Administrator

Administrator

50 ሺህ ሰዎች በመፈንቅለ መንግስቱ ተጠርጥረው ፓስፖርታቸውን ተነጥቀዋል

   በቅርቡ ከከሸፈው የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ጋር በተያያዘ በዜጎቹ ላይ መረር ያለ እርምጃ መውሰዱን የቀጠለው የቱርክ መንግስት፣ያሰራቸው ሰዎች ቁጥር ከ26 ሺህ በላይ መድረሱን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
የአገሪቱን የፍትህ ሚኒስትር በኪር ቦዝዳግን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፤ ከመፈንቅለ መንግስት ሙከራው ጋር በተያያዘ 16 ሺህ ሰዎች በመደበኛ ሁኔታ ታስረው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ ሲሆን ሌሎች 6 ሺህ ታሳሪዎችም ለፍርድ እንዲቀርቡ በሂደት ላይ ይገኛሉ፤8 ሺህ ያህል ታሳሪዎች ደግሞ ከእስር ቢፈቱም ምርመራ እየተደረገባቸው ነው፡፡
ሚኒስትሩ የቀሪዎቹን 4 ሺህ ያህል እስረኞች ጉዳይ በተመለከተ ያሉት ነገር እንደሌለ የጠቆመው ዘገባው፤ከመፈንቅለ መንግስቱ ጋር ንክኪ አላቸው ተብለው ከታሰሩት 26 ሺህ ያህል ሰዎች መካከል ወታደሮች፣ ፖሊሶች፣ የመንግስት ሰራተኞችና ሌሎች ግለሰቦች እንደሚገኙበትና በሺዎች የሚቆጠሩትም ከስራቸው መባረራቸውን አመልክቷል፡፡
የፕሬዚዳንት ኤርዶጋን መንግስት ከመፈንቅለ መንግስቱ ጋር በተያያዘ እየወሰደ ባለው እጅግ ከረር ያለ እርምጃ፣ ከ50 ሺህ በላይ የሚሆኑ ተጠርጣሪዎች ፓስፖርቶች መሰረዛቸውን፣ ጋዜጠኞችና ምሁራን መታሰራቸውን፣ ከ130 በላይ መገናኛ ብዙኃን መዘጋታቸውንም ዘገባው ገልጧል፡፡
በቅርቡ በአገሪቱ መንግስት ላይ በተቃጣው የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ፣ ከ246 በላይ ሰዎች ለሞት መዳረጋቸውንና ከ2 ሺህ በላይ የሚሆኑትም የመቁሰል አደጋ እንደደረሰባቸው ዘገባው አስታውሷል፡፡


ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ንሥር ጎጆ ቤቷን ትልቅ ዛፍ ቅርንጫፍ ላይ ትሠራለች፡፡
አንዲት ድመት ደግሞ ከነልጆቿ የዛፍ ግንድ መካከል የተቦረቦረ ሥፍራ ትኖራለች፡፡
አንዲት የዱር አሣማ ደግሞ ከዛፉ ግርጌ በተቦረቦረው ግንድ ውስጥ ከነልጇቿ ትኖራለች፡፡
እነዚህ ሶስት እንስሳት እንደ ጎረቤታሞች ሁሉ በፍቅር ተሳስበው፣ በአንዱ ግንድ ላይ ሲኖሩ ያስቀኑ ነበር፡፡ በኋላ ግን ተንኮለኛዋ ድመት ያንን የመሰለ የፍቅር ህይወታቸውን ልታደፈርስ ተነሳች፡፡
ወደ ንስሩ ጎጆ ወጣች-ድመቲት፡፡
 እንዲምህ አለቻት፡-
‹‹እኔና አንቺ ከባድ አደጋ እያንዣበብን ነው››
‹‹እንዴት?›› አለች ንሥር››
‹‹አሣም ተንኮለኛ ናት፡፡ የእኛን ህይወት ለማበላሸት ሌት ተቀን ከመጣጣር አልታቀበችም››
ንሥርም፤
‹‹እኛ የምንኖረው የራሳችንን ኑሮ፡፡ አሣማም ልጇም የሚኖሩት የራሳቸውን ኑሮ፡፡ ለምን እንደራረሳለን?›› አለችና ጠየቀች፤ በሙሉ የዋህነት፡፡
ድመትም፤
