Monday, 27 May 2013 13:49

ወንጀልን ለመከላከል በሚታጠቁት መሳሪያ የግድያ ወንጀል የሚፈፅሙ የፖሊስ አባላት

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

ወንጀልን ለመከላከል በሚታጠቁት መሳሪያ የግድያ ወንጀል የሚፈፅሙ የፖሊስ አባላት በርካታ መሆናቸውንና በአዲስ አበባ ብቻ ባለፉት ሰባት አመታት ከእስር በላይ በፖሊስ አባላት የተፈፀሙ ግድያዎች እንዳሉ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ፖሊስ በበኩሉ፣ አብዛኞቹ የፖሊስ አባላት ህግ ለማስከበር፣ ወንጀልን ለመከላከልና ፍትህን ለማስፈፀም ጠንክረው የሚሰሩ መሆናቸውን ገልፆ፣ የፖሊስን አቋም በተቃረነ ወንጀል የሚፈፅሙ አባላትን በአገሪቱ ህግ መሰረት ለፍ/ቤት በማቅረብ ተገቢውን እርምጃ እየወሰደ መቆየቱን ይገልጻል፡፡ የፖሊስ አባላት ፅኑ የፍትህ አቋም እንዲኖራቸው፣ ሥነ ስርዓት አክባሪነታቸዉ እንዲጠናከር፣ እንዲሁም ሥነ ስርዓት የሚጥሱትም ተገቢውን ቅጣት እንዲያገኙ የተለያዩ የመተዳደሪያ ደንቦች ተግባራዊ እየተደረጉ መቆየታቸውን ፖሊስ ይገልፃል፡፡

የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የሥነ ስርዓት ደንቡን ይበልጥ ለማሻሻል የዲሲፕሊን መመሪያና የቅጣት አወሳሰን ሰነድ አዘጋጅቶ እንዳጠናቀቀ ተጠቁሟል፡፡ በባህር ዳር ያጋጠመውን አይነት አሰቃቂና አሳዛኝ ድርጊት ዳግመኛ እንዳይከሰት ለመከላከል፣ በፖሊስ አባላት የሚፈፀሙ የወንጀል ድርጊቶችና የመፍትሄ እርምጃዎች ላይ ውይይት እንዲፈጠር ለማበረታተት በማሰብ ከአዲስ አበባ ዙሪያ ከፖሊስና ከፍ/ቤት ያሰባሰብናቸውን መረጃዎች አቅርበናል፡፡ ከ2 ዓመት እስከ ዕድሜ ልክ ተፈርዶባቸዋል ባልደረባውን በ18 ጥይት መትቶ የገደለው ፖሊስ ጉዳይ በፍ/ቤት እየታየ ነው የአዲስ አበባ ፖሊስ አባል የሆነው የ20 ዓመቱ ኮሎኔል አወል አብዱልቃድር መስከረም 13 ቀን 1999 ዓ.ም ቦሌ ክ/ከተማ ቀበሌ 15 ክልል አቶ ሚካኤል ተሻለ የተባለ ግለሰብን ከመኪናው ያስወረደው “ትላንት ዘበኛህ የቤት ሠራተኛህን ደብድቦ ከያዝነው በኋላ አምልጦናል፤ እንፈልገዋለን” በማለት ነው፡፡ ከፖሊስ በተገኘ መረጃ መሰረት፤ ከተወሰነ የንግግር ልውውጥ በኋላ ኮሎኔል አወል በታጠቀው ክላሺንኮቭ ጠብመንጃ ግለሰቡን ጭንቅላቱ ላይ በመምታት በመግደሉ በከባድ ሰው የመግደል ወንጀል ተከስሷል፡፡ ጉዳዩን የመረመረው ፍ/ቤትም ግንቦት 7 ቀን 1999 ዓ.ም በዋለው ችሎት በዕድሜ ልክ ፅኑ እስራት እንዲቀጣ በይኗል፡፡

