Saturday, 23 February 2013 11:02

33ቱ ተቃዋሚዎች አብረው ለመስራት የመግባቢያ ሰነድ ይፈራረማሉ

Written by  አበባየሁ ገበያው
Rate this item
(2 votes)

የመሰብሰቢያ አዳራሽ አላገኙም

በሰላማዊ ትግል ወደ ስልጣን ለመውጣትና የመድብለ ፓርቲ ስርዓትን ለመገንባት የፓርቲዎች በጋራ መስራት ወሳኝ መሆኑን የተናገሩት የ33ቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ተወካይ አቶ አስራት ጣሴ፤ 33ቱ ፓርቲዎች በዘላቂነት አብረው ለመስራት የሚያስችላቸውን የመግባቢያ ሰነድ የፊታችን ማክሰኞ እንደሚፈራረሙ ገለፁ፡፡
ፓርቲዎቹ የመግባቢያ ሰነዱን›› ‹‹የአዳማ ፒቲሺን ፈራሚዎች አብሮ የመስራት የመግባቢያ ሰነድ›› ብለው ለመጥራት አስበዋል፡፡ ሰነዱ የፓርቲዎቹን ልዩነት በማጥበብ በጋራ ለመስራት ይጠቅማል ያሉት አቶ አስራት፤ ልዩነታችን ውበታችንና ጥንካሬያችን ነው ብለዋል፡፡ “በምርጫ ብቻ ተገናኝቶ ተቃውሞ ማሰማት እና መለያየት ብቻ ሳይሆን መዋቅራዊ ባለው መንገድ መታገል ውጤታማ ያደርጋል” ሲሉም የመግባቢያ ሰነዱን መፈራረም ያስፈለገበትን ምክንያት ተናግረዋል፡፡
28ቱ ፓርቲዎች ልዩነቶች ቢኖሯቸውም ከየፓርቲዎቹ ተውጣጥቶ የተዋቀረው ኮሚቴ በነደፈው የጋራ ስልት ላይ ወደ 13 የሚደርሱ የመግባቢያ ነጥቦች መካተታቸውን ገልፀዋል - የፓርቲዎቹ ተወካይ፡፡ የመግባቢያ ሰነዱ ማክሰኞ ይፈረማል ቢባልም በመሰብሰቢያ አዳራሽ እጦት እስካሁን ጉባኤው የት እንደሚካሄድ አልታወቀም ያሉት አቶ አስራት፤ አራት ሆቴሎች ጠይቀን ቦታ አጥተናል ብለዋል። አንድ ሆቴል ቀብድ አምጡ ብለውን ይዘን ሄደን ልንከፍል ስንል “እባካችሁ ተውን” ብለው እንደመለሷቸውና እስከ አሁን የት ይሁን የሚለውን ለመወሰን እንደተቸገሩም ይገልፃሉ፡፡

Read 3014 times Last modified on Saturday, 23 February 2013 13:03