Saturday, 09 February 2013 10:50

ካህናትና ምእመናን ዕጩ ፓትርያሪክ እንዲጠቁሙ ተጠየቀ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የስድስተኛው ፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴ÷ ካህናት እና ምእመናን ስድስተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባት ሊኾን ይገባል የሚሉትን ዕጩ በመጠቆም እንዲሳተፉ ጠየቀ፡፡ አስመራጭ ኮሚቴው፣ ስለ ስድስተኛው ፓትርያሪክ የምርጫ ሂደትና የተመረጡት ፓትርያሪክ ስለሚሾሙበት ቀን ለቤተ ክርስቲያኒቱ ካህናትና ምእመናን ግልጽ ለማድረግ ከትላንት በስቲያ በጽ/ቤቱ በሰጠው መግለጫ ባስተላለፈው ጥሪ÷ በሀገር ውስጥ ያሉ ካህናት÷ አገልጋዮች መኾናቸውን፣ ምእመናንና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ደግሞ የአጥቢያው ቤተ ክርስቲያን አባላት መኾናቸውን የሚገልጽ ደብዳቤ በመያዝ በአስመራጭ ኮሚቴው ጽ/ቤት በአካል በመቅረብ፣ ከሀገር ውጭ የሚገኙትም በፋክስ ቁጥር 011 - 1567711 እና 011-1580540 ከየካቲት 1 - 8 ቀን 2005 ዓ.ም ድረስ ዕጩአቸውን እንዲጠቁሙ ጠይቋል፡፡

አራት ሊቃነ ጳጳሳትን፣ ሁለት የጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ሓላፊዎችን፣ ሁለት የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎችን፣ አንድ የሰንበት ት/ቤት፣ አንድ የማኅበረ ቅዱሳንና ሦስት የምእመናን ተወካዮችን በአጠቃላይ 13 አስፈጻሚዎችን በአባልነት በያዘውና ታኅሣሥ 10 ቀን 2005 ዓ.ም በቅ/ሲኖዶስ በተቋቋመው አስመራጭ ኮሚቴ ወጥቶ በቋሚ ቅ/ሲኖዶሱ መጽደቁ በተገለጸው መሪ ዕቅድ እንደሚያመለክተው÷ የስድስተኛው ፓትርያሪክ ምርጫ ሂደት የሚጀምረው ለአንድ ሱባኤ/ሳምንት በሚቆይ የጸሎት ጊዜ ነው፡፡ ከትላንት የካቲት 1 ቀን እስከ የካቲት 8 ቀን 2005 ዓ.ም በሚዘልቀው በዚህ የጸሎት ሱባኤ÷ ቤተ ክርስቲያኒቱ ቅን/ርቱዕ መሪ እንድታገኝ፣ እግዚአብሔር የወደደውንና የፈቀደውን በመንበሩ ያስቀምጥ ዘንድ ካህናቷና ምእመናንዋ አምላካቸውን በጸሎት እንዲማፀኑ በዐዋጅ ታዝዘዋል፡፡በምርጫው ለመሳተፍ የሚችሉት መራጮች÷ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ሓላፊዎች፣ የጥንታውያን ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ካህናት፣ ምእመናን፣ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች እና የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ናቸው፡፡

ታኅሣሥ 8 ቀን 2005 ዓ.ም ቅ/ሲኖዶሱ ባጸደቀው የፓትርያሪክ ምርጫ ሕገ ደንብ አንቀጽ 7 ንኡስ አንቀጽ 1 - 7 ላይ በተዘረዘረው የመራጮች ማንነት÷ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በሙሉ፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ም/ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያና የድርጅት ሓላፊዎች፣ የየሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች፣ በሀገር ውስጥና በውጭ አገር የሚገኙ ገዳማት አበምኔቶች፣ እመምኔቶች እና የታላላቅ አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር ከየሀገረ ስብከቱ ሰበካ ጉባኤያት የተወከሉ አራት የካህናት፣ አራት የምእመናንና አራት የሰንበት ት/ቤት ተወካዮች ጠቅላላ ብዛታቸው ከእያንዳንዱ ሀገረ ስብከት 12 ሰዎች፣ የመንፈሳዊ ኮሌጆች መምህራንና ተማሪዎች ተወካዮች ከየኮሌጆቹ ሁለት ሁለት ሰው፣ ቤተ ክርስቲያን ሕጋዊ ዕውቅና የሰጠቻቸውና ከቤተ ክርስቲያኗ ጋራ አብረው በመሥራት ላይ የሚገኙ ማኅበራት ተወካዮች ከየማኅበራቱ አንድ አንድ ሰው እንደኾኑ ተደንግጓል፡፡

በዚህ ድንጋጌ መሠረት በስድስተኛው ፓትርያሪክ ምርጫ የሚሳተፉ መራጮች አጠቃላይ ቁጥር 800 ሲሆን ይህም ባለፉት አምስት ፓትርያሪኮች ከተሳተፉት መራጮች ብዛት ጋራ ሲነጻጸር ‹‹በእጅጉ የላቀ ነው›› ተብሏል፡፡ በሀገር ውስጥ በሚገኙት የ53ቱ አህጉረ ስብከት ሊቃነ ጳጳሳት ሰብሳቢነት በሚመራ የአስተዳደር ጉባኤ ውሳኔ የሚለዩት መራጮች ዝርዝር እስከ የካቲት 16 ቀን ለአስመራጭ ኮሚቴው እንዲላክ፣ መራጮቹም እስከ የካቲት 19 ቀን 2005 ዓ.ም አዲስ አበባ እንዲገቡ መታዘዙን የኮሚቴው መግለጫ ጠቅሷል፡፡

