Saturday, 19 January 2013 11:59

የብሄራዊ ቡድኑ አባላት ከአዲስ አድማስ ጋር

Written by 
Rate this item
(7 votes)

በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ተሳታፊ የሚሆነው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ካሉት ጠንካራ ጎኖች አንዱ ምርጥ አጥቂዎችን መያዙ ነው፡፣ ቁልፍ ሚና ይኖራቸዋል ከሚባሉት አጥቂዎች ደግሞ የቅዱስ ጊዮርጊሱ አዳነ ግርማ እና የደደቢቱ ጌታነህ ከበደ ይገኙበታል፡፡ እነዚህ ሁለቱ አጥቂዎች ብሄራዊ ቡድኑ ለአፍሪካ ዋንጫ ዝግጅት ሲያደርግ በተቀመጠበት የኢንተርኮንትኔንታል ሆቴል በማረፊያ መኝታ ቤታቸው ጎረቤታሞች ነበሩ፡፡ ሁለቱ ተጨዋቾች ኢትዮጵያ ከ31 ዓመታት በኋላ ለአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ከሱዳን ጋር እዚህ አዲስ አበባ ጋር ባደረገችው የመልስ ጨዋታ በፈጠሩት ጥምረት ታሪክ ሰርተዋል፡፡ ጥቅምት 4 ቀን 2005 ተደርጎ በነበረው በዚሁ ታሪካዊ ፍልሚያ ኢትዮጵያ ወደ አፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ የበቃችብትን ጎል አዳና በጭንቅላቱ ከመረብ ያሳረፈው ከጌታነህ ከበደ የተሻገረለትን ክሮስ በአግባቡ በመጠቀም ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የግራ መስመር ተመላላሽ ተጨዋቾች የሆኑት የደደቢቱ ምን ያህል ተሾመ እና የስዊድኑ ሴሪናስካ ክለብ ተሰላፊ ዩሱፍ ሳላህ ደግሞ ሌሎቹ የብሄራዊ ቡድናችን ምርጦች ናቸው፡፡አሉላ ግርማንም ሁላችንም እናውቃለን፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስ እና የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ወሳኝ የቀኝ ተመላላሽ ተጨዋች ነው፡፡ ሰሞኑን ከእነዚህ አምስት የብሄራዊ ቡድን ቁልፍ ተጨዋቾች ጋር በኢንተርኮንትኔንታል ሆቴል ተገናኝቻለሁ፡፡ በርግጥ 23ቱም የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች ባነጋግር ፍላጎቴ ነበር፡፡ እንደ ዋና አሰልጣኙ ሰውነት ቢሻው አነጋገር ሁሉም ቋሚ ተሰላፊዎች፤ ወሳኝ ሚና የሚኖራቸው ኮከቦቻችን ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ በ29ኛው አፍሪካ ዋንጫ አለችበት፡፡ አዳነ፤ጌታነህ፤ ዩሱፍ፤ ምንያህልና አሉላ በዚህ ዙርያ እና በሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች አስተያት ሰጥተውኛል፡፡

ጭውውታችንን በትውልድ ስፍራ ብንጀምርስ---ጌታነህ
የተወለድኩት በዲላ ነው፡፡ ዲላ በቡና ምርቷ ትታወቃለች፡፡ አምስት ኳስ ተጨዋቾችን ለኢትዮጵያ እግር ኳስ አፍርታለች፡፡ እነ ከፍያለሁ፤ ብርሃኔ አንለይ፤ ዳንኤል ደርቤ የዲላ ልጆች ናቸው፡፡አዳነ
እኔ የተወለድኩት በሃዋሳ በምትገኘው ኮረም የተባለች ሰፈር ነው፡፡ ኮረም ብዙ ኳስ ተጨዋቾች እና ሾፌሮችን ያፈራች ሰፈር ናት፡፡ እዚያ ኮረም ሜዳ የሚባል ስፍራ አለ፡፡ ያ ሜዳ በርካታ ተጨዋቾችን ወደ ኢትዮጵያ እግር ኳስ ያመጣና ለብሄራዊ ቡድን ያበቃ ነው፡፡ እነ ሙሉጌታ ምህረት፤ ዮናታን ከበደና ሌሎችም ከዚያ ነው የወጡት፡፡ምንያህል
ተወልድጄ ያደግኩት እዚሁ አዲስ አበባ ነው፡፡ ሰፈሬም መገናኛ አካባቢ 24 ቀበሌ ነው፡፡አሉላ
ትውልዴ በ6 ኪሎ ጃንሜዳ ሰፈር ነው፡፡
ኳስ ተጨዋችነትን የጀመራችሁት በልጅነት ነው ወይስ አዋቂ ከሆናችሁ በኋላ?አዳነ
ከልጅነቴ ጀምሮ ከኳስ ጋር ነው ያደግሁት እናም ታዋቂ ኳስ ተጨዋች የመሆን ህልም ነበረኝ፡፡ ይህን ህልም ይዤ አድጌያለሁ፣ አሁን እውን ስለሆነ በጣም ደስ ይለኛል፡፡ጌታነህ
እግር ኳስ ተጨዋችነት ሙያዬ እንደሚሆን ባላስብም በሰፈር ውስጥ እየተጫወትኩ ሳድግ ፍላጎቱ የተፈጠረ ይመስለኛል፡፡ ካደግኩ በኋላ ግን ሙያዬ እንደሚሆን እርግጠኛ ነበርኩ፡፡ምንያህል
