Saturday, 29 December 2012 09:35

ብዙ ያልተነገረለት የኢህአዴግ ራዕይ - የአፍሪካ አውራ ፓርቲ መሆን!

Written by  ኤልያስ
Rate this item
(3 votes)

በሃያ ሰባት አገራት 232 ጋዜጠኞች በእስር ላይ ይገኛሉ (ሥልጣን ሳይሆን መረጃ ስለጠየቁ!)
አንዳንዴ ሳስበው የዘመኑ ፖለቲካ አስቂኝ ነገር ይመስለኛል(ደንበኛ ኮሜዲ!) አስቂኝነቱ ግን ለፖለቲከኞቹ አይደለም፤እነሱማ ስራቸው ነው (ማን ነበር ንጉስነት እንጀራዬ ነው ያለው?) አስቂኝነቱ ለእኛ ነው- ለተደራሲያኑ!!(በጥበብ ቋንቋ መግለፄ እኮ ነው) ፖለቲካን እንደ ኮሜዲ ቲያትር አስባችሁት ታውቃላችሁ? (የምርም እኮ ኮሜዲ ነው!)

መቼም የፖለቲካ ኮሜዲው ደራሲያንና ተዋንያን ማን እንደሆኑ አይጠፏችሁም ብዬ አስባለሁ፡፡ ፖለቲከኞቹ ናቸዋ! ተደራስያኑ ደግም ምስኪኑ ህዝብ! (“ልማታዊ ህዝብ” ይባላል እንዴ?) ለነገሩ “የበይ ተመልካች” ወይም ታዛቢ ብንባልም አይከፋንም (ሃቅ ነዋ!) እናላችሁ ---- ፖለቲከኞቹ ይበላሉ፤ እኛ ኩራዝ እንይዛለን፡፡ ፖለቲከኞቹ ይወስናሉ፤ እኛ እንሰማለን፡፡ ምን ይደረግ … እጣ ፈንታችን እኮ ነው፡፡ (ይታደሉታል እንጂ አይታገሉትም!) ለነገሩ ተሰጥኦ ከሌለን ቀሽም ኮሜዲ ነው የምንሰራው (አያስቅ አያስለቅስ!) አያችሁ የፖለቲካ 
ኮሜዲ ችሎታ ይጠይቃል - ልዩ ተሰጥኦ!
እኔ መቼም የፖለቲካ ኮሜዲ ዘመን መሆኑ በጣም ነው ደስ ያለኝ (ምርጫ የለኝማ!) ግን እኮ በምናብ ባቡር (እውነተኛው ባቡር እስኪጀመር--) ወደ ኋላ ሸተት ብላችሁ የ60ዎቹን የፖለቲካ ተውኔቶች ብትመረምሩ የአሁኑን የፖለቲካ ኮሜዲ “ተመስገን!” ማለታችሁ አይቀርም፡፡ መቼም ከፖለቲካ ትራጄዲ የፖለቲካ ኮሜዲ ይሻላል፡፡ እኔ በበኩሌ ከምናዝን ቢቀለድብን እመርጣለሁ (Choosing the lesser evil እንደሚባለው!)
