግን፣ ከፍቅረኛ ጀርባ ማማተርና ግራ ቀኝ መቀላወጥ፣ በወንዶችም ሆነ በሴቶች ዘንድ እኩል ነው ይላል። ምናልባት በወንዶችና በሴቶች መካከል ልዩነት ካለ፣ የሚቀላውጡበት ምክንያት ላይ ነው። በእርግጥ፣ በመካከላቸው ልብን የሚያጠግብ ፍቅር ሳይኖር “ፍቅረኞች” የሚል ስያሜ ከያዙ፣ በስሜት ውጭ ውጭውን ለመናፈቅ ሌላ ምክንያት አያስፈልጋቸውም - አላፊ አግዳሚውን ለማየት አይናቸው የሚቅበዘበዘው ስለማይዋደዱ ነው። በፍቅር የሚዋደዱ ከሆነስ? ይሄ ነው ጥያቄው። ከፍቅረኛቸው ውጭ ሌላ ወንድ እንዲመኙ የሚገፋፉ

5 ምክንያቶች በሚል ኮስሞፖሊታን ባቀረበው ፅሁፍ መነሻነት ነገሩን ብናስብበት አይከፋም።

1. በኑሮ ሽግግር የሚፈጠር ጭንቀት የኑሮ ሽግግር ማለት፣ ከዩኒቨርስቲ መመረቅ ወይም ቀለበት ማሰር ሊሆን ይችላል። 30ኛ አመት እድሜ ላይ መድረስ፣ አልያም አንዱን ስራ ትቶ ሌላ ለመሞከር መወሰንም እንደ ኑሮ ሽግግር ይቆጠራል። የኑሮ ሽግግር፣ አነሰም በዛ፣ በአእምሮዋ ውስጥ ብዙ ጥያቄዎችን መፍጠሩ አይቀርም። የህይወቴ አቅጣጫ ወዴት ያመራል? ከዚህ በኋላ ምንድነው የማደርገው?... እነዚህንና ሌሎች ጥያቄዎችን እያነሳች ከፍቅረኛዋ ጋር ብትመክር ተገቢ ነው፣ በጣም ከተደጋገመ ግን መሰላቸትን ያስከትላል። ለነገሩማ፣ ለብቻዋ ሆና ነገሩን እያወጣች እያወረደች ማሰብና ማሰላሰል እንዳለባት አያከራክርም። ለጥያቄዎቿና ለሃሳቦቿ፣ መቋጫ እያበጀች ካልሄደችና ያንኑን መልሳ መላልሳ የምታሰላስል ከሆነ ግን፣ አላስፈላጊ ጭንቀት ይፈጥርባታል። በማያቋርጥ የእንጥልጥል ስሜት እየተብሰለሰለች ምቾት ታጣለች። ይሄኔ፣ ከጭንቀት የሚገላግልና ለአፍታም ቢሆን ከአስቀያሚው ስሜት የሚያዘናጋት ሰው ብታገኝ ትመኛለች። ከፍቅረኛዋ ውጭ ሰው ፍለጋ ትማትራለች። (በእርግጥ፣ ሰው ማየት አስጠልቷት የምትተኛ ሴትም አትጠፋም። ወይም ከሴት ጓደኞቿ ጋር ሌላ ሌላ ነገር እያወራች ጭንቀቷን ለመርሳት የምትሞክርም ትኖራለች)። ነገር ግን፣ ከኑሮ ሽግግር ጋር የሚከሰት ጭንቀት፣ ከሌላ ወንድ ጋር እንድትወጣም ሊገፋፋት ይችላል።

2. የጓጓችለትና የኮራችበት ነገር፣ ፍቅረኛዋ ካልተጋራት ሴቶች፣ አድናቆትን መስማት ይፈልጋሉ ይባላል። በአድናቆት ጥምና ረሃብ ነጋ ጠባ ይሰቃያሉ ማለት ግን አይደለም። በጣም የምትወዱትን ነገር ሌሎች ሰዎች ቸል ሲሉት፣ የምትጓጉለትን ነገር ሲዘነጉት፣ የምታከብሩትን ነገር ከምንም ሳይቆጥሩት ሲቀሩ ምን ይሰማችኋል? ይደምቃል፣ ይሟሟቃል ያላችሁትን ነገር፣ ሰዎች ሲያደበዝዙትና ሲያቀዘቅዙት… ንዴት፣ ሃዘን፣ ድብርት ይፈጠር የለ? ቢያንስ ቢያንስ፣ “ኩም አልኩ” የሚባለው አይነት አስቀያሚ ስሜት ይፈጠራል። ሴቶች፣ ከምር ትልቅ ዋጋ የሚሰጡትና የሚኮሩበት ነገር ሲሰሩ፣ ስሜታቸውን ተጋርቶ ነገሩን እንዲያደምቅና እንዲያሟሙቅ የሚጠብቁት ፍቅረኛቸውን ነው። ፍቅረኛዋ፣ ነገሩን በቸልታ ካለፈው፣ “ኩም” ትላለች። ብሩህ አድርጋ የቀረፀችው የህይወት ምስል ይጨልምባታል። እናም የጨለመውን የሚያበራ፣ አልያም በመጠኑ ፈካ የሚያደርግ ሌላ ሰው ለማግኘት ግራ ቀኝ ትቃኛለች። በእርግጥ፣ ድብርትን የሚያባርርና ብሩህ ስሜትን የሚያላብስ ፊልም በማየት ከጭጋጋማው መንፈስ ለመላቀቅ የምትሞክርም ትኖራለች። አልያም ድብረቷ በጭፈራ እንዲወጣላት ከጓደኞቿ ጋር ናይት ክለቦችን ስታዳርስ ብታድር አይገርምም። የደበዘዘውን አለም የሚያበራ የሆነ ወንድ ለማግኘት እንድታስብም ሊያነሳሳት ይችላል።

