Saturday, 30 March 2013 14:21

ካስተማሩ አይቀር እንዲህ ነው!

Written by 
Rate this item
(0 votes)

በአዲስ ከተማ ክ/ከተማ በወረዳ 3 ዘንድሮ የተከፈተው ሐኒኮምብ አካዳሚ የተባለ (ከኬጂ እስከ 8ኛ ክፍል ድረስ የሚያስተምር) ት/ቤት ገና ከጅምሩ ያሳየው በብሩህ ተስፋና ራዕይ የተሞላ አዎንታዊ እንቅስቃሴ በእጅጉ ስለማረከኝ ነው እቺን መልዕክት ለመፃፍ የተነሳሁት፡፡ በነገራችን ላይ ልጄን ቀደም ሲል አስገብቼው ከነበረው ት/ቤት በማስወጣት ነው እዚህ አዲስ ት/ቤት ያስገባሁት፡፡ እግዜር ይስጣቸው እነሱም አላሳፈሩኝም፡፡ ልጄን በምፈልገውና በምመኘው የጥራት ደረጃ እያስተማሩልኝ ነው - ያውም በፍቅርና በሥነምግባር እየኮተኮቱ፡፡ በሌላው ት/ቤት ያላየሁት መምህራንና ወላጅ መረጃ የሚለዋወጥበት “ኮሙኒኬሽን ቡክ” በእጅጉ አስደምሞኛል - የልጄን የትምህርት አቀባበልና አጠቃላይ ሁኔታ በቀላሉ እንድከታተል አስችሎኛል፡፡ በህዳር ወር መጨረሻ ላይ ት/ቤቱ “ስፔሊንግ ቢ” የተባለ የተማሪዎች የስፔሊንግ ውድድር አካሂዶ እንደነበርም መጥቀስ እፈልጋለሁ - ት/ቤቱን ለምን እንዳደነቅሁት በቅጡ እንድትረዱልኝ፡፡

በውድድሩ የተካፈሉ ተማሪዎች አሸናፊ ለመሆን ያሳዩት እልህ አስጨራሽ የፉክክር ስሜት አስገራሚና በስሜት የሚያጥለቀልቅ ነበር፡፡ በተለይ የልጁን የትምህርት ሁኔታ በቅርበት ለሚከታተል ለእንደኔ ያለው ወላጅ! በውድድሩ 1ኛ በመውጣት ያሸነፈችው ተማሪ፤ ዋንጫ እና የአንድ አመት (ከክፍያ ነፃ) የትምህርት እድል አግኝታለች- እንደሽልማት፡፡ እንዲህ ያለው የውድድር ስሜትና ሽልማቱም ጭምር ተማሪዎቹ በትምህርታቸው ላይ እንዲተጉ ያነሳሳቸዋል የሚል እምነት ስላለኝ በእጅጉ የምደግፈውና የማበረታታው ነው፡፡ የሚገርማችሁ ደግሞ ት/ቤቱ ልጆቻችንን ብቻ አይደለም የሚያስተምርልን፡፡ እኛን ወላጆችንም ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ሁለቴ አሰልጥኖናል - ልጆችን እንዴት በፍቅር ማሳደግ እንደሚገባ፣ በትምህርታቸው ውጤታማ እንዲሆኑ ከቤት ስለምናደርግላቸው ድጋፍ እና በሌሎች ተያያዥ ርዕሰጉዳዮች ዙሪያ እነዶ/ር አቡሽን በመሳሰሉ የሞቲቬሽን አሰልጣኞች እጅግ ጠቃሚ ትምህርት ተሰጥቶናል፡፡

በመዲናችን ሲሰሙት የሚያስደነግጥ ክፍያ የሚጠይቁና “ስማቸው የከበዳቸው” አንዳንድ ቀሽም የግል ት/ቤቶች እንዳሉ እናውቃለን፡፡ ምናልባት ሐኒኮምብ ያስደነቀኝም ለዚህ ሊሆን ይችላል፡፡ በመጨረሻ ልጄን እዚህ ት/ቤት በማስገባቴ የተሰማኝን ልዩ ደስታና ኩራት በመግለፅ ለልጄ ፍቅር እየለገሱ የሚያስተምሩልኝን በሥነምግባር የታነፁ መምህራንና የት/ቤቱን አስተዳደር ላመሰግን እወዳለሁ፡፡ ሌሎችም ት/ቤቶች ከሃኒኮምብ ብዙ ሊማሩ ይችላሉ ብዬ አስባለሁ፡፡ “ካስተማሩ አይቀር እንዲህ ነው” አደራ ታዲያ ወደፊት እንጂ ወደኋላ እንዳትሄዱብን! (የተማሪ ጆሴፍ አባት)

Read 3273 times