‹‹አሣማ እንደኛ ቀና ብትሆን ጥሩ ነበር፡፡ ነገር ግን ልቧ ክፉ ነው፡፡ ስለሆነም የሁላችንም የጋራ መኖሪያ የሆነውን ግንድ ከሥሩ እየገዘገዘች ልትጥለው ነው፡፡ ከእንግዲህ መኖሪያ አይኖረንም። የአንቺም የእኔም ልጆች የእሷ ምግብ መሆናቸው ነው›› አለች፡፡ ንሥር በጣም ተረበሸች፡፡ ተሸበረች፡፡ ድመት ሆዬ፣ ከንሥር ጎጆ ወደዛፉ ግርጌ ወረደች፤ አሣማዋ ዘንድ መጣችና፤
‹‹እመት አሣማ፤ የእኔና አንቺ  ሕይወት አደጋ ላይ መሆኑን ታውቂያለሽ?›› ስትል አሣማን ጠየቀቻት፡፡
አሣማም፤
‹‹ለምን? እንዴት? እኔ ምንም የማውቀው ነገር የለም››፤ አለቻት፡፡
ድመትም፤
‹‹እዚያ፤ ዛፉ አናት ላይ ካለችው ንሥር መጠንቀቅ አለብሽ፡፡ አንድ ቀን ስትዘናጊላት ወደ ታች ወርዳ ግልገልሽን ይዛብሽ ትሄዳለች፡፡ ጊዜ እየጠበቀች ነው፡፡ ያንቺ ልጆች የንሥር ልጆች ቀለብ እንዳይሆኑ ብታስቢበት ይሻላል›› አለች፡፡
ልክ እንደ ንሥሩ ሁሉ አሣማም በጣም ደነገጠች፡፡ በጣም ተሸበረች፡፡ ድመት ሁለቱን ጎረቤቶቿን እጅግ አድርጋ ካስፈራራች በኋላ ወደ መኖሪዋ ተመለሰች፡፡ ከዚያን ጊዜ በኋላ የፈራች ለማስመሰል ድመት ቀን ቀን መውጣቷን ተወች፡፡ ለልጆቿ ምግብ ለመፈለግ ማታ ማታ ብቻ ሆነ የምትወጣው፡፡
ንሥር ከጎጆዋ መውጣት ፈራችና ራሷን ዘግታ ቁጭ አለች፡፡
አሣማም ከፍርሃቷ የተነሳ ከዛፉ ግርጌ ካለው ሥር ንቅንቅ አልልም ብላ ከመኖሪያዋ ሳትወጣ ልጆቿን መጠበቅ ሆነ ሥራዋ፡፡ ቀን እየገፋ ሲመጣ የንሥርና የአሳማ ቤቴሰቦች በረሀብ አለቁ፡፡ ድመትም ለራሷና ለልጆቿ የሚሆን የተትረፈረፈ ምግብ አገኘች፡፡
የጋራ ቤታቸውን አስከብረው፣ በፍቅር እየተሰባሰቡ የሚኖሩ የታደሉ ናቸው፡፡ በተንኮል የሌሎችን ህይወት የሚያደፈርሱ እኩያን፤ የጊዜ ጉዳይ እንጂ ዋጋ መክፈላቸው አይቀሬ ነው፡፡ ለሁሉም በሚበቃ አገር፤ የሌላውን ህልውና በሚያጨልም መልኩ ግፍ መፈፀም የማታ ማታ ማስጠየቁ ሳታውቅ በስህተት፣ አውቀህ በድፍረት ባደረግኸው መጠየቅ አለና፤ የምታደርገውን በቅጡና በጥንቃቄ አድርግ! የሀገራችን ሰላም ማጣት ለማንም የሚበጅ አይደለም፡፡ ችግሮችን በሰላማዊ መንገድ መፍታት እንጂ በኋይል ለመፍታት መሞክር ጊዜያዊ መፍትሔ እንጂ ዘላቂ መላ አይሆንም፡፡ መንግሥት በየጊዜው የሚወስዳቸው አርምጃዎች እንድም ሶስትም ናቸው ከሚባሉት ከመልካም አስተዳደር፣ ከፍትሕና ከሙስና ችግሮ አኳያ፣ ያላንዳች ማንገራገር ራሱን ካልመረመረ ወደ ካንሰርነት በመለወጥ ላይ ያለ በሽታ ይዞ እንደመክረም መሆኑ አይካድም፡፡
የአገራችንን ጠቅላይ ስዕል (bigger picture) ማየት ተገቢ ነው፡፡ ገዢ የሚባሉትን ትላልቅ ችግሮች እንጂ እንደ ቀዶ ጥገና ሀኪም የተወሰኑ ብልቶን ብቻ ለይቶ ለማከም መጣር የተነካኩትን አካላት እንደ መዘንጋት ስለሚሆን አጠቃላይ ጤና ከመታወክ አይድንም፡፡ “የአብዬን እከክ ወደ ምዬ ልክክም” (Blame - Shifting) አያዋጣም፡፡ ነገ ተነገ - ወዲያ እናስተካክለዋለን ማለትም (procrastination) ችግሮችን ከማባባስና ቀንን ከማቅረብ በስተቀር የሚፈይደው ነገር አይኖርም። አድሮ ቅርንጫፍ አብቅሎ አፍጦ ይመጣብናልና፡፡
ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን በ“ሐምሌት” ትርጉሙ እንዲህ ይለናል፡-
“ዛሬ ለወግ ያደረግሺው፣ ወይ ለነገ ይለምድብሻል፤ ልማድ ፊት እንዳሳዩት ነው፣ ወይ ይጠፋል ወይ ያጠፋል፡፡ ከርሞም የሰለጠነ እንደሁ፣ ተፈጥሮ ይሆናል ይባላል”
እንጠንቀቅ፡፡ ራሳችንን እንመርምር፡፡ የችግሮቻችንን አጠቃላይ ስዕል እንቃኝ፡፡ ነጋ - ጠባ እያወራናቸው ያልፈታናቸው ችግሮች የትየለሌ ናቸው! በግልፅ ችግሮቻችንን እንወያይባቸው፡፡ ልዩ ልዩ ታርጋ እሰጠን አንሽሻቸው፡፡ ፈረንጆች Denial የሚሉት ዓይነት፤ ያለውን ነገር እንደሌለ አድርገን መካድና መካካድ፤ የትም አያደርሰንም፡፡ መረጃ ባለመስጠት፣ አገር አናድንም፡፡ ጥቃቅኑን ነገር እየመነዘርን ፀጉር ስንጠቃም ያው ከቁንጫ መላላጫ ማውጣት ነውና ከንቱ ድካም ይሆናል፡፡ አንድም ደግሞ ከግጭት አዙሪት እንዴት እንውጣ ብሎ ራስን መጠየቅ አስፈላጊ ነው። እንደ ሰሞኑ የውሃ ዋና ጭቅጭቅ አፍጥጠው ሚመጡ አያሌ ጅላጅል ሀሳቦች፣ የማመን ያለማን ግልፅነት የጎደለው ስፖርት፣ የዓለም መሳቂያ እንዳያደርጉን አሁንም ዐይናችንን መክፈት ተገቢ ነው፡፡ ምላሽ ያላገኙ ጥያቄዎችን ከልብ እንፈትሽ፡፡
“የግጭት ቀለበለት ካሰርን ቆይተናል ሰርጉ ገና አልተደገሰም” እየተባለ ሲሾፍ፤ ውስጡ መራራ ዕውነት እንዳለ አለማስተዋል የዋህነት ነው፡፡ በበርካታ ስራ አጥ ወጣት የተወጠረች አገር ምንም አይነት ተንኮል ቢሸረብባት አይገርምም!! an idle mind is the devil’s workshop ይሏልና!! (ሥራ የፈታ አዕምሮ የሰይጣን ስራ - ቤት ይሆናል፤ እንደማለት ነው) እለት ሰርክ በተግባር የምናውን ነገር ስንክድ መፍትሄ መፈለግ ያባት ነው፡፡ ተግባር መስተውት ነው፡፡ ከተግባር ወዲ የምንቆጥረውም ስክር አይኖርም፡፡ “መስተዋት የምትነግርህን፣ የእናትህ ልጅ አትነግርህም” የሚባለው ተረትና ምሳሌ፣ በሀገራችን ያለውን የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ እና የማህበራዊ ሁኔታ መቃወስ በቅጢ እንድንፈትሽ፣ መስተዋቱን በጥንቃቄ እንድናይ፤ አመላካች ነው፡፡

የኢትዮጵያ መንግስት፣ በግማሽ ዓመት 670 ሚ.ዶላር ለእዳ ክፍያ አውጥቷል

የውጭ እዳ በፍጥነት እየተከማቸበት የመጣው የኢትዮጵያ መንግስት፣ በ2006 ዓ.ም የብድር እዳ ከነወለዱ 570 ሚ. ዶላር መክፈሉ የሚታወስ ሲሆን፣ ዘንድሮ ክፍያው በእጥፍ ጨምሮበታል። ዘንድሮ እስከ መጋቢት ድረስ፣ 670 ሚ.ዶላር እንደከፈለ ከገንዘብ ሚኒስቴር የተገኘ መረጃ ገልጿል።
ከአራት አመት በፊት፣ የመንግስት ጠቅላላ የውጭ እዳ ወደ 9 ቢሊዮን ገደማ እንደነበረ የገንዘብ ሚኒስቴር ጠቅሶ፣ ዘንድሮ እስከ መጋቢት ወር ድረስ፣ የእዳው ክምችት 20.6 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን አስታውቋል።
በተለይ፣ በባቡር መስመር ግንባታ፣ በቴሌኮም እና ለአመታት በተጓተቱት የስኳር ፕሮጀክቶች ሳቢያ በፍጥነት እየተከማቸ ከመጣው ብድር ጋር፣ ለእዳና ለወለድ ክፍያ የሚውለው የውጭ ምንዛሬም እየከበደ እንደመጣ የሚኒስቴሩ ሪፖርት ያሳያል።