3. ሊበጠስ የተቃረበ ግንኙነት እየሳሳ ሊበጠስ የደረሰ የፍቅር ግንኙነት፣ ምንም ቢሆን የፍቅረኞቹን ስሜት መረበሹ አይቀርም። በእርግጥ፣ “አንድ ሐሙስ የቀረው የፍቅር ግንኙነት”፣ አንዳንድ ሴቶችን ወደ ፍቅረኛቸው ይበልጥ እንዲጠጉ ሊገፋፋቸው ይችላል። ነገር ግን፣ ከወዲሁ ከፍቅረኛቸው ጀርባ አሻግረው እንዲመለከቱና ወደ ሌላ ወንድ እጃቸውን እንዲዘረጉ ሊያነሳሳቸውም ይችላል። የፍቅር ግንኙነት ከተቋረጠ፣ አንዳች የጉድለትና የክፍተት አስቀያሚ ስሜት ይፈጠራል። በዚህ ስሜት ላለመዘፈቅ ብላ ቅድመ ዝግጅት ታደርጋለች፤ ጉድለትን የሚሞላ ማካካሻና ምትክ ፍለጋ አካባቢዋን ትቃኛለች። ይሆናል የምትለው ወንድ ያየች ሲመስላትም፣ ለመሞከር ትነሳሳለች።

4. ሲጀመር አዝናኝ የነበረው ፍቅር ሲደነዝዝ በፍቅር ሲቀራረቡ፣ የሌት ተቀን ሃሳባቸው ሁሉ ደግ ደጉ ላይ ያተኩራል። አንዱ ከሌላው ለሚያገኘው ደስታ ትልቅ ዋጋ ይሰጣሉ። አንዱ የሌላውን መልካም ነገር ከልብ እያደነቀ ይረካል። ሲተያዩ፣ ሲያወሩ፣ ሲበሉም ሆነ ሲተኙ… ብዙ የሚያስደስቱ ነገሮችን ያገኛሉ። የልባቸውን ያወራሉ፣ ይቀላለዳሉ፣ ይተሳሰባሉ፣ ይከባበራሉ። በጣም ሲቀራረቡ ግን፣ ቀናት ተንከባልለው ወራት ሲያልፉ ግን፣ መከባበር ይቀርና መቆጣጠር በቦታው ይተካል። መቀላለድ ይቀርና መናቆር ይመጣል። የልብ ማውራት ሳይሆን ድብብቆሽና ጥርጣሬ ይበቅላል። ይሄ ሁሉ የሚሆነው፣ የአንዳቸውም ፍቅር ሳይቀንስ ነው። አንዳቸውም ሌላውን አልበደሉ ይሆናል። ግን፣ እርስ በርስ ፍቅራቸውን የሚያጣጥሙበትና የሚገልፁበት ሁኔታ ተለውጧል። ያንን የፍቅር አኗኗር ትተው፣ በሌላ “ልማዳዊ” አኗኗር ቀይረውታል። አንዱ ሌላውን የሚያይበት መነፅር ተለውጧል። ጥሩ ጥሩው ሳይሆን ጉድለት ጉድለቱ ብቻ እንዲታያቸው ማድረግ ጀምረዋል። ይሄኔ፣ የፍቅር ህይወታቸውን መልሰው ለማደስ መፍትሄ ካልፈጠሩ በቀር፣ አልያም የደነዘዘውን ሕይወት እንደእጣ ፈንታ በፀጋ ካልተቀበሉ በቀር፣ ደጅ ደጁን፣ ወጪ ወራጁን መመልከት መጀመራቸው አይቀርም።

5. አዳራቸው እንደ ቀድሞው አጓጊነቱ ሲያቆም ሲጀመር የነበረው ፍቅር ሲደበዝዝ፣ የአልጋ ቆይታቸውም እንደ ድሮው አጓጊነቱ እየቀረ ሲሄድ፣ መፍትሄ ያስፈልገዋል - ፍቅራቸውን ለማንቃትና ለማደስ፣ አልጋቸውን ለማነቃነቅና ለመፈንደቅ። ይሄ ቀላል አይደለም። በፍቅር ወይም በትዳር አንድ አመት ከቆዩ በኋላ፣ ግንኙነታቸው እንደ አጀማመራቸው አጓጊ እንዲሆን ማድረግ እንደሚያስፈልግ ያምኑበታል? ድሮ እሷ እሱን፣ እሱ ደግሞ እሷን ለመማረክ ነበር የሚያስቡትና የሚጥሩት። ከአመት በኋላ ግን ሃሳብና ጥረታቸው፣ አንዱ ሌላውን ለመቆጣጠር ነው - እንከን ፍለጋ። ይህንን ወደ ቀድሞው ትክክለኛ የፍቅር ግንኙነት መመለስ እንዳለባቸው ያምኑበታል? ካላመኑበት፣ የደነዘዘውን ፍቅር ማንቃትና የቀዘቀዘውን መኝታ ቤት ማሞቅ አይችሉም። ይሄኔ፣ ፍንደቃ እየናፈቃቸው ሌላ ወንድ ማሰብ የሚጀምሩና ወዲህ ወዲያ ጎራ የሚሉ ይኖራሉ።

Read 66881 times
Administrator

Latest from Administrator