አንዳንዶች የቀድም ጠ/ሚኒስትር “ግልባጭ” የሚሏቸው (እሳቸውም የእሱ “ግርፍ” ነኝ ብለዋል እኮ) የኢፌዲሪ ጠ/ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ፤ ከኢቴቪ ጋር የመጀመርያውን ቃለምልልስ ሲያደርጉ፤ አገራችን ከባለ ሁለት ዲጂት የኢኮኖሚ ዕድገት ባሻገር፣ በመንገድ ግንባታና ማስፋፊያ ሥራዎችም ከአፍሪካ ተወዳዳሪ የሌላት ቀዳሚዋ አገር መሆኗን ሲገልፁ፤ (ሲያበስሩ በሚል ይተካልኝ!) ነፍሴ እንዴት በደስታ ጮቤ እንደረገጠች አልነግራችሁም፡፡ ከምሬ እኮ ነው! (ካልማልኩ አታምኑኝም?) ወዲያው ግን … አንድ “ነገረኛ ጥያቄ” ከአዕምሮዬ ጥግ ብቅ አለና ደስታዬን ነጠቀኝ። በቃ በጣፋጭ ህልም ከተሞላ የጥጋብ እንቅልፍ ላይ የተቀሰቀስኩ ነው የመሰለኝ፡፡ “በመንገድ ግንባታና ማስፋፊያስ ቀዳሚ ሆንን … በዲሞክራሲ ግንባታስ? በመድብለ ፓርቲ ሥርዓት ምስረታስ? በነፃና ፍትሃዊ ምርጫስ? በፕሬስ ነፃነትስ? የህዝቦችን ሰብአዊ መብት በማክበርስ?--” ደህና የነበርኩት ሰውዬ የነፃነት ታጋይ ሆኜላችሁ ቁጭ አልኩ፡፡ አይገርማችሁም? ያለ ዕቅድና ያለ ፍላጐቴ እኮ ነው በእነዚህ ሁሉ የጥያቄዎች ጐርፍ የተጥለቀለቅሁት፡፡ ታዲያ ምን እንደቆጨኝ ታውቃላችሁ? ያንን ጠ/ሚኒስትሩን ኢንተርቪው ያደረገ የኢቴቪ ጋዜጠኛ ባገኝ ኖሮ “ጠይቅልኝ” ብዬ እማፀነው ነበር (ለእኛ እስኪገኙ ልማታዊ ጋዜጠኛ ልጠቀም ብዬ እኮ ነው!)
በነገራችሁ ላይ ኢትዮጵያ ጋዜጠኞችን በማሰር ቶፕ 10 ውስጥ መግባቷን ሰምታችኋል አይደል? (ሪፖርቱ ኢህአዴግ አይልም - ኢትዮጵያ እንጂ!)
ከዓለም ጋዜጠኞችን በብዛት በማሰር ቁጥር አንድ አገር ማን መሰለቻችሁ? ቱርክ ናት ይላል- ሪፖርቱ። 49 ጋዜጠኞቿ ቤታቸው ወህኒ ሆኗል፡፡ ኢራን 45 ጋዜጠኞችን አስራ በሁለተኛነት ትከተላለች፡፡ ቻይንዬ ደግሞ 32ቱን የፕሬስ ሰዎች ሸብ አድርጋ ሶስተኛ ደረጃ ይዛለች፡፡ አራተኛዋ አገር ዘመዳችን ኤርትራ ስትሆን 28 ጋዜጠኞችን ዘብጥያ አውርዳለች፡፡ ኢትዮጵያ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች - ጋዜጠኞቿን በማሰር፡፡ በነገራችሁ ላይ መንግስታት ምን እንደነካቸው አይታወቅም ጋዜጠኞችን እንደጦር መፍራት ጀምረዋል፡፡ እናም ዘንድሮ ከ1990 ዓ.ም ወዲህ በመላው ዓለም ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ጋዜጠኞች መታሰራቸውን ነው ሪፖርቱ ይፋ ያደረገው - በጠቅላላው በ27 አገራት ውስጥ 232 ሪፖርተሮች፣ የፎቶ ጋዜጠኞችና ኤዲተሮች ለእስር ተዳርገዋል (ስልጣን ሳይሆን መረጃ ጠይቀው!)
እኔ የምላችሁ ግን … ኢቴቪ የሚዲያ ዳሰሳ የሚለው ፕሮግራሙ ላይ የስያሜ ለውጥ አደረገ እንዴ? የሚዲያ ዳሰሳው ቀርቶ የኒዮሊበራል አቀንቃኝ አገራት የተራራቁበትን “ልማታዊ መፃህፍት” እያስኮመኮመን እኮ ነው፡፡ እኔ ግን አንድ ሃሳብ አለኝ - ስለ ፕሮግራሙ፡፡ ሃሳቤ በይዘቱ ወይም በአቀራረቡ ላይ አይደለም፡፡ በፕሮግራሙ ርዕስ ወይም ስያሜ ላይ ብቻ ነው! እንደኔ እንደኔ የሚዲያ ዳሰሳም ሆነ የመፃህፍት ዳሰሳ የሚለው ስያሜ ፈፅሞ ፕሮግራሙን አይመጥንም፡፡ እውነቴን እኮ ነው … ጋዜጠኞቹ የሚያቀርቡልን እኮ ዳሰሳ ሳይሆን የስብከትና የፕሮፓጋንዳ ቅይጥ ነገር ነው (ሚስቶ እንደሚሉት) ስለዚህ ለምን በኢቴቪ የፕሮፓጋንዳና የቅስቀሳ ዲፓርትመንት ሥር “የልማታዊ አስተሳሰብ ማስፋፊያ ፕሮግራም” አይባልም? የሚል ሃሳብ አለኝ (ዲፓርትመንቱ ከሌለ ይቋቋማ!) ልብ አድርጉ! እንዲህ ያሻኝን የምናገረው ኢቴቪ የእኛ የሰፊው ህዝብ ሃብትና ንብረት ነው ብዬ ነው (ለግል ባለሃብት ተሸጠ እንዳትሉኝ?)