በ2004 እና በ2005 ዓ.ም፣ ለእዳና ለወለድ ክፍያ የሚውለው የውጭ ምንዛሬ ግማሽ ቢሊዮን ገደማ ነበር። አምና የክፍያው ሸክም ወደ አንድ ቢሊዮን ዶላር ተጠግቷል (980 ሚ.ዶላር)።
የወለድ ክፍያው ለብቻው ሲታይም እንዲሁ፣ ከአመት አመት እየጨመረ መጥቷል። ከአራት አመት በፊት፣ 100 ሚሊዮን ዶላር የነበረው የወለድ ክፍያ፣ አምና ከ250 ሚሊዮን ዶላር በላይ ሆኗል። ዘንድሮም እስከ መጋቢት ድረስ፣ ለወለድ 210 ሚ.ዶላር እንደተከፈለ፣ የገንዘብ ሚኒስቴር መረጃ ይገልፃል። እየከበደ የመጣውን የእዳና የወለድ ክፍያ ለማሟላት፣ ከኤክስፖርት የሚገኘውን ገቢ በአምስት አመታት በእጥፍ ለማሳደግ ታስቦ የነበረ ቢሆንም፣ ከ2003 ዓ.ም ወዲህ፣ የኤክስፖርት ገቢ እስካሁን አልጨመረም። ያኔ ከነበረበት፣ የ3 ቢሊዮን ዶላር ገቢ፣ ብዙም አልተነቃነቀም።
ደግነቱ፣ ለነዳጅ ግዢ ይውል የነበረው የውጭ ምንዛሬ፣ ባለፉት ሁለት አመታት ቀንሷል። ከ2006 ዓ.ም ጋር ሲነፃፀር፣ የቤንዚን  የአለም ገበያ ዋጋ በ70% ቀንሷል። የናፍታ ደግሞ በ60% ቀንሷል። በዚህም፣ መንግስት በአመት ውስጥ፣ ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ ወጪ ለማዳን እድል አግኝቷል።
ይህም ብቻ አይደለም። በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በየአመቱ ወደ አገር ቤት የሚልኩት የውጭ ምንዛሬ እየጨመረ መምጣቱ፣ መንግስትን ጠቅሟል። ከአራት አመት በፊት፣ በአመት 2.5 ቢሊዮን ዶላር ገደማ ይልኩ የነበሩ ኢትዮጵያውያን፣ አሁን በአመት ከ4 ቢሊዮን ዶላር በላይ ይልካሉ - በኤክስፖርት ከሚገኘው የውጭ ምንዛሬ የሚበልጥ።

የምርምር ውጤቶች መድብል ነው ተብሏል
    በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የመካኒካልና ኢንዱትሪያል ምህንድስና መምህር በሆኑት ፕሮፌሰር ዳንኤል ቅጣው፣የተሰሩ የምርምር ውጤቶች የተሰባሰቡበት፤ ‹‹እንሆ መንገድ›› የተሰኘ መፅሐፍ ዛሬ ከጠዋቱ ከ3፡00 ጀምሮ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት የስብሰባ አዳራሽ ይመረቃል፡፡
 መፅሃፉን ያዘጋጀው አንዷለም አባተ (የአፀደ ልጅ) እንደሆነ ታውቋል፡፡ የምርምር ውጤቶቹ በመፅሀፍ መልክ የታተመበት ዋና አላማ፣ ችግር ፈቺ የምርምር ውጤቶች ማህበረሰቡ ዘንድ ደርሰው ጥቅም ላይ እንዲውሉ በማሰብ እንደሆነ በመጽሐፉ መግቢያ ላይ ተገልጿል፡፡ መፅሐፉ በ10 ክፍሎችና በበርካታ ንዑስ ርዕሶች ተከፋፍሎ፣በ188 ገፅዎች የተቀነበበ ሲሆን በ80 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