ኮሎኔል አለሙ አያኖ በጉለሌ ክ/ከተማ፣ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን ፊት ለፊት፣ ተስፋዬ ታደለ የተባለ ግለሰብ “ወደ ህግ ቦታ አልሄድም” አለኝ በሚል ምክንያት ለስራ በተሰጠው ክላሽንኮቭ ጀርባው ላይ በመምታት ስለገደለው ተከሶ ፍ/ቤት የቀረበው በጥር 2000 ዓ.ም ነበር፡፡ ሰኔ 18 ቀን 2000 ዓ.ም ፍ/ቤቱ በዋለው ችሎት ተከሳሹ በ10 ዓመት ፅኑ እስራት እንዲቀጣና ለሁለት ዓመት ከህዝባዊ ጥቅማጥቅም እንዲታገድ ወስኗል፡፡ የ23 ዓመቱ ኮንስታብል ሱልጣን ጀማል አሁን የሚገኘው ወህኒ ቤት ነው፡፡ የዛሬ ሰባት ዓመት ከስራ ባልደረባው ኰንስታብል አንሰ ሼህ አብደላ ጋር በተፈጠረ ጊዜያዊ ጠብ ምክንያት ለጥበቃ ሥራ በተሰጠው ክላሽንኮቭ ጠብመንጃ ግለሰቡን ተኩሶ በመግደሉ ፍ/ቤት በ15 ዓመት ፅኑ እስራት እንዲቀጣ ወስኖበታል፡፡ የፌደራል ፖሊስ አባል የሆነው የ34 ዓመቱ ምክትል ሳጅን ደበሽ ታረቀኝም ወህኒ የገባው የስራ ባልደረባውን መግደሉ በፍ/ቤት ተረጋግጦበት ነው፡፡

ግለሰቡ፤ ኮንስታብል መሶር ዊይሰን የተባለውን ባልደረባውን አድርጐት በነበረው የወታደር ከስክስ ጫማ ጭንቅላቱ ላይ በመምታትና በመርገጥ ጉዳት ያደረሰበት መስከረም 17 ቀን 2000 ዓ.ም ሲሆን ለጥቂት ቀናት ህክምና ሲከታተል ቆይቶ ህይወቱ ሊያልፍ ችሏል፡፡ ፍ/ቤቱ የካቲት 13 ቀን 2001 ዓ.ም በዋለው ችሎት ተከሳሹ በ6 ዓመት ፅኑ እስራት እንዲቀጣ በይኖበታል፡፡ የፌደራል ፖሊስ አባሉ ኮሎኔል ኡፋይሳ ጉንዲስ ሐምሌ 3 ቀን 2004 ዓ.ም እስራኤል ኤምባሲ አካባቢ በጥበቃ ላይ የነበረውን ባልደረባውን በ18 ጥይት መትቶ በመግደል ተጠርጥሮ ክስ የተመሰረተበት ሲሆን ጉዳዩ በፍ/ቤት በመታየት ላይ እንደሚገኝ ከፖሊስ የተገኘ መረጃ ይጠቁማል፡፡ ኮሎኔል ብዟየሁ ግርማም፤ “ሰው በመግደል ወንጀል ተጠርጥሮ ጉዳዩ በፍ/ቤት እየታየ ይገኛል፡፡ ኮሎኔሉ ሌሊት በሥራ ላይ እያለ ከአዲስ አበባ ወደ ድሬዳዋ በመጓዝ ላይ ያለ የነበረ ሚኒባስን እንዲቆም ይጠይቃል፡፡ ሹፌሩ መኪናውን ለማቆም በማቀዝቀዝ ላይ ሳለ ኮሎኔሉ ባልታወቀ ምክንያት ተኩስ በመክፈቱ የሚኒባሱ ሹፌር ህይወት ማለፉን የክስ መዝገቡ ያመለክታል፡፡

ኮሎኔል ብዟየሁ በተጠረጠረበት የሰው መግደል ወንጀል ክስ ተመስርቶበት ጉዳዩ በፍርድ ሂደት ላይ ሲሆን ድርጊቱን መፈፀሙን እንዳመነ የፖሊስ መረጃ ይጠቁማል፡፡ “ድርጊቱን የፈፀምኩት ሰይጣን አሳስቶኝ ነው” ብሏል - ለፍ/ቤት በሰጠው ቃል፡፡ የ22 ዓመቱ ኮሎኔል ሃብታሙ ካሣሁን ጌታሁን፤ እስር ቤት የገባው በግድያ ሳይሆን በዘረፋ ወንጀል ተከሶ ነው፡፡ መስከረም 12 ቀን 2003 ዓ.ም ከቀኑ በ9 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ክ/ከተማ ልዩ ቦታው ዑመር ስመትር ት/ቤት አካባቢ ወ/ት ዘሃራ አብዱራህማንን በያዘው ሽጉጥ ሰደፍ ቀኝ ጉንጯ ላይ በመምታት ከጣላት በኋላ፣ ከቦርሳዋ ውስጥ 1.514566.55 የያዙ የባንክ ቼኮች እንዲሁም 755 ብር የሚያወጡ ልዩ ልዩ እቃዎች ወስዶ ሊያመልጥ ሲል እጅ ከፍንጅ ይያዛል፡፡ በፈፀመው ከባድ የውንብድና ወንጀል የተከሰሰው ግለሰቡ፤ ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ ፍ/ቤት በ12 ዓመት ፅኑ እስራትና በ2ሺ ብር እንዲቀጣ ወስኗል፡፡