አንዳንዴ ተቃዋሚዎች፤ “ኢህአዴግ ሚዲያውን በሞኖፖል ተቆጣጥሮታል” ሲሉ እሰማና እኛ ሳናውቅ ንብረታችን ተሸጠ? ብዬ እደነግጣለሁ (ኢህአዴግ ገዝቶት እንዳይሆን ብዬ እኮ ነው!) አለዚያማ ማን የማንን ንብረት ይቆጣጠራል? ወይም ደግሞ እንደ መሬት “የህዝብና የመንግስት” ነው ይበሉንና አርፈን እንቀመጥ፡፡ እኔ የምለው ግን ---- የፖለቲካ ምህዳር የማን ንብረት ነው? “የህዝብና የመንግስት” ነው እንዳትሉኝና እንዳታስቁኝ (የዘመኑ ፖለቲካ ኮሜዲ ነው አልተባባልንም?) ኢህአዴግ ግን አንዳንዴ ያበዛዋል፡፡ ምናለ እቺን እንኳ ለተቃዋሚዎች ቢለቅላቸው (የፖለቲካ ምህዳር መሬት መሰለው እንዴ?)
በነገራችሁ ላይ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ሬዲዮ ምስጉን ሠራተኞች ሰሞኑን መሸለማቸውን ስሰማ እንዴት ደስ እንዳለኝ አታውቁም፡፡ የህዝብ ሽልማት ቢቀርባቸው የድርጅቱን እንኳን ያግኙ እንጂ! (ከሁለት ያጣ ሆኑ እኮ) ይሄን ደስታዬን ለአንዱ “ሟርተኛ” ወዳጄ ሳጋራው ምን እንዳለኝ ታውቃላችሁ? (“ደርግም እኮ “ኮከብ ሠራተኞች” እያለ ይሸልም ነበር!”) ምኑ ጨለምተኛ ነው ባካችሁ?
እናንተ--- ሰሞኑን የሰማኋት አንዲት ዜና እንዴት ያለች የፖለቲካ ኮሜዲ መሰለቻችሁ! የዜናዋን ፍሬ ነገር ልንገራችኋ --- ባለፈው ሳምንት ወደ ሩዋንዳ የተጓዙት ጠ/ሚኒስትራችን፤ ከሩዋንዳው ፕሬዚዳንት ጋር መወያየታቸውን የዘገበው ኢቴቪ፤ ፓርቲያቸው ኢህአዴግ ከሩዋንዳዉ ገዢ ፓርቲና ከሌሎች ተራማጅ አስተሳሰብ ያላቸው የአፍሪካ ፓርቲዎች ጋር በጋራ ለመስራት ስምምነት ላይ መደረሱን ጠቁሟል (ዘይገርም ነገር!) የቀድሞው የኢፌዲሪ ፕሬዚዳንት የዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳን የህይወት ታሪክ በሚተርከው “የነጋሶ መንገድ” የተሰኘ መፅሃፍ ላይ ያነበብኩትን አንድ መረጃ ካልነገርኳችሁ የዚህን ዜና አንደምታ ልታገኙት አትችሉም፡፡ ኢህአዴግ ገና ድሮ በትግል ላይ ሳለ (ከስልጣን ጋር ሳይተዋወቅ ማለት ነው) ስለነበረው ራዕይ ነጋሶ ሲናገሩ፤ “ኢህአዴግ በአፍሪካ ግዙፍና ተፅዕኖ ፈጣሪ ገናና ፓርቲ የመሆን ራዕይ” እንደነበረው ገልፀዋል፡፡ አሁን ትንሽ ተገለጠላችሁ? እኔ ሳስበው ኢህአዴግ ሩዋንዳ ድረስ ሄዶ ከባዕድ ፓርቲ ጋር ተስማምቶ የተመለሰው እቺን የጥንት ራዕይ ለማሳካት ይመስለኛል፡፡ አንዳንዶች “እዚህ መዲናዋ እምብርት ላይ 34 ተቃዋሚ ፓርቲዎች እንደራደር እያሉ ሲማጠኑት ሩዋንዳ ተሻግሮ መደራደር ምን ዓይነት ንቀት ነው?” ሊሉት ይችላሉ (ሲሰማቸው አይደል!)