 ሚዩዚክ ሜይዴይ ከኢትዮጵስ ኮሌጅ ጋር በመተባበር ‹‹ዛሬም እንጉጎሮ›› በተሰኘው የፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማሪያም የግጥም መፅሀፍ ላይ ነገ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ በብሄራዊ ቤተ- መፅሀፍትና ቤተ መዛግብት አዳራሽ ውይይት ይካሄዳል፡፡  ለውይይት የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት በደብረብርሀን ዩኒቨርሲቲ የስነ-ፅሁፍ መምህርና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፒ. ኤች.ዲ እጩ የሆኑት ደራሲ ታደለ ፈንታው እንደሆኑ የተገለፁ ሲሆን በውይይቱ ላይ የመሳተፍ ፍላጎት ያለው ሁሉ እንዲገኝ  ሚዩዚክ ሜይዴይ ጋብዟል፡፡

ዛይ ራይድ ሜትር ታክሲዎች፤ በመጪው ሳምንት ስራ ይጀምራሉ

      አዲስ አበባ ከኒውዮርክና ጀኔቭ ቀጥላ ሶስተኛዋ የዲፕሎማቲክ ከተማ ናት፡፡ እነዚህ ዲፕሎማቶችና ቱሪስቶች እንዲሁም የመዲናዋ ነዋሪዎች ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት ይፈልጋሉ፡፡ ከ15 ዓመት በፊት በጣት የሚቆጠሩ ደረጃቸውን የጠበቁ ሆቴሎች ነበሩ፡፡ ዛሬ፣ ከ100 በላይ ሆነዋል፡፡ አዲስ አበባ መሃሏ ነው እንጂ በአራቱም አቅጣጫ ሲመለከቱ፤ “እውነት አዲስ አበባ ናት!” በማለት ያስገርማሉ - በሪል እስቴቶችና በግለሰቦች የተገነቡት ዘመናዊ መኖሪያ ቤቶች፡፡
የመዲናዋ ከፍተኛ ችግርና ራስ ምታት የሆነው የትራንስፖርቱ ጉዳይ ነው፡፡ መንግስት ታክሲዎች በቀጠና ተሰማርተው እንዲሰሩ አደረገ፡፡ ነገር ግን ችግሩ ባሰበት እንጂ አልተቀረፈም፡፡ ሐይገር ባስ አስመጣ፤ ችግሩ ግን ያው ነው፡፡ ቅጥቅጥ ቺኳንታዎች፣ ከፍተኛ የህዝብ ማመላለሻ አውቶብሶችና የሲቪል ሰርቪስ አውቶቡሶች በድጋፍ ሰጪነት እንዲሰሩ ተደረገ፡፡ ምንም ጠብ አላለም፡፡ በስራ መግቢያና መውጫ እንዲሁም በስራ ሰዓት ረዣዥም ሰልፎች መመልከት የዘወትር ልማድ ከሆነ ሰነባብቷል፡፡
ይህንን ችግር ለመቅረፍ አሁንም መንግስት አዲስ ነው ያለውን ዘዴ ቀይሷል፡፡ አንዱ ረዥም ርቀት ተጓዥ አውቶቡሶችን ማቅረብ ነው፡፡ ችግሩን ምንም ያህል አልቀረፉም እንጂ 50 አውቶቡሶች ስራ ጀምረዋል፡፡ ሌላው ዘዴ ደግሞ የታክሲ ማኅበራት ተደራጅተው ዘመናዊ ታክሲዎች እንዲያስገቡ ማድረግ ነው፡፡
በብርሃን ባንክ የገንዘብ ድጋፍ 750 ታክሲዎች ተገዝተው ከቀረጥ ነጻ ሊገቡ ነው ተብሏል፡፡ በዚህ በሁለተኛው ዘዴ በመሳተፍ ችግሩን ለመቅረፍና የበኩሉን ሚና ለመወጣት ያሰበ ወጣት፤ የአሜሪካና የሌሎች አገሮችን ልምድ ይዞ ብቅ ብሏል፡፡ የዛይ ራይድ መስራችና ዋና ሥራ አስፈፃሚ ወጣት ሀብታሙ ታደሰ፡፡ ዛይ ራይድ የሚሰራው በሶፍትዌር ነው፡፡ የታክሲ አገልግሎት የፈለገ ሰው www.zayride.com ገብቶ ታክሲ እንዲመጣለት ጥሪ ያደርጋል፡፡  አገልግሎት ፈላጊው በአገልግሎት መጠየቂያ ፎርም ላይ ስምና አድራሻውን ይጽፋል፡፡ ከዚያም ታክሲው በጂፒኤስ እየተመራ፣ ወዲያው በአድራሻው ከች ይላል፡፡ ዛይ፤ በዝዋይ ሐይቅ ደሴት ላይ የሚኖሩ ዜጎች መጠሪያ ነው፡፡ወጣት ሀብታሙ ባሌ ውስጥ በጎባ ከተማ ነው የተወለደው፡፡  በአራት ዓመቱ ወደ አዲስ አበባ መጥቶ ት/ቤት ገባ፡፡ እስከ 7ኛ ክፍል ከተማረ በኋላ፣ በ1981 ዓ.