ታዳጊ ሳለሁ የፕሮጀክት ተጨዋች ነበርኩ። አንዳንዴ የብሔራዊ ቡድን ማሊያ ለልምምድ እንድለብስ ሰዎች ሲሰጡኝ አልፈልግም እላቸው ነበር፡፡ ወደፊት የራሴን መልበሴ አይቀርም ብዬ አስብ ነበር፡፡ በውስጤ ይህ እምነት ነበረኝ፡፡ አሁን እዚህ ደረጃ ደርሼ የሚያኮራ ሙያ ሆኖልኛል፡፡ አሉላ
ያደጉት በጃን ሜዳ አካባቢ ስለነበር ለስፖርቱ ቅርበት ነበረኝ፡፡ አባቴ በቀለም ትምህርት እንድገፋ ቢመክረኝም እግር ኳስን አዘውትሮ መጫወት አበዛ ነበር፡፡ በትምህርት ቤት የደረጃ ተማሪ ነበርኩ፣ በእግር ኳሱ በጣም እየገፋሁበት ስሄድ ግን ሙያዬ እንደሚሆን እያወቅሁ መጣሁ፡፡ዩሱፍ
ከልጅነቴ ጀምሮ ኳስ ተጨዋች መሆን እፈልግ ነበር፡፡ በቲቪ እያየሁ ያደግሁት ስፖርት ነው፡፡ ቤተሰቤ በተለይ አባቴ እንድማር ይፈልግ ነበር፡፡ ኳስ እንድጫወት የሚፈቀድልኝ በትምህርቴ ስበረታ ብቻ ነበር፡፡ በኋላ ግን በስዊድን ፕሮፌሽናል ሊግ ውስጥ ገብቼ አሁን ላለሁበት ደረጃ በቅቻለሁ፡፡ እናም የምከበርበት ሙያ ሆኖልኛል። ማንም እግር ኳስ ተጨዋች ትልቁ ዓላማው በብሔራዊ ቡድን ውስጥ መጫወት ነው፡፡ እኔም በስዊድን ወጣት ብሔራዊ ቡድን ውስጥ ተጫውቻለሁ፡፡
ወደ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ስገባ ከፍተኛ ደስታ ተሰምቶኛል፡፡ አሁን ደግሞ የመጀመርያው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ልሳተፍ ነው፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የገባሁበትን የመጀመሪያ አጋጣሚ የፈጠረው አሰልጣኝ ስዩም ከበደ ነው፡፡ በኢሜልና በስልክ ባደረግነው ግንኙነት በምጫወትበት ክለብ ውስጥ ያለኝን ብቃት የሚያሳዩ የቪዲዮ ምስሎች እንድልክለት ስዩም ጠየቀኝ፡፡ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ፊልሞችን መመልከት እንደሚፈልግ ነገረኝ፡፡ በምጫወትበት የስዊድን ክለብ ሴሪናስካ ዘንድሮ እና ባለፈው የውድድር ዘመን ያደረግኋቸውን ጨዋታዎች የሚያሳዩ ፊልሞች ላኩኝ፡፡ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ፊልሞቹን ተመልክተው ወደ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በመቀላቀል ልሠራ እንደምችል በስልክ ነገሩኝ፡፡ በዚህ መንገድ ብሔራዊ ቡድኑን ለመቀላቀል ችያለሁ፡፡
ብሄራዊ ቡድኑ ለአፍሪካ ዋንጫ ካለፈ በኋላ ያገኛችሁት አጠቃላይ የገንዘብ ሽልማት ስንት ደረሰ?አዳነ
355ሺ ብር
ጌታነህ
335ሺ
ምንያህል
300ሺ ብር
አሉላ
350ሺ ብር
ከትልቅ ጨዋታ በፊት በየትኛውም ቡድን ውስጥ ተጨዋቾች መጨነቅና መወጠራቸው አይቀርም፡፡ ከሱዳን ጋር ወደ አፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ በተደረገው የመጨረሻው ፍልሚያ የብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች መብላትና መተኛት ሁሉ ተቸግረው ነበር ይባላል፡፡ አሁን ደግሞ ከ31 ዓመታት በኋላ ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ዋንጫ አልፋለች፡፡ የሚያጨናንቅ ነገር አለ?አዳነ
በሱዳኑ ጨዋታ እንቅልፍ ማጣታችንንና መጨነቃችንን የተናገርነው ከ31 ዓመታት በኋላ ኢትዮጵያ ወደ አፍሪካ ዋንጫ የምታልፍበት ወሳኝና የመጨረሻ ምእራፍ ላይ ደርሰን ስለነበር ነው፡፡ ታሪክ መስራት፤ ህዝባችንን ማስደሰት፤የሚሉትን ማሰብ ያስጨንቃል። አሁን ግን በከፍተኛ የራስ መተማመን ውስጥ ነው ያለነው። አንዴ ማለፋችንን ስላረጋገጥን ምንም አይነት ጭንቀት እና ጫና የለብንም፡፡ እንደውም ጫናው ለእነ ዛምቢያ ነው የሚሆነው፡፡ እኔ በበኩሌ አልጨናነቅም፡፡ ዛምቢያ አሁን ሻምፒዮናነቷን ለማስጠበቅ ትጨናነቃለች። እኛ ግን ማንም አያውቀንም፡፡ አለመታወቃችን ጭንቀት የሚፈጥረው በምድቡ ተቀናቃኞች ላይ ነው፡፡ጌታነህ
