Saturday, 04 May 2013 10:04

የፍቺ ቢዝነስ በአሜሪካ፡ ከ900 ሺ ፍቺ በአመት 30 ቢ. ዶላር የኢትዮጵያውንማ፣ “ቤቱ ይቁጠረው” ነው የሚባለው!

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

(የአሜሪካውያን ነገር! መፍትሄ ይዞ ብቅ የሚል አይጠፋም። ሚቸል ክሮዝቢ፣ የፍቺ ወጪዎችን በሶስት እጅ የሚቀንስ ዘዴ በመፍጠር ቢዝነስ ጀምራለች።) አዲስ አበባ ውስጥ ሁለት መኖሪያ ቤት የነበራቸው ባልና ሚስት፣ በፍቺ ሲለያዩ የፈጠሩትን ፀብ ልንገራችሁ። እንደ ምርጫቸው አንድ አንድ መከፋፈል ይችሉ ነበር። ባል አንደኛውን ቤት መረጠ። ሚስት ምንም አልከፋትም። የመኖሪያ ቤቶቹ ዋጋ ተቀራራቢ ስለሆነ፣ ሌላኛውን ቤት መረጠች። በቃ? በጭራሽ! ሚስትዬው ያለምንም ጣጣ ስለተስማማች፣ ባልዬው በቁጭትና በእልህ ተነሳስቶ ሃሳቡን ቀየረ። እንለዋወጥ አለ - ሚስትን ለማሳረር በመመኘት።

የራሱን ጥቅም ሳይሆን፣ የሚስቱን ጉዳት ለማየት ነው የናፈቀው። በእርግጥ ሚስትዬው፣ አንደኛውን ቤት እስካገኘች ድረስ ግድ አልነበራትም። ግን እልህ ውስጥ ገባች፤ “አይሆንም!” አለች። ሁለቱን ለማስታረቅ ያልተደረገ ሙከራ ባይኖርም አልተሳካም። ስለዚህ መኖሪያ ቤቶቹ ተሸጠው በገንዘብ እንዲከፋፈሉ ተወሰነ። አቶ ባል፣ ነገርዬው እንዲህ እየከረረ እዚህ ደረጃ ላይ የሚደርስ አልመሰለውም ነበር። ግን፣ የተበላሸውን ነገር መልሶ ማስተካከል አይችልም። ቤት የሚገዛ ሰው ፈልገው ማምጣት አለባቸው፤ ወይም ደግሞ በፍርድ አፈፃፀም መስሪያ ቤት በኩል፣ በሃራጅ ቤቶቹ ይሸጣሉ። ያው፤ ለሃራጅ የቀረበ ንብረት ብዙም ዋጋ አያወጣም። ለዚህም ነው፤ ባልዬው ቤት የሚገዙ ሰዎችን አፈላልጎ ያመጣው። ይህን ሁሉ ጣጣ በመፍጠሩ የተበሳጨችው ሚስትዬው ግን ፈቃደኛ አልሆነችም። በሃራጅ ካልተሸጠ ሞቼ እገኛለሁ አለች። የራሷን ጥቅም ከማስላት ይልቅ፣ የባልዬውን መክሰር ለማየት ጓጉታለች።

ከፍርድ አፈፃፀም ሰራተኞች እንደሰማሁት፣ ቤቶቹ በሃራጅ ስለተሸጡ ሁለቱ ሰዎች ወደ 300 ሺ ብር ገደማ ከስረዋል። ከፍቺ ጋር አላስፈላጊ እልህ የሚፈጠረው በኢትዮጵያ ብቻ አይደለም። የትም አገር ቢሆን፣ ትዳር በፍቺ ሲፈርስ፣ ብዙውን ጊዜ አዲስ ጥላቻና ቂም ያበቅላል። ባለትዳሮቹን ለፍቺ ከገፋፋቸው ጥላቻ ይልቅ፣ ለመፋታት ከወሰኑ በኋላ በንብረት ክፍፍልና በልጅ አስተዳደግ ጉዳዮች ላይ ሲከራከሩ የሚፈጠረው ጥላቻ የባሰ ነው። በእርግጥ በሰለጠኑት አገራት፣ የፍቺ ጣጣዎችን በስርዓት ለማስኬድና የመናቆር ስሜቶችን ለማብረድ፣ ባልና ሚስት የህግ ባለሙያዎችን (ጠበቆችን) ይዘው ነው የሚከራከሩት ወይም የሚደራደሩት። ግን፣ ይሄም ቢሆን ወጪው ቀላል አይደለም። አሜሪካ ውስጥ፣ በፍቺ የሚለያዩ ጥንዶች፣ እያንዳንዳቸው በአማካይ 10 ሺ ዶላር ለህግ አማካሪ ይከፍላሉ። አንድ ትዳር ሲፈርስ 20 ሺ ዶላር ለጠበቆች ክፍያ ይውላል ማለት ነው። ሌሎች ወጪዎች ተጨምረውበት፣ በአሜሪካ የፍቺ ነገር በአመት 30 ቢሊዮን ዶላር ገደማ እንደሚፈጅ፣ ሰሞኑን የወጣው የፎርብስ መፅሄት ገልጿል።

ምን ያህል ሰው በዚህ ወጪ እንደሚቸገር አስቡት። የቢዝነስ ስራ ዋነኛ ባህርይ፣ “ችግሮችን የሚያቃልልና ወጪዎችን የሚቀንስ መፍትሄ” ማቅረብ አይደል? ይሄውና፣ የ37 አመቷ ሚቸል ክሮዝቢ፣ የፍቺ ወጪዎችን በሶስት እጅ የሚቀንስ ዘዴ በመፍጠር የቢዝነስ ስራ ጀምራለች። ጥንዶች ለፍቺ ከሃያ ሺ ዶላር በላይ ማውጣት አይኖርባቸውም። ከ7ሺ ዶላር ባነሰ ወጪ ጉዳያቸውን በድርድር ይጨርሳሉ። በዚያ ላይ ደግሞ፣ ከተጨማሪ ቂምና ጥላቻ ይድናሉ የምትለው ክሮዝቢ፣ በቢዝነሷ ስኬታማ በመሆኗ ባለፉት ጥቂት ወራት ድርጅቷ አንድ ሚሊዮን ዶላር ገቢ አግኝቷል - ፎርብስ እንደዘገበው።

መቼስ፣ ፍቺ ከተፈፀመ አይቀር፣ ወጪንና ጥላቻን የማያባብስ ዘዴ ሲገኝለት መልካም ነው። በአሜሪካ ከጊዜ ወደ ጊዜ ጋብቻና ፍቺ የሚፈፅሙ ሰዎች ከጠቅላላ የህዝብ ቁጥር ጋር ሲነፃፀሩ፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀነሱ መጥተዋል። ከሃያ አመት በፊት፣ ከአስር ሺ ሰዎች መካከል በአመት 98 ጋብቻዎች እና 47 ፍቺዎች ይፈፀሙ ነበር። ዛሬ የጋብቻዎቹ ቁጥር ወደ 68፣ የፍቺዎቹ ቁጥር ደግሞ ወደ 34 ቀንሷል። በአጠቃላይ ግን ባለፈው አመት በምድረ አሜሪካ ከ2.1 ሚሊዮን በላይ ጋብቻዎችና ወደ ዘጠኝ መቶ ሺ ገደማ ፍቺዎች ተፈፅመዋል። የአውሮፓም እንዲሁ ተመሳሳይ ነው፤ በአመት 2.2 ሚሊዮን ጋብቻዎችና አንድ ሚሊዮን ገደማ ፍቺዎች ይፈፀማሉ።

Read 3857 times