ም ከቤተሰቦቹ ጋር ወደ አሜሪካ ሄዶ ቦስተን መኖር ጀመረ፡፡ 13ኛ ዓመት በዓሉን ያከበረው እዚያ ነው፡፡ ቦስተን ማሳቹሴት ት/ቤት 9ኛ ክፍል ገብቶ፣2ኛ ደረጃን አጠናቀቀ፡፡ ከዚያም ከማሳቹሴት ዩኒቨርሲቲ  በኢኮኖሚክስ የመጀመሪያ ዲግሪውን አገኘ፡፡ ፍላጎቱ በቢዝነስ መሰማራት ስለነበረ፣በተማረው ትምህርት ተቀጥሮ አልሰራም፡፡ ከታላቅ ወንድሙ ጋር ቦስተን ውስጥ “ባሻ” የተባለ የኢትዮጵያ ሬስቶራንት ከፍተው መስራት ጀመሩ፡፡ ሀብታሙ፤አዲስ አበባ ህዝቡን የሚያሳትፍ፣የተሟላ ደህንነት ያለው፣ዘመናዊና ርካሽ የትራንስፖርት ሲስተም ያስፈልጋታል ይላል፡፡ ከተማዋ እያደገች እንደሆነ ጠቅሶ፣ አዳዲስ፣ መብራታቸው የሚሰራ፣ ፍሬናቸው ያልተበላሸ፣ ነዳጅ በየመንገዱ የማያልቅባቸው፣ ሁልጊዜ ፍተሻና ሰርቪስ የሚደረግላቸው፣ … ዘመናዊ ታክሲዎች ያስፈልጋታል ብሏል፡፡ ስለዚህ በኢንተርኔት የሚሠራ ሲስተም አዘጋጅቷል፡፡ አዲሱ ሲስተም ሞባይል ስልክ ላይ የሚጫን አፕሊኬሽን ነው፡፡ የታክሲ አገልግሎት ፈላጊው በጣቱ ሲስተሙን ሲነካ፣ ታክሲው በጥቂት ጊዜ ውስጥ ፈላጊው ያለበት ቦታ ይመጣለታል፡፡ ታክሲው ሲመጣ፣ ታርጋው፣ የአሽከርካሪው ስምና ፎቶ ለፈላጊው ይደርሳል፡፡ ለአሽከርካሪው ደግሞ የአገልግሎት ፈላጊው  ስም፣ ስልክ ቁጥርና ፎቶ ይደርሰዋል፡፡ ታክሲ ፈላጊው ስብሰባ ቦታ ወይም ገበያ መኻል ወይም ቢሮ አካባቢ ቢሆን፣ታክሲ አሽከርካሪው የአገልግሎት ፈላጊውን ማንነት በቀላሉ እንዲያውቅ ይረዳዋል፡፡ የታክሲው ሰሌዳ ቁጥርም ፈላጊው ዘንድ ስላለ በቀላሉ ሊያውቀው ይችላል፤በማለት ሀብታሙ አስረድቷል፡፡ ይህ ሲስተም ሁሉንም ሰው ተጠቃሚ ያደርጋል ይላል፡፡ በአሁኑ ወቅት ከተማው ውስጥ ባሉ አሮጌ ላዳዎች ኅብረተሰቡ ካልተቸገረ በስተቀር አይጠቀምም፡፡ ምክንያቱ ደግሞ የሚጠይቁት ዋጋ በጣም ውድ ስለሆነ ነው፡፡ ለትንሽ ርቀት የሚጠይቁት 50 እና 60 ብር ነው፡፡ እኛ ግን የምናስከፍለው መንግስትና ማኅበራቱ በሚወስኑት ታሪፍ በኪ.ሜትር አስልተን ነው፡፡ በዚህ አይነት ህዝቡ በተመጣጣኝ  ዋጋ አገልግሎት ያገኛል፡፡ አሁን ያሉት ላዳ ታክሲዎች  ብዙ ጊዜ ቆመው ነው የሚውሉት፡፡ የእኛ ታክሲዎች ግን ብዙ ምልልስ ያደርጋሉ፡፡ ለምሳሌ ፒያሳ የሄደ ታክሲ ባዶውን አይመለስም፤ከሄደበት ሌላ ተጠቃሚ ይዞ ይመለሳል፡፡ አሁን የሚገቡት አዲስ ታክሲዎች 750 ናቸው፡፡ ለከተማው ህዝብ በሙሉ አገልግሎት ለመስጠት በቂ አይደሉም፡፡ ስለዚህ አሁን በአገልግሎት ላይ ያሉትንም አሮጌ ላዳዎች እንጠቀማለን፡፡ በዚህ ዓይነት ብዙ ምልልስ ሲያደርጉ ጥሩ ገቢ ያገኛሉ፤ መኪናቸውንም ይቀይራሉ፤የከተማዋንም እይታ ይለውጣሉ፡፡
በከተማዋ ካሉት 26 ማኅበራት ውስጥ ከ6ቱ ጋር ለመስራት ባለፈው እሁድ መፈራረሙን ሀብታሙ ገልጿል፡፡ አብዛኞቹ የተፈራረሙባቸው ጉዳዮች ስነ ምግባርን የተመለከተ ነው፡፡ ታክሲ እያሽከረከሩ ጫት መቃም፣ ሲራ ማጨስ፣ ቤንዚን ሳይሞሉ መጓዝና መንገድ ላይ ማቆም፣ መጠጥ ጠጥቶ  ማሽከርከር፣ … ተጠቃሚዎች ወደ ታክሲ እንዳይመጡ ስለሚያደርጉ ክልክል ናቸው፡፡ የተሳፋሪው ደህንነት እንዲጠበቅ፣ ዕቃ (ሞባይል፣ ገንዘብ፣--) ረስቶ ቢወርድ ሾፌሩ ተጠያቂ ይሆናል፡፡ በነዚህ ነጥቦች ላይ ነው ተስማምተው የተፈራረሙት፡፡ ሌላው የዛይ ራይድ ጥቅም ለተማሪዎች አገልግሎት መስጠት ነው፡፡ ሲስተሙ ላይ የተማሪዎች አፕሊኬሽን አለ፡፡ አንድ ወላጅ ልጆቹን ት/ቤት ማድረስ የማይችልበት ሁኔታ ቢፈጠር፣ ዛይ ራይድን ጠርቶ ት/ቤት እንዲያደርስለት ማድረግና ልጆቹ ት/ቤት እስኪደርሱ በስልካቸው መቆጣጠር ይችላል፡፡ ታክሲው የት ጋ እንደታጠፈ፣ ስንት ደቂቃ እንደፈጀበት፣ የት እንደደረሰ፣ ልጆቹ ከታክሲው ወርደው ት/ቤት ሲገቡ፣ በሲስተሙ ይከታተላል፡፡  
