Monday, 08 April 2013 10:09

“50 አመት የሚያገለግል” የኮብልስቶን መንገድ በ2 ወር ተበላሸ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(2 votes)

አዲስ አበባ መርካቶ አካባቢ ቤሩት ሆቴል በሚባለው ስፍራ ለ50 አመት እንዲያገለግል ታስቦ በነዋሪዎች መዋጮ የተሠራው የኮብልስቶን መንገድ፣ ሁለት ወር ሳያገለግል በመበላሸቱና ሰፈሩ በመፀዳጃ ቤት ፍሳሽ በመጥለቅለቁ እንደ አዲስ እንዲገነባ ሰሞኑን ተወሰነ፡፡ አንድ ቦታ ሲበጠስ እየተመዘዘ እንደሚያልቅ “ዳንቴል” ተስፋ አስቆራጭ እየሆነ የመጣው “የኮብልስቶን” መንገድ እንዲህ በአጭር ጊዜ መበላሸቱ እንዳሳዘናቸው የገለፁ አንድ የአካባቢው ነዋሪ፣ መንገዱን ለማሰራት አስር ያህል አመታት ዝግጅት ሲደረግ እንደነበር ተናግረዋል፡፡ 200 ሜትር ያህል የሚረዝመው ይህ መንገድ፣ በ1996 ዓ.ም አስፋልት ይነጠፍበታል ከተባለ በኋላ ነዋሪው ገንዘብ ቢያዋጣም የውሃ ሽታ ሆኖ መቅረቱን የተናገሩ ነዋሪዎች፣ ለ3ኛ ጊዜ ገንዘብ ካዋጡ በኋላም መንገዱ የተሰራው በኮብል ስቶን ነው ብለዋል፡፡

ለ3ኛ ጊዜ በተሰበሰበው መዋጮ እያንዳንዱ ቤተሰብ ሁለት መቶ ብር፣ እያንዳንዱ ነጋዴ ደግሞ ሁለት ሺ ብር አዋጥቷል፡፡ አሮጌ የፍሳሽ መውረጃ ቱቦዎች እንዳልታደሱ ነዋሪዎች ገልፀው፣ እስከነጭራሹ ቱቦዎቹ ተዘግተው ኮብልስቶን ሲነጠፍበት የሽንት ቤት ቅልቅል ፍሣሽ ከዝናብ ጎርፍ ጋር እየገነፈለ አካባቢውን እያጥለቀለቀው በመሆኑ መቸገራቸውን ገልፀዋል፡፡ ሁለት መቶ ሜትር ገደማ የሚሆነው ተዳፋት መንገድ ላይ የሚገኙ ነዋሪዎች ለበሽታ እንደተጋለጡና ነጋዴዎችም ሱቃቸውን ለመዝጋት እንደተገደዱ ተናግረዋል፡፡ የወረዳው መስተዳድር የስራ ሃላፊዎች ግን በዚህ አይስማሙሙ፡፡

የተበላሹ ቱቦዎች አለመቀየራቸውን በተመለከተ ምላሽ የሰጡ የስራ ሃላፊ፣ የቱቦዎች ሁኔታ ተመዝኖ ተጨማሪ አገልግሎት መስጠት እንደሚችሉ የተረጋገጡ ቱቦዎች አልተቀየሩም፤ ጥራት የላቸውም ተብለው በባለሙያ የተመዘኑ ቱቦዎች ደግሞ በአዲስ ተተክተዋል ብለዋል፡፡ የተበላሸውን መንገድ ለማሰራት ምን እንደታሰበ የተጠየቁት የስራ ሃላፊው አሁን ያለው አማራጭ ህብረተሰቡ ኮሚቴ አዋቅሮ ገንዘብ አዋጥቶ በድጋሚ ሙሉ በሙሉ ማሠራት መቻል ነው ብለዋል፡፡ ነዋሪው ገንዘብ ካላዋጣ ተቀማጭ ገንዘብ ስለሌለ ሊሠራ እንደማይችል የተናገሩት የስራ ሃላፊው፣ ህብረተሰቡ ገንዘብ በድጋሚ አዋጥቶ የማይሰራ ከሆነ ወረዳው ከነደፋቸው ሌሎች ስራዎች ጋርበቀጣይ አብሮ የሚታይ ይሆናል ብለዋል፡፡

Read 2985 times