በፓትርያሪክ ምርጫ ሕገ ደንቡ እንደተደነገገው፣ ምርጫው ታዛቢዎች ይኖሩታል፡፡ እኒህም÷ ከአራቱ አኀት አብያተ ክርስቲያናት (ግብጽ፣ አርመን፣ ሕንድ እና ሶርያ) ከእያንዳንዳቸው አንድ አንድ ሰው፣ ከዓለም አብያተ ክርስቲያናት ማኅበር አንድ፣ ከአፍሪቃ አብያተ ክርስቲያናት ም/ቤት አንድ፣ በቋሚ ቅ/ሲኖዶስ ከቤተ ክርስቲያኗ ምእመናን የሚመረጡ ታዋቂ የአገር ሽማግሌዎች ሦስት፣ በመንግሥት የሚወከሉ ሦስት ሰዎች እንደኾኑ ተገልጧል፡፡አስመራጭ ኮሚቴው እስከ የካቲት 16 ቀን 2005 ዓ.ም በፓትርያሪክ ምርጫ ሕገ ደንብ የዕጩዎች መመዘኛ መሠረት አጣርቶ ለምርጫ የሚያቀርባቸውን ዕጩ ፓትርያሪኮች ማሳወቅ ይጠበቅበታል፤ ለምርጫ የሚቀርቡት ዕጩዎች ብዛትም አምስት ነው፡፡

ለዕጩ ፓትርያሪክነት የሚጠቆመው ሊቀ ጳጳስ፣ ጳጳስ ወይም ኤጶስ ቆጶስ÷ ዜግነቱ ኢትዮጵያዊ የኾነ፣ የውጭ አገር ዜግነት ካለውም የውጭ ዜግነቱን ሰርዞ ወደ ኢትዮጵያዊነቱ የተመለሰ፣ ዕድሜው ከ50 ዓመት ያላነሰ ከ70 ዓመት ያልበለጠ፣ ከቤተ ክርስቲያኒቱ የአብነት ትምህርቶች ቢያንስ በአንድ ጉባኤ የተመረቀ ቢቻል ሁለገብ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ያለው ኾኖ ከከፍተኛ የመንፈሳዊ ትምህርት ተቋማት ወይም በዘመናዊ ትምህርት ቢያንስ ዲፕሎማ ወይም ዲግሪ ያለው፣ ሙሉ አካል ያለውና ጤንነቱ የተሟላ፣ የቤተ ክርስቲያኗ ቋንቋ የኾነውን ግእዝን የሚያውቅ ኾኖ ቢቻል ከዓለም አቀፍ ቋንቋዎች አንዱን የሚያውቅ፣ በቅድስና ሕይወቱና በግብረ ገብነቱ የተመሰገነ፣ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት በመፈጸም በቂ የአስተዳደር ችሎታና ልምድ ያለው መኾን እንደሚገባው በፓትርያሪክ ምርጫ ሕገ ደንቡ ላይ በሰፈረው መመዘኛ ተደንግጓል፡፡ ከአምስቱ ዕጩዎች መካከል ለዕጩ ፓትርያሪክነት ይኹንታ የሚሰጣቸውን አባቶች ለመወሰን የመጨረሻ ሥልጣን ያለው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ነው፡፡ ምልአተ ጉባኤው ከየካቲት 16 ቀን ጀምሮ ተሰብስቦ ከተወያየ በኋላ የካቲት 19 ቀን 2005 ዓ.ም አምስቱን ዕጩ ፓትርያሪኮች ለሕዝቡ ይፋ እንደሚያደርግ በኮሚቴው መግለጫ ላይ ተጠቅሷል፡፡

የ፮ኛው ፓትርያሪክ ምርጫ የካቲት 21 ቀን 2005 ዓ.ም እንደሚከናወን፣ ለፓትርያሪክነት የተመረጠው አባት በዓለ ሢመት ደግሞ የካቲት 24 ቀን 2005 ዓ.ም እንደሚፈጸም ኮሚቴው ያስታወቀ ሲኾን ምርጫው ኀሙስ፣ የካቲት 21 ቀን 2005 ዓ.ም ተካሂዶ በዚሁ ዕለት ከምሽቱ 12፡00 ላይ የተመረጠው አባት በብዙኀን መገናኛ አማካይነት ለሕዝብ ይፋ እንደሚኾን ገልጧል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በራሷ ሲኖዶስ መመራት ከጀመረችበት ከ1951 ዓ.ም ወዲህ ስድስተኛ ፓትርያሪክ በመኾን ለመንበረ ተክለ ሃይማኖት የሚመረጠው አባት ሹመት (በዓለ ሢመት) የካቲት 24 ቀን 2005 ዓ.ም በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እንደሚፈጸም ኮሚቴው አስታውቋል፡፡ በዓለ ሢመተ ፕትርክናውም የሚከናወነው ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የልዩ ልዩ አብያተ ክርስቲያን መሪዎች፣ የሃይማኖት ተቋማት ተወካዮች፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ ካህናትና ምእመናን በተገኙበት እንደሚኾን በመግለጫው ላይ ተመልክቷል፡፡

Read 4473 times Last modified on Saturday, 09 February 2013 14:11