ዛይ ራይድ፤አዲሶቹ ታክሲዎች እስኪገቡ ድረስ አይጠብቅም፡፡ በሚቀጥለው ሳምንት በ130 ላዳ ታክሲዎች ሥራ እንደሚጀምር ሀብታሙ ተናግሯል፡፡ አሁን ባጃጆችን አልመዘገቡም እንጂ በቅርብ ጊዜ ውስጥ ከከተማ ወጣ ወዳሉ ኮንዶሚኒየሞች የሚያደርሱ ባጃጆችን ለማሰማራት ዕቅድ አለው፡፡ ይህን ሲስተም ለመስራት 2 ሚሊዮን ዶላር (40 ሚ.ብር ገደማ) ያህል በጀት መድበው ነበር የተነሱት፡፡ ነገር ግን በየጊዜው አዳዲስ ነገሮች ስለሚጨመሩና የተሰራውም በየጊዜው መሻሻል ስላለበት፣ወጪው ከተገመተው በላይ ከፍ ማለቱን ሀብታሙ ታደሰ ተናግሯል፡፡ ይህ ሲስተም ከተጀመረ አራት ወይም አምስት ዓመት ቢሆነው ነው፤ይላል ሀብታሙ፡፡ በአሜሪካ ማሳቹሴትስ ከተማ የጀመረው UBR የተባለ ኩባንያ ነው፡፡ ይህ ኩባንያ በዓመት 60 ቢሊዮን ዶላር ያንቀሳቅሳል፡፡ ሲስተሙ በጎረቤት አገር ኬንያም እየተሰራበት ነው፡፡ ሲስተሙ ከተጀመረ ወዲህ የኬንያ አሽከርካሪዎች ገቢ በሦስት እጥፍ ማደጉን ሃብታሙ ገልጿል፡፡ ለአዲስ አበባ የላዳ ታክሲ ባለቤቶችም ሆነ ለአዲሶቹ የታክሲ ባለንብረቶችና ሹፌሮች ተስፋ ሰጪ ዜና ይመስላል፡፡ አገልግሎቱ በፍጥነት ከተስፋፋ ደግሞ የከተማዋ ነዋሪዎችንም ከታክሲ ወረፋ ግፊያ ይገላግል ይሆናል፡፡     

 በድርቁ የተጎዱ፣የምርጥ ዘርና የማዳበሪያ መግዣ አጥሯቸዋል
     በባሌ ዞን አጋርፋ ወረዳ ኢላጊጎዳሪ ቀበሌ ማዳበሪያ ሲገዙ ያገኘናቸው ወ/ሮ ከበቡሽ መንግሥቱ ገበሬ ናቸው፡፡ የ45 ዓመቷ ወይዘሮ፤5 ልጆቻቸውን የሚያሳድጉት አርሰው በሚያገኙት ገቢ ነው፡፡ አምና ብዙ አርሶ አደሮች በድርቁ ሲጎዱ፣ ወ/ሮ ከበቡሽ ጥሩ ምርት ማግኘታቸውን ይናገራሉ፡፡ ‹‹አምና ድርቅ አልጎዳኝም፤ ጥሩ ምርት አግኝቻለሁ፡፡ 4 ሄክታር መሬት ነው ያለኝ፤ ከአንድ ሄክታር 50 ኩንታል አግኝቻለሁ፡፡
‹‹በዚህ ዓመትም የተሻለ ጥሩ ምርት ለማግኘት ጥሩ ዝግጅት እያደረግን ነው፡፡ የእርሻ መሬቴን አራት ጊዜ አርሻለሁ፣ አንድ ጊዜ ነው የሚቀረኝ፡፡ አምና ዩሪያና ዳኘ ነበረ የተጠቀምኩት፡፡ ዛሬ የገዛሁት ዳፕ ነው፤ዩሪያ አላገኘሁም፡፡ ዳፑን 650 ብር ነው የገዛሁት፡፡ ምርጥ ዘርም ኩንታሉን በ800 ብር ገዝቻለሁ፡፡ የግብርና ባለሙያዎች ጥሩ ምርት እንድናገኝ ያሠለጥኑናል፤ በመስመር እንድንዘራ ይመክሩናል፤የመሬቱ ለምነት እንዲጨምር ዳፕና ዩሪያ ደባልቀን እንድንጠቀም፣ አረምና እንክርዳድ እንዳይወጣ ኬሚካል ያቀርቡልናል፡፡ በአጠቃላይ አብረን ነው የምንሠራው ማለት እንችላለሁ›› ብለዋል፡፡