ኮሎኔል እዮብ ቀልሜሳ የዛሬ አራት ዓመት ሦስት የሥራ ባልደረቦቹ ላይ 18 ጥይቶችን በመተኮስ በፈፀመው የግድያ ሙከራ ተከስሶ ፍ/ቤቱ ጥፋተኝነቱን በማረጋገጡ ነው ወህኒ የወረደው - የ10 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈርዶበት፡፡ በእርግጥ ከዚህ ቀደምም ታስሮ ተፈቷል፡፡ በ1999 ዓ.ም በአደገኛ ቦዘኔነታቸው ከሚታወቁ ሁለት አባሪዎች ጋር ከሌሊቱ 6፡30 ላይ አንድ ግሮሰሪ ገብቶ ከአስተናጋጅ ላይ ገንዘብ በመውሰድና እቃዎችን በመሰባበር ክስ ተመስርቶበት ታስሮ ነበር፡፡ ከተፈታ በኋላ አንድ የስራ ባልደረባው በስብሰባ ላይ “ስራህ በሙሉ ከአንድ ፖሊስ የሚጠበቅ አይደለም፤ ሁልጊዜ እየታሰርክ ትፈታለህ፣ ከወንጀለኛ ጋር ነው የምትውለው” በማለት ከመጥፎ ምግባሩ እንዲመለሰ ይገመግመዋል፡፡ ኮሎኔል እዮብ ግን በስራው ከመፀፀት ይልቅ ቂም ይይዛል፡፡

ስብሰባው ሲጠናቀቅም “ለምሳ ተረኛ የግቢ ጥበቃ ነኝ” በማለት ክላሽንኮቭ ጠብመንጃና 30 ጥይት በመረከብ የገመገመውን ባልደረባውን ጨምሮ ሦስት የስራ ባልደረቦቹ ላይ 18 ጥይቶች በመተኮስ በፈፀመው የግድያ ሙከራ ተከስሶ ጥቅምት 4 ቀን 2001 ዓ.ም በ10 ዓመት ፅኑ እስራት እና በሁለት ዓመት ከህዝባዊ መብት እንዲታገድ ተወስኖበታል፡፡ የ25 ዓመቱ ረዳት ሳጅን አስሬ አየለ ባይዴ፤ ባለፈው ዓመት አንድ ግለሰብ በቁጥጥር ስር ለማዋል ከ20 በላይ የፖሊስ አባላት ጋር በመሆን ወደ መኖርያ ቤቱ ይሄዳል፡፡ ተፈላጊው እጁን ለመስጠት ፈቃደኛ ባለመሆኑ ፖሊሶች አጥር ዘለው ይገባሉ፡፡ ይሄኔ ግለሰቡ የፖሊስ አባላቱ ላይ ድንጋይ፣ ብርጭቆና ስለት መወርወር ይጀምራል፡፡ ረዳት ሳጅን አስሬ የፖሊስ ሙያ የሚጠይቀውን ጥበብ በመጠቀም ተጠርጣሪውን መያዝ ሲገባው በያዘው ክላሽ ጠብመንጃ ግለሰቡ ላይ በመተኮስ አንገቱ ላይ ይመታውና ወዲያው ህይወቱ ያልፋል፡፡

ሳጅን አስሬ አየለ ባይዴ፤ ህጋዊ መከላከልን ከመጠን በማሳለፍ በፈፀመው የግድያ ወንጀል ተከስሶ ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ ፍ/ቤት በሁለት ዓመት ቀላል እስራት እንዲቀጣ ወስኗል፡፡ ከፖሊስ የተገኘ መረጃ እንደሚያመለክተው፤ የፖሊስ አባላት በተለያዩ የግልና ሌሎች ያልታወቁ ችግሮች የተነሳ ራሳቸውን የሚያጠፉበት አጋጣሚዎችም አሉ - ብዙ ነው ባይባልም፡፡ በ1998 ዓ.ም አንድ ኮንስታብል በሚያድርበት ካምፕ ውስጥ በራሱ ክላሽንኮቭ ጠብመንጃ ደረቱ ላይ ሁለት ጊዜ በመተኮስ እራሱን በራሱ ያጠፉ ሲሆን በ2000 ዓ.ም ደግሞ በብሄራዊ ቤተመንግስት በጥበቃ ሥራ ላይ ተመድቦ የነበረ አንድ ምክትል ሥራ ላይ ተመድቦ የነበረ አንድ ምክትል የአስር አለቃ በራሱ መሳሪያ አንገቱ ሥር በመተኮስ ራሱን በራሱ አጥፍቷል-ከፖሊስ በተገኘ መረጃ፡፡

Read 4325 times