ከ31 ዓመታት በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫ ኢትዮጵያን የምናሳልፍበት እድል በፈጠረው ፍልሚያ የነበረው ጭንቀት የተፈጠረው ቅድም አዳነ በዘረዘራቸው ምክንያቶች ነው፡፡ የተለየ የምጨምረው ቢኖር በወቅቱ ባይሳካልንስ ብለን መስጋታችንን ነው፡፡ ከጨዋታ በፊት በየሚዲያው "የመጨረሻው እድላቸው" ተብሎ መነገሩም ያስጨንቅ ነበር፡፡ አሁን ግን በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ መሳተፋችን በመረጋገጡ በምድብ የምናደርገው ውድድር ስለሆነ ብዙም የሚያስጨንቅ ነገር አለ ብዬ አላስብም፡፡ምንያህል
አሁን እየገባን ያለው ወደ አህጉራዊ ውድድር ነው። ባለፈው በሱዳን ጨዋታ ጭንቀት የተፈጠረብን ወደዚህ የውድድር ምዕራፍ ለመሸጋገር ወሳኝ ፍልሚያ ላይ በመድረሳችን ነበር፡፡ ወደ ታላቅ ምዕራፍ ለመሸጋገር ዋዜማ ላይ ስለነበርን ነው ከፍተኛ ጫና የተፈጠረብን፡፡ አሁን ስለአፍሪካ ዋንጫ ለማውራት የበቃነው ያንን ወሳኝ ፍልሚያ አልፈን ነው፡፡
በምድብ 3 የመክፈቻ ጨዋታ ስለምትገጥሟት ሻምፒዮኗ ዛምቢያ ወቅታዊ የአቋም ሁኔታ ምን መረጃ አላችሁ?አዳነ
ከፍተኛ ትኩረት የሰጠነው ካለፈው የአፍሪካ ሻምፒዮን ዛምቢያ ጋር የምናደርገው የምድቡ መክፈቻ ጨዋታን ነው፡፡ ሁላችንም እንደተከታተልነው ዛምቢያ በወዳጅነት ጨዋታዎች ተከታታይ ሽንፈት ስላጋጠማት በጥሩ አቋም ትገኛለች ለማለት ያጠራጥራል፡፡ በአንፃሩ የኛ ዝግጅት የተሳካ ነው፡፡ ሁለት የወዳጅነት ጨዋታዎች አሸንፈናል፡፡ በአንዱ አቻ ወጥተናል፡፡ በተለይ ከአፍሪካ ኃያል ቡድኖች አንዷ ከምትባለው ቱኒዚያ ጋር አቻ የወጣንበት ሁኔታ ጥንካሬያችንን ያጎላዋል፡፡ ከዚህ አንፃር የምድብ 3 የመክፈቻ ጨዋታ ከእኛ ይልቅ ፈታኝ የሚሆነው ለዛምቢያ ይመስለኛል፡፡ እነሱ ተሸብረው ይገባሉ። እኛ ግን ከዚህ በፊት ከሚያውቁን የተሻለ ጥንካሬ ይዘን እንገጥማቸዋለን፡፡
አዳነ እና ጌታነህ ሁለታችሁም የዋልያዎቹ ወሳኝ አጥቂዎች እንደመሆናችሁ አንድ የታዘብኩትን ሁኔታ እንዴት እንደምታዩት ማወቅ እፈልጋለሁ፡፡ ከ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ አራት ምድቦች መካከል ምድብ 3 በጥንካሬው ብቻ ሳይሆን በርካታ ምርጥ አጥቂዎች የተሰባሰቡበት ሆኖ ይለያል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የአጥቂ መስመር ከመቸውም ጊዜ በላቀ ሁኔታ በምርጥ ስብስብ የተዋቀረ ይመስለኛል፡፡ የናይጄርያ ብሄራዊ ቡድንም የአፍሪካ ዋንጫውን ምርጥ አጥቂዎች በመያዝ የሚጠቀስ ነው፡፡ በዛምቢያም ቢሆን አንዱ ልዩ ጥንካሬ የአጥቂ መስመሩ ነው፡፡ በፈረንሳይ ሊግ ምርጥ የተባሉ አጥቂዎችን የያዘውና ከፍተኛ ልምድ ያላቸው የፊት መስመር ተሰላፊዎችን ያካተተው የቡርኪናፋሶ ቡድንም የሚናቅ አይሆንም። ይህን የምድብ 3 የአጥቂዎች መብዛት እንዴት ታነፃፅሩታላችሁ?ጌታነህ
ብዙ የማውቃቸው የናይጄርያ አጥቂዎችን ቢሆንም አንዳንድ የዛምቢያ አጥቂዎችንም አውቃለሁ፡፡ ይሁንና የእኛ ቡድንም በአጥቂዎቹ ብዙ የሚተናነስ አይደለም። የቡድናችን ሁላችንም አጥቂዎች ጠንካሮች ነን፡፡ በየጨዋታው ሁሉም አጥቂዎች ጎል እያገባን ቆይተናል። አንዳችን ገብተን ጎል ማስቆጠር ቢያዳግተን ተቀይረን በመግባት ጎል እያገባን እየወጣን ነው፡፡ አጥቂ ሆነህ ሜዳ ስትገባ ጎል ማግባት አለብህ። በእኛ ቡድን ያሉ አጥቂዎች ጥንካሬም ይህንኑ ሃላፊነት በአግባቡ እየተወጣ ነው። ሁላችንም ወደ ሜዳ የምንግባው በአንድ ሆነ በሌላ አጋጣሚ ጎል ለማስቆጠር እምነትና ጥንካሬ ይዘን ነው፡፡
አዳነ