አያችሁ --- ኢህአዴግ ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር መስራትን በተመለከተ ሁለት ራዕዮች እንዳሉት የደረስኩበት ሰሞኑን ነው - አገራዊና አህጉራዊ ይባላል። ቅድም እንደነገርኳችሁ አህጉራዊ ራዕዩ በአፍሪካ ገናና ፓርቲ መሆን ነው - ተፅዕኖ ፈጣሪ ግዙፍ ፓርቲ! አገራዊ ራዕዩስ? እንግዲህ ራዕይ ይሁን አይሁን አላውቅሁም እንጂ ከ2002 ምርጫ በኋላ “አዲስ ራዕይ” በተሰኘው የራሱ ልሳን ላይ እንዳሰፈረው ተቃዋሚዎች እንዳያንሰራሩ ለማድረግ በርትቶ እንደሚታትር ጠቁሟል (ጨለምተኛ ራዕይ ይሏል ይኼ ነው!)
አህጉራዊ ራዕዩን በተመለከተ ትንሽ የሚያሰጋኝ ምን መሰላችሁ? ኢህአዴግ ከአፍሪካ ልማታዊ ፓርቲዎች ጋር ጥምረት ወይም ግንባር ከመሰረተ በኋላ እዚህ አገር እንዳደረገው “ገናና ፓርቲ ነኝ” ብሎ ሸብ ለማድረግ እንዳይሞክር ነው (እነሱስ በእጃቸው ሙቅ ይዘዋል እንዴ?) ለነገሩ ኢህአዴግም ቢሆን አብዛኞቹ የአፍሪካ ገዢ ፓርቲዎች እንደሱው የነፃነት ታጋዮች እንደነበሩ የሚዘነጋው አይመስለኝም (ሁሉም በልቡ ገናና ነኝ ባይ እኮ ነው!) ምናልባት ዘንግቶት ችግር ላይ ከወደቀም የሚያዝንለት የለም፡፡ “የአገሩ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ጡር ነው” እየተባለ መሳለቂያ ነው የሚሆነው፡፡
እኔ የምለው ግን--- ከአገሩ አልፎ በአህጉር ደረጃ ገናና የመሆን ህልም ያለው ፓርቲ እንዴት የኮሙኒኬሽን አቅምና ብቃት አይኖረውም? ኢህአዴግ እኮ በኮሙኒኬሽን “Poor” ነው (ድክም ያለ!) አንዴም እንኳ የመግባባት ብልሃቱን ሳያሳየን ይኸው 21 ዓመት ሞላው። እንኳንስ “ጠላቴ” ብሎ ከፈረጃቸው ተቃዋሚዎች ጋር ቀርቶ ከእኛ ከህዝቦቹ ጋር እንኳ ሁሌ አይደል የሚላተመው? (ደግነቱ አጥፍቻለሁ ማለት ይወዳል!) እውነቴን ነው የምላችሁ ---- ኢህአዴግ ከአገር በቀሎቹ ፓርቲዎች ጋር እንዲህ ዓይንና ናጫ ሆኖ አህጉራዊ ራዕዩን ለማሳካት ቢነሳ ፈፅሞ አይሳካለትም፡፡ ለማንኛውም ግን ያስብበት ለማለት ያህል ነው፡፡

Read 5726 times