“ዊ ፋውንድ ላቭ› የቢልቦርድ 100 ትኩስ ነጠላ ዜማዎችን ደረጃ እየመራ ሲሆን ሪሃና ገበያውን በነጠላ ዜማዋ እንዲህ ስትቆጣጠር ለ11ኛ ጊዜ ነው፡፡ በቢልቦርድ የ53 ዓመት ታሪክ ለዚህ ስኬት የበቃች ሰባተኛዋ አርቲስትም አድርጓታል፡፡ የሪሃና ሁለተኛው ነጠላ ዜማ ‹ዩ ዳ ዋን› ትናንት ተለቅቋል፡፡ በአዲሱ አልበሟ ከጄይዚ ጋር ብቻ የሰራችው ሪሃና፤ ቀደም ሲል ከ17 በላይ ምርጥ ዘፋኞች ጋር የሰራቻቸው ዜማዎች ያሏት ሲሆን በ2012 ከማዶና ጋር ለመስራት እንዳሰበች ታውቋል፡፡
ወደ ሙዚቃው ኢንዱስትሪ ከገባች ገና 6 ዓመት የሆናት በርባዶሳዊቷ ሪሃና ከዚህ በፊት ባሳተመቻቸው 5 አልበሞች በመላው ዓለም 20 ሚሊዮን የዓልበሞቿን ቅጂዎችና 60 ሚሊዮን ነጠላ ዜማዎቿን ቸብችባለች፡፡ባለፈው ዓመት ከሙዚቃ ኢንዱስትሪው 29 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ያገኘችው ሪሃና፤ ፋሺን በመቀያየር ትታወቃለች፡፡ በዓመት ለፀጉሯ ውበት ብቻ 1 ሚሊዮን ዶላር እንደምታወጣ የዘገበው ዴይሊሜል ነው፡፡ በ2011 የሃብት መጠኗ 72 ሚሊዮን ዶላር የተገመተላት ሪሃና፤ ባለፉት 5 ዓመታት የፀጉሯን አሰራርና ቀለም 13 ጊዜ መቀያየሯን ያመለከተው ዴይሊ ሜል፤ ፋሽኗን አንዴ ስትቀይር በአማካይ 90ሺ ዶላር እንደምታወጣ አስታውቋል፡፡