ከዚህ በፈት የነበሩ የብሄራዊ ቡድን አጥቂዎች ጎል የማግባት ችግር ነበረባቸው፡፡ አሁን ያለን አጥቂዎች ግን ለውጤት የሚያበቁ ወሳኝ ጎሎችን በሜዳችን ሆነ ከሜዳ ውጭ ለማስቆጠር ብዙ ችግር የለብንም፡፡ የሁላችንም ወቅታዊ ብቃት ይህን ለማለት የሚያስተማምን ይመስለኛል፡፡ ቡድናችን ድሮ ከሜዳ ውጭ አያገባም ነበር፡፡ ያ ነገር አሁን ባለው የአጥቂ ትውልድ ተሰብሯል፡፡ ለዚህም ነው በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ጎል ለማግባት ብቃቱ እንዳለን በእርግጠኝነት ነው የምናገረው። በወዳጅነት ጨዋታዎቹ እንደታየውም በርካታ የግብ ሙከራዎችንም እናደርጋለን፡፡ በቡድናችን ኢላማውን የጠበቀ ሙከራ የማድረግ ብቃት እና ጥንካሬ ያላቸው አጥቂዎች መኖራቸውን ማንም አይክደውም፡፡ ስለሆነም በተቃራኒ ቡድኖች ስላለው የአጥቂ መስመር ጥንካሬ ብዙ ማሰብ አልፈልግም፡፡ የኢትዮጵያ አጥቂዎች ጥንካሬ በአፍሪካ ዋንጫው ማጣርያ ብቻ ሳይሆን በዓለም ዋንጫው ማጣርያ ሲታይ የቆየ በመሆኑ ይህ ጥንካሬ አሁንም በአፍሪካ ዋንጫው ቀጥሎ ለውጤት እንደሚያበቃን ነው ተስፋ የማደርገው፡፡
እንግዲህ የአፍሪካ ዋንጫን ለየት ከሚያደርጉት ባህርያት መካከል ጎል ከገባ በኋላ በየቡድኖቹ ተጨዋቾች የሚታየው የደስታ አገላለፅ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ጐል ሲያገባ ደስታውን እንዴት ለመግለፅ ታስቧል?አዳነ
እንደ ብዙ የአፍሪካ አገራት ኢትዮጵያም ብዙ ባህል ያላት አገር ናት እና መልካም ገፅታዋንና እና ባህሏን የሚያስተዋውቅ የደስታ አገላለፅ ለማድረግ እንሞክራለን። በዚህ ታላቅ መድረክ ጎል በማግባት የሚፈጠረውን አጋጣሚ ማንነታችንና አገራችንን ለማስተዋወቅ ብንችል ደስ ይለናል፡፡ ሁሉም ይህን ያስባል ብዬ እገምታለሁ፡፡ በቡድን ደረጃ እንዲህ አይነት የጎል ደስታ አገላለፅ እንስራ ብለን የመከርነው ነገር የለም፡፡ ግን ቀላል ነገር ነው። በየጨዋታው መግቢያ ላይ ተመካክረን የምናደርገው ነው፡፡ጌታነህ
ልክ ነው ከወዲሁ የተዘጋጅንበት ነገር የለም፡፡ እኔ ግን የማስበው ጎል ያገባው ተጨዋች የሚያሳየውን ደስታ አገላለፅ በመከተል የምንፈልገውን ጭፈራ የምናሳይ ይመስለኛል፡፡ አሁን አዳነ አግብቶ ኦሮምኛ ቢጨፍር እሱን አጅበን ነው ኦሮምኛ የምንጨፍረው። ጎል አግቢው ያሳየውን የደስታ አገላለፅ ሁላችንም የቡድኑ አባላት በደስታ የምንጋራው ይመስለኛል፡፡ አስቀድመን ብንዘጋጅም ባንዘጋጅም በአንድ መንፈስ ማራኪ ደስታ አገላለፅ እንደምናሳይ አውቃለሁ፡፡
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በተለይ ባለፉት ሁለት ዓመታት ስኬታማ እየሆነ መጥቷል፡፡ የዚህ ልዩ ብቃት ምስጢር ምንድነው? የቀድሞዎቹ ቡድኖች ግብ አያስቆጥሩም ነበር፤ ከሜዳ ውጭ ማሸነፍም ሆነ ነጥብ መጋራት በጣም ሲከብዳቸው ቆይቷል። አሁን ግን ከሜዳ ውጭ ግብ ማስቆጠርና ነጥብ ይዞ መውጣት እየተለመደ ነው፡፡ አስቀድሞ ቢገባም ከኋላ ተነስቶ ግብ በማስቆጠር ውጤት ማስጠበቅ እየተቻለ ነው። ይህ አይነቱ ስኬት በአጋጣሚ የሚገኝ አይደለም፡፡ ለሚታዩት ለውጦች አበይት ምክንያቶች ምንድን ናቸው?አዳነ
የመጀምሪያው ምክንያት ይህን ቡድን ለረጅም ጊዜ ሲያሰለጥን የቆየው አንድ አሰልጣኝ መሆኑ ነው። ከዚህ በፊት እንደሚታወቀው የብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ በየጊዜው ይቀያየራል፡፡ ይህም ቋሚ ቡድን ለመስራት የሚያመች አልነበረም፡፡ የአሰልጣኞች መቀያየር በየጊዜው በአዳዲስ ልጆች ወጥ አቋም ሊኖረው የማይችል ቡድን መስራትን ያስገድዳል፡፡ ይህ ደግሞ የውጤት እንቅፋት ነው፡፡ አሁን ያለው ብሄራዊ ቡድን ለሁለት ዓመታት በአንድ አሰልጣኝ ሲገነባ እና ሲሰለጥን የቆየ ነው። ብዙዎቻችን አንድ ላይ ሆነን እሰከ 10 ጨዋታዎች አድርገናል። ይሄ ሁኔታ የቡድኑ ተጨዋቾች አብረን በመስራት ለረጅም ጊዜ እንድንቆይ ከማድረጉም በላይ፣ ከፍተኛ መግባባት እና መተዋወቅ ፈጥሮልናል፡፡ ጥሩ እና አሳማኝ ብቃት ያላቸው አዳዲስ ተጨዋቾች በየጊዜው ወደ ብሄራዊ ቡድኑ ይገባሉ፡፡ በየጨዋታው አዲስ ቡድን አዲስ ስብስብ እየተሰራ አልነበረም፡፡ ለየትኛው ቡድን ውጤታማነት ይሄ አይነቱ የቡድን መዋቅር እጅግ ወሳኝ ሚና ይኖረዋል፡፡ጌታነህ
በአዳነ አስተያየት ላይ የምጨምረው ቢኖር ባለፈው አንድ አመት ተጨዋቾችን በየጊዜው መቀያየር እና ቡድን ማፍረስ አልነበረም፡፡ ይህ ቡድን አዲስ ተጨዋች ቢጨመርበት እንጅ ባለፉት 10 ጨዋታዎች ቋሚ ልጆች አብረን ቆይተናል፡፡ ከዚህ ቀደም በየጊዜው አሰልጣኝ ሲቀያየር፤ ወደ ብሄራዊ ቡድን የሚመጣው አዳዲስ ስብስብ ችግር ነበረው፡፡አዳነ
የአመጋገብና የስነልቦና ባለሙያዎች ከቡድኑ ጋር መስራታቸውም ሌላ ለውጥ ነው፡፡ እነዚህ ሁሉ ሁኔታዎች በቡድኑ የተሰባሰቡ ተጨዋቾች በሁሉም ረገድ ተዋህደው እና ተግባብተው በአላማ እንዲሰሩ ምክንያት ነበር። የትኛውም የቡድን ተጨዋች ከሌላ የቡድን አጋሩ ጋር የመግባባት ችግር የለበትም፡፡ በሜዳ ላይም ሆነ ከሜዳ ውጭ ባለ ብቃት እና ባህርይ የሚጣጣም እና የሚግባባ ነው፡፡ አሁን በብሄራዊ ቡድን ያለው የተጨዋቾች ስብስብ ተበትኖ አንድ ሳምንት ልምምድ ሳይሰራ ቆይቶ በድጋሚ ቢሰባሰብ በቀላሉ ተቀናጅቶ ለመስራት አይከብደውም፡፡የብሄራዊ  አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች ብሄራዊ ቡድኑ ለአፍሪካ ዋንጫ ያለፈው በተደረገው የማጣርያ ድልድል በተፈጠረለት ምቹ እድል ነው ይላሉ፡፡ የተወሰኑ ደግሞ ስኬቱን ተዓምር ያደርጉታል፡፡ ለዚህ አፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ወሳኝ አጋጣሚ የምትሉት ምንድነው? አዳነ
በአፍሪካ ዋንጫው ማጣርያ በተለይ ከሜዳ ውጭ ከቤኒን ጋር ተጋጥመን በአቻ ውጤት ነጥብ ተጋርተን ስንወጣ ወሳኙ አጋጣሚ ተፈጥሯል ብዬ አምናለሁ። ከቤኒን ጋር እዚህ በሜዳችን 0ለ0 ወጥተን፣ በመልስ ጨዋታ ወደዚያ አቅንተን ከሜዳችን ውጭ፤ በሌሎች ደጋፊዎች ጩኸት ተከበን የተጫወትን ሲሆን፣ አንድ እኩል በመውጣት ወደ ቀጣይ የማጣርያ ምእራፍ ያለፍነው ከፍተኛ መስዕዋትነት ከፍለን ነው፡፡ጌታነህ
በማጣርያው ያደረግናቸው ጨዋታዎች በሁለት ምእራፍ የተደረጉ ቢሆንም አራት ጨዋታዎች አድርገናል። ይህ ማለት እንግዲህ ማጣርያው በምድብ የተዘጋጀ ቢሆን የቀረን ተጋጣሚ አንድ አገር ብቻ ብቻ መሆኑ ነው፡፡ በምድብ ማጣርያ ሦስት፤ በሜዳችን ሶስት ከሜዳ ውጭ ሦስት በአጠቃላይ ስድስት ጨዋታዎች ነበር የሚደረገው። በሁለት ዙር በተካፈልነው ማጣርያ ያደረግነው ሁለት በሜዳችን ሁለት ደግሞ ከሜዳ ውጭ አራት ጨዋታዎች ነው፡፡ ስለዚህ የማጣርያው አይነት ብዙም እድል የሚፈጥር አለመሆኑን መረዳት ያስፈልጋል።አሉላ
ለአፍሪካ ዋንጫ ያለፈው ብሔራዊ ቡድን እንደ ቤተሰብ የተጠናከረ የቡድን ስብስብ አለው። ውጤታችን የህብረት ነው፡፡ በአገር ፍቅር መንፈስ የተገኘ ነው። በስነልቦናና በስነምግብ የነበረን አጠቃላይ ዝግጅትና አደረጃጀት ከፍተኛ ኃላፊነት ውስጥ ከቶን ነበር። ብሔራዊ ቡድኑ በከፍተኛ ልምምድ ነው ተገቢውን ብቃትና ጥንካሬ ሊያገኝ የቻለው፡፡
የአትዮጵያ እግር ኳስ ለበርካታ አመታት በፌደሬሽን ውዝግብ በአገር ውስጥ ሊግ አለመጠናከር እና በተለያዩ ምክንያቶች ተዳክሞ ቆይቷል፡፡ በእግር ኳሱ ዛሬ ለተከፈተው አዲስ የለውጥ እና የእድገት ምእራፍ በር ከፋች የሆኑ ክስተቶች እና ምክንያቶችን ልትነግሩኝ ትችላላችሁ?አዳነ
ካለፉት አምስት አመታት ወዲህ ለውጦች እየተፈጠሩ መጥተዋል፡፡ በተለይ አስቀድሞ የነበረው የፊርማ ክፍያ 35 ሺ ነበር፡፡ በ2000 ዓም እኔ ወደ ጊዮርጊስ ስገባ ወደ 70ሺ ብር አደገ፡፡ ይህ ብሩህ ተስፋ ነበር፡፡ ለብዙ ተጨዋቾች መነሳሳትም ምክንያት ሆኗል፡፡ አሁን የፊርማ ክፍያ በአማካይ እስከ 400ሺ ብር ነው፡፡ ከፍተኛው እስከ 800ሺ ብር ደርሷል። ተጨዋቾች ጠንክሮ ለመስራት ይሄ ጥቅም በቂ ምክንያት ይሆናቸዋል፡፡ጌታነህ
ከጊዮርጊስ ክለብ ባሻገር የፊርማ ክፍያ በሌሎች ክለቦች ባለሃብቶች ትኩረት ተሰጥቶት ይሰራበት መጀመሩም ሌላው የለውጥ በር ከፋች ይመስለኛል። አሁን እኔ በደደቢት ክለብ በ75ሺ ብር ፊርማ ስገባ የባለሃብቶች ትኩረት ወደሌሎች ክለቦች መስፋፋቱን ያሳየ ነበር፡፡ በደደቢት ክለብ ለተጨዋቾች ብቃት ማደግ ይሄው የፊርማ ክፍያ ከፍተኛ መነሳሳት እየፈጠረ ነው። ሁላችንም ተጨዋቾች ጠንክረን የምንሰራው ነገ ደህና የፊርማ ብር በማግኘት ለመጠቀም ነው፡፡ በብዙ ክለቦች የተጨዋቾች ደሞዝ እኩል ነው፡፡ የሚለያየን የፊርማው ክፍያ ነው፡፡አሉላ
እግር ኳስ ከኢኮኖሚ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ በአገራችን እግር ኳስ የመዕለ ንዋይ ፍሰት እየጨመረ መምጣቱ እየታየ ላለው ለውጥና እድገት ጉልህ አስተዋጽኦ አበርክቷል፡፡ የአውሮፓ እግር ኳስ ከፍተኛ ደረጃ የደረሰው በገንዘብ አቅም ነው፡፡ የዚህ ዘመን ተጨዋቾች በእግር ኳስ ከፍተኛ ስኬት እያገኛችሁ ነው፡፡ ስኬታማነት አድናቆት እና ዝና ያመጣል፡፡ ዝነኛ መሆን ደግሞ አንዳንዴ ያዘናጋል፡፡ አዳነ
ስኬታማ ሲሆኑ አድናቆት እንደሚኖር ሁሉ፤ ስኬታማ ባለመሆንም ትችት ያጋጥማል። ስለሆነም አድናቆት ለእኔ ብዙ አይገርመኝም፡፡ አድናቆቱንም ትችቱንም ተላምጄዋለሁ፡፡ አድናቆት የሚያዘናጋ አይመስለኝም፡፡ ያው እንደምታውቀው የምጫወትበት ቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ብዙ ደጋፊ ያለው ነው፡፡ አንዳንዴ በጨዋታ ላይ ሃትሪክ ስሠራ ከፍተኛ አድናቆት አገኛለሁ። ደጋፊዎች ያለናንተ ሰው የለም ሁሉ ይሉናል፡፡ በጨዋታ ላይ ደጋፊዎች ስሜን እየጠሩ ሲያወድሱኝ በውስጤ ጥሩ ስሜት ይፈጥራል። ግን አልኮፈስበትም፡፡ የደጋፊ ባህርይ ነገ ጥሩ ካልሆንክ ደግሞ ወደ ስድብ ይቀየራል፡፡ በርግጥ ለምን ተሰደብኩ ብዬ አልናደድም፡፡ ደጋፊዎች በብቃቴ ጥሩ አለመሆን ተበሳጭተው የፈለገውን ቢሰድቡኝ ምንም አይመስለኝም፡፡ ቤተሰቤን ሲነኩ ግን ደስ አይለኝም፡፡
እግር ኳስ ስሜታዊ ያደርጋል፡፡ በስሜት የምትሳደበውና የምትተቸው ደግሞ ጥላቻ ነው ብዬ አላስብም፡፡ አሉላ
አሁን የደረስንበት ደረጃ ላይ ለመድረስ ብዙ መስዋዕትነት ከፍለናል፡፡ ያገኘነው ስኬት ደግሞ ብዙ አድናቆት አትርፎልናል፡፡ ምንያህል
ከታዳጊነቴ ጀምሮ በርካታ ድጋፍ ባለው የቡና ክለብ መጫወቴ ከአድናቆት ጋር አላምዶኛል፡፡ አድናቆት ኃላፊነትን ይጨምራል፡፡ በምትሠራው፣ በምታደርገው ሁሉ ጥንቁቅ ያደርግሃል፡፡ አድናቆት ክብር ያመጣል፡፡ እናም በክብር እንቀበለዋለን፡፡ ዩሱፍ
የኢትዮጵያ ህዝብ ድጋፍ በጣም ደስ የሚል ነው። በደቡብ አፍሪካም ብዙ ድጋፍ እንደሚጠብቀን አውቃለሁ፡፡ አድናቆት ለተሻለ ውጤት ያነሳሳል፤ ትበረታታለህ፡፡ በጣም ደስ ይልሃል፡፡ የተሻለ ትሠራለህ። በሙያህ አድናቆት እንዲኖርህ ትፈልጋለህ፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድኑን በተሳካ ሁኔታ ለመቀላቀል በመቻሌ የክለቤ ኃላፊዎች፣ የቡድን አጋሮቼ እና በስዊድን ያሉ ቤተሰቦቼ እጅግ በጣም ተደስተዋል፡፡ እርግጠኛ ነኝ፣ ብዙዎቹ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተሰልፌ በደቡብ አፍሪካ በሚደረገው 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ስሳተፍ በትኩረት ሁሉንም ይከታተላሉ፡፡
እንግዲህ የኢትዮጵያ ህዝብ ስፖርት አፍቃሪ ነው። ባለፉት 30 ዓመታት አትሌቶች በኦሎምፒክና በዓለም ሻምፒዮና መድረክ ባስመዘገቡት ውጤቶች ሲኮራና ሲደሰት ኖሯል፡፡ አሁን የእናንተ ትውልድ ለአፍሪካ ዋንጫ ካለፈ በኋላ በእግር ኳሱ እያበደ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ተወዳጅ ስፖርት እግር ኳስ ነው አትሌቲክስ?ጌታነህ
ለኢትዮጵያ ህዝብ ተወዳጁ ስፖርት እግር ኳስ ነው የሚመስለኝ፡፡ ለአፍሪካ ዋንጫ ባለፍን ወቅት በመላው አገሪቱ ህዝቡ አደባባይ ወጥቶ ደስታውን የገለፀበትን ሁኔታ ስትመለከት ይህን ለማለት ያስደፍርሃል፡፡ አዳነ
እግር ኳስ የስፖርቶች ንጉስ ነው፡፡ ለምን ብትለኝ እግር ኳስ የቡድን ስራን መሠረት አድርጐ ውጤት የሚገኝበት መሆኑ ተወዳጅ ያደርገዋል፡፡ ሩጫ ብዙውን ጊዜ የአንድ ሰው ጥረት የሚታይበት ነው፡፡ እግር ኳስ የ90 ደቂቃ ልፋት፣ የህብረት ትግል የሚታይበት ነው፡፡ የፉክክር ደረጃውም ከፍተኛ መዝናናት የሚፈጥር ስለሆነ እግር ኳስ ከሩጫ ይልቅ ተወዳጅ ይመስለናል፡፡ ዮሴፍ
በልቤ እግር ኳስ የማስበልጥ ቢሆንም ለኢትዮጵያውያን አትሌቲክስ ኩራት መሆኑን አውቃለሁ፡፡ እግር ኳስ ግን እጅግ ግዙፍና ትልቅ ስፖርት ነው፡፡ ምን ያህል
የህዝቡን ቀልብ የሚስበው እግር ኳስ ነው፡፡ በፊት በውጤቱ አለመኖር ፍቅሩ ቀንሶ ሊሆን ይችላል። አሁን የተገኘው ስኬት የኢትዮጵያ ህዝብ ለእግር ኳስ ፍቅር የተገዛ መሆኑን አስመስክሯል፡፡ እግር ኳስ ቅጽበታዊ ውሳኔን የሚጠይቅ፣ ከፍተኛ የፉክክር ደረጃ ያለው መሆኑ ልዩ ስፖርት ያደርገዋል፡፡
እስቲ በቅጽል ስያሜዎች ዙሪ እናውራ፡፡ የብሔራዊ ቡድን ተጨዋቾች ልዩ ልዩ ቅጽል ስሞች አላቸው፡፡ አሁን አዳነ አዴ፣ ወፍጮ ይሉሃል፣ ጌታነህስ ማን ብለው ነው የሚጠሩህ? አዳነ
ወፍጮ ብለው የሚጠሩኝ ደጋፊዎች ምን ማለታቸው እንደሆነ ከሌላ ነገር ጋር የሚያያዙት አሉ፡፡ እኔ ግን እንደስድብ የሚቆጠር ቅጽል ስያሜ ቢሆን እንኳን ምንም አይመስለኝም፡፡ አሁን የቡና ደጋፊዎች ወፍጮ ብለው እየጠሩ ሊሰድቡኝ ሲሞክሩ የሚገርምህ እልህ ውስጥ ገብቼ ከፍተኛ ውጤት ለማግኘት እነሳሳለሁ፡፡ ጌታነህ
አሁን አዳነን ወፍጮ ሲሉት ብዙ ምግብ ይበላል ከማለት ጋር የሚያያዙት ይኖራሉ፡፡ ይህ ስም የወጣለት ግን በሜዳ ላይ ሲጫወት በነበረው ሚና ነው፡፡ በአንድ ጨዋታ ላይ አዳነ ተሰልፎ የተቃራኒ ቡድን ተጨዋቾችን እየተጋፈጠና እየተጋጨ ሲጫወት ተመልክተው ነው አሰልጣ ሰውነት ይሄን ስም ያወጡለት፡፡ ስላደነቁት የወጣ ቅጽል ስም መሆኑ መታወቅ ይኖርበታል፡፡ ለነገሩ አዳነ ለብዙ የቡድን ተጨዋቾች ቅጽል ስም በማውጣትም ይታወቃል፡፡ እኔን አሁን ገዬ ነው የሚለኝ፡፡ አዳነ
በቅጽል ስም ሰው የምጠራው ሙሉ ስም መያዝ ልማዴ አልሆን ብሎ ነው፡፡ በተለይ በጨዋታ ላይ ከቡድን አጋሮቼ ጋር ለመግባባት እዚያው የመጣልኝን አጠራር እጠቀማለሁ፡፡ የቡድን ልጆች ይህን አጠራሬን ሰምተው ያፀድቁታል፡፡ አሁን ጌታነህን ኳስ እንዲያቀብለኝ ስፈልግ ጌታነህ ብዬ ከምጠራው የመጀመሪያውን ፊደል "ገ" እና ለማቆላመጥ "ዬን" ጨምሬ ገዬ ብዬ እጠራዋለሁ፡፡ ለአንዳንዶቹ ደግሞ ከአጨዋወታቸው እና ከድርጊታቸው ተነስቼ ስም አወጣላቸዋለሁ፡፡ አሁን አምበላችንን ደጉን "ስለ"ብዬ የምጠራው፡፡ ዩሱፍ
ብሄራዊ ቡድኑን ከተቀላቀልኩ በኋላ ሜዳ ላይ ብቻዬን ኳስ ሳንጠባጥብ አሰልጣኙ ተመልክተው በቃ የውጭ አገር ሰው መሆንህ ቀርቷል፡፡ አሁን አበሻ፣ እንደውም ጐንደሬ ሆነሃል አሉኝ፡፡ ይህንኑ ተቀብሎ ተጨዋቹ ሁሉ "ጐንደሬ" ይለኝ ጀመር፡፡ የቡድን አጋሮቼ በዚያ ሲጠሩኝ ደስ የሚላቸው ከሆነ ብዬ ተቀብዬዋለሁ፡፡ በስዊድን ስጫወት በአባቴ ስም ሳላህ ብለው ይጠሩኛል ፡፡ ምን ያህል
በክለብ ደረጃ መጫወት ስጀምር እናትና አባቴ ባወጡልኝ ስም ነበር የምጠራው፡፡ ድሮ ከሰፈር ጀምሮ ግን የወጣልኝ የቅጽል ስም ቤቢ ነው፡፡ አሁን ከፍተኛ ዕውቅና ካገኘሁ በኋላ ዋናው ስሜ ምንያህል መታወቅ ጀመረ እንጂ ብዙ ሰው ቤቢ እያለ ነው የሚጠራኝ፡፡ በቅጽል ስም መጠራራት ያዝናናል፡፡
ባለፈው ሰሞን እውቁ የአርሰናል አሰልጣኝ አርሴን ቬንገር ስለአፍሪካ ዋንጫ ተጠይቀው ባልተጠበቀ ሁኔታ ኢትዮጵያን ጠቅለዋል፡፡ በዘንድሮ የአፍሪካ ዋንጫ ኢትዮጵያ አለችበት፣ ግን ከኢትዮጵያ ቡድን የአምስት ተጨዋቾችን ስም ማንም አያውቅም ብለዋል፡፡ ከዚሁ የቬንገር አስተያየት ጋር ተያይዘው በወጡ ዘገባዎች፣ ኢትዮጵያ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ የምትሳትፈው ለዓለምና ለቬንገር ማንነቷን ለማሳወቅ ነው ብለዋል፡፡ እኔ በበኩሌ የቬንገር አስተያየት የብዙ አሰልጣኞች፣ የእግር ኳስ መልማዮችና የዝውውር ደላሎችን ቀልብ የሚስብ የዝውውር ጥሪ ይመስለኛል፡፡ እናንተስ?አዳነ
የቬንገር ንግግር ያለምክንያት አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ የሚታወቅ ምንም ፕሮፌሽናል ተጨዋች ስለሌላት ይመስለናል፡፡ እኛ እግር ኳስ ሙያችን አድርገን የምንጫወት ፕሮፌሽናሎች ብንሆንም የምንወዳደርበት ፕሮፌሽናል ሊግ አለመኖሩ ዕውቅናችንን ቀንሶታል። ብዙውን ጊዜ ግን በእግር ኳስ ዙሪያ ያሉ ባለሙያዎች ለሚታወቁ ተጨዋቾችና ቡድኖች ትኩረት ከመስጠት ይልቅ አዲስ መጤ ለሆኑት ይጓጓሉ፡፡ ለዚህም ይመስለኛል ቬንገር ኢትዮጵያን በተለይ ሊጠቅሱ የቻሉት፡፡ እነ ጋና፣ ናይጀሪያ ይታወቃሉ ታይተዋል፡፡ ኢትዮጵያን ግን ማንም አያውቃትም፡፡ ቬንገር ብቻ ሳይሆኑ ብዙዎች እኛ ላይ ትኩረት ያደርጉብናል፡፡ ጌታነህ
በአፍሪካ ዋንጫ የሚሳተፉ አገራት እነ ናይጀሪያ፣ ጋና፣ እና ሌሎችም በአውሮፓ አሰልጣኞች ይታወቃሉ። ቬንገር ኢትዮጵያን የጠቀሱት ስለማውቃት እናያታለን ብለው ነው፡፡
አሰልጣኝ ሰውነት፣ በአፍሪካ ዋንጫ ራሳችንን እናስተዋውቃለን፣ እናሳያለን ብለው ለቬንገር ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ እስከ ሩብ ፍጻሜ የመድረስም ፍላጐት እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በበኩላቸው፤ ዋንጫ ባታመጡ እንኳን ጥሩ ተጫውታችሁ አገራችሁን አስጠሩ ብለዋችኋል፡፡ ኢትዮጵያ ከዚህ አፍሪካ ዋንጫ ምን አይነት ውጤት ትጠብቅ?አዳነ
ያለንበት ምድብ ጠንካራ ነው፡፡ የኛ ቡድንም ግን ጠንካራ ነው፡፡ አንዳንድ ሚዲያዎች በተለይ የአገር ውስጥ ቡድናችንን የሚያነሳሳ ግምት ከመሰንዘር ይልቅ በጣም በሚያሳዝን ግምት የቡድናችንን አቅም የሚያወርድ አስተያየት መስጠታቸው ያሳፍራል፡፡ እኛ በቡድናችን ውጤታማነት የራሳችን እምነት እና እቅድ ቢኖረንም ሚዲያው ባለን አቅም ላይ የተሻለ ሞራልና መነሳሳት የሚፈጥር ግምት መሰንዘር ቢለምድ ጥሩ ነው፡፡
አንድ ምሳሌ እዚህ ጋ ልጥቀስልህ፡፡ የእንግሊዝ ብሔራዊ ቡድን በሚሳተፍባቸው የዓለም ዋንጫና የአውሮፓ ዋንጫ ውድድሮች በአገሪቱ ሚዲያ ከጅምሩ የሚሰጠው ግምት ተጋንኖ ነው የሚቀርበው፡፡ ውድድሮቹ ከመጀመራቸው በፊት በርካታ የእንግሊዝ ሚዲያዎች ቡድናቸውን በሚሰጡት ግምት ለዋንጫ ያጩታል። ተጨዋቾቹ የዓለም ምርጦች መሆናቸውን አድንቀው ይዘግባሉ፡፡ በእኛ አገር ሚዲያዎች ግን አነስተኛ ግምት የመስጠት አባዜ አለ፡፡ አላግባብ የማናናቅ እና የማውረድ ተግባር በተደጋጋሚ አጋጥሟል፡፡ እኛ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ የምንሳትፈው ራሳችንንም አገራችንንም ወደተሻለ ደረጃ ከፍ ለማድረግ ነው፡፡ የመጀመሪያ ዙር አልፈን ጥሎ ማለፍ ውስጥ መግባት እንፈልጋለን፡፡ ጌታነህ
የመጀመሪያው ዓላማችን ከምድባችን ማለፍ ነው። ከዚያ በኋላ ያለውን የጥሎማለፍ ምዕራፍ በሂደት የመወጣት ፍላጐት ነው ያለኝ፡፡ አሉላ
የእኛ ስብስብ እዚህ ደረጃ መድረሱ አልተጠበቀም ነበር፡፡ ይህን ግምት ፉርሽ አድርጐ ለአፍሪካ ዋንጫ ደርሷል፡፡ እናም በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ በሚኖረን ተሳትፎ በተደጋጋሚ እንደተገለፀው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ክስተት ይሆናል፡፡ ብዙ እየተወራልን ነው። ዛምቢያ ሳይታሰብ ዋንጫ ወስዳለች፡፡ ማንም ወደ ውድድር ሲገባ ለማሸነፍ ነው ሌላ ትርጉም የለውም። እያንዳንዱን ጨዋታ ለክብር ነው የምንጫወተው። እርግጠኛ ነኝ በዚህ አፍሪካ ዋንጫ በኢትዮጵያ ቡድን ማንም ያልገመተው ውጠት ይመጣል፡፡ ሁሉም ቡድን ዋንጫ ለመውሰድ ያስባል፡፡ እኔ እያንዳንዱን ጨዋታ በትኩረት አድርገን ውጤታማ በመሆን ክስተት ሆነን ለመምጣት እንፈልጋለን፡፡
ዋንጫውን ከወዲሁ አናስብም፤ ከመጀመሪያ ጨዋታ ጀምሮ ትኩረታችን ተመሳሳይ ነው፡፡ ዩሱፍ
ጥሩ ቡድን አለን፡፡ በራሳችን ጨዋታ ማንንም ሳንፈራ በጥሩ ፉክክር እንሳተፋለን፡፡ ቡድናችን ከፍተኛ በራስ መተማመን አለው፡፡ ስለዚህ በማራኪ እግር ኳስ ተሳትፎ እናደርጋን፡፡

Read 8585 times