አርሶ አደር አደም ሁሴን፤በአጋርፋ ወረዳ የአሊ ቀበሌ ነዋሪ ናቸው፡፡ አቶ አደምን ያገኘነው ለመኸር እርሻ መሬታቸውን ሲያዘጋጁ ነው፡፡ አቶ አደም በግላቸው 6 ሄክታር መሬት አላቸው፡፡ በኮንትራትና በእኩል ክፍያ የወሰዱት መሬት ስላለ፣ በአጠቃላይ 15 ሄክታር እያለሙ ነው፡፡ የቀበሌው ዋነኛ ምርት ስንዴ በዓመት አንዴ ነው የሚመረተው፡፡ ምክንያቱ ደግሞ በአካባቢው በቂ ዝናብ አይጥልም፡፡ ‹‹በበልግ የሚዘራው ገብስ፣ በቆሎ፣ ጤፍ፣ አተር፣… ናቸው፡፡ በአሁን ሰዓት የሚታየው የእነዚህ ሰብሎች ቡቃያ በጣም ጥሩ ነው፡፡ ባለፈው ዓመት የተከሰተው ድርቅ፤ አሊ ቀበሌ ይሻላል እንጂ ከጎናች ባሉ ቀበሌዎች አማለማ፣ ኤልምዲ፣አንድ ሌላ ቀበሌ ድርቅ ያስከተለው ጉዳት ከፍተኛ ነው፡፡ እህል ጠፋ፤ ከብቶች ተጎዱ፣ ሞቱ፡፡
 በዚህ ዓመት የዝናቡ አመጠጣጥ ጥሩ ስለሆነ፣ የእኛም ዝግጅት እንደዚያው ያማረ ነው፡፡ ማሳው አራቴ ታርሷል፣ ዘርና ማዳበሪያ ተገዝቷል፣ አንዴ አርሰን ለመዝራት ዝግጁ ነን፡፡›› ብለዋል፡፡
መንግሥት፣ የግብአት (ምርጥ ዘር፣ ማዳበሪያ…) አቅርቦት ቢያሟላም ጥቂት ችግሮች መኖራቸውን አቶ አደም አልሸሸጉም፡፡ ‹‹ማዳበሪያው ቢቀርብም አምና ስላላረስን መግዣ ገንዘብ አጥሮናል፡፡ ዘርም በግብርና ቢሮ በኩል ቢዘጋጅም እንደየፍላጎታችን አይደለም፤ ለሁሉም አልደረሰም፡፡ ነዋሪው ማዳበሪያና ምርጥ ዘር መግዣ ገንዘብ የለውም፡፡ ወረዳው እያደረገ ያለው ጥረት ቢኖርም ለሁሉም ማዳረስ አይችልም፤ በጣም አነስተኛ ነው፡፡ በድርቁ በጣም ተጎድተን ስለነበር መንግሥት ድጋፍ እንዲያደርግልን እንጠብቃለን፡፡›› በማለት አስረድተዋል፡፡ ስለ ማዳበሪያ ዋጋ መወደድ ሌሎች አርሶ አደሮችም ተናግረዋል፡፡
 አምና በአቶ አደም ማሳ አካባቢ መጠነኛ ዝናብ ጥሎ ስለነበር ብዙ አልተጎዱም፡፡ ‹‹ከሌሎች የተሻልኩ ነኝ›› ይላሉ፡፡ ዘንድሮ የአየር ሁኔታው ጥሩ ስለሆነና በዚሁ ዓይነት ከቀጠለ በሄክታር ከ80-90 ኩንታል እንደሚጠብቁ ገልጸዋል፡ ‹‹አምና ምንም ምርት አልነበረም ማለት ይቻላል፡፡ በሄክታር ከ20-30 ኩንታል ነው የተገኘው፡፡ ካቻምና (2006) ከ80-90 ኩንታል ስላገኘን ዘንድሮም እንደዚያ ነው የምንጠብቀው፡፡›› በማለት አጠቃለዋል፡፡
አቶ ጁሐር ጀማል፤ የአጋርፋ ወረዳ ግብርና ጽ/ቤት ም/ኃላፊ ነው፡፡ ወረዳው ዝናብ አጠር እንደሆነ ጠቅሶ አምና መጀመሪያ ላይ ዝናቡ ጥሩ ስለነበር፣ 12ሺህ ሄክታር መሬት መታረሱን፣ ነገር ግን ወደ ኋላ ላይ ዝናቡ ስለጠፋ ከፍተኛ ጉዳት ማስከተሉን፤ ዘንድሮም በመጋቢትና ሚያዝያ የጣለው ከፍተኛ ዝናብ ባስከተለው ጎርፍ 851  ሄክታር መሬት መጎዳቱን ገልጿል፡፡ የዘንድሮ በልግ ዝናብ አመጣጥና አጣጣል  ጥሩ ነው፡፡ በበልግ የተዘራው እህል በአንድ ማሳ እያደገ፣ በሌላው ደግሞ እየደረቀና እየታጨደ ስለሆነ፣ ከአምናው የተሻለ 300 ሺህ ኩንታል እህል ይገኛል ብሎ እንደሚገምት ተናግሯል፡፡  
አቶ ጁሐር ለመኸሩ ከፍተኛ ዝግጅት መደረጉን፣ መጪውን የአዝመራ ወቅት አስመልክቶ በጽ/ቤቱ ውይይት መደረጉን፣ ለግብርና ባለሙያዎችና ለአርሶ አደሮች ምን ማድረግ እንዳለባቸው፣እንዴት በዘመናዊ መንገድ ማረስ እንደሚገባቸው ሥልጠና መሰጠቱንና የቴክኒክ ድጋፍ መደረጉን ገልጿል፡፡ በወረዳው ካሉት 13,500 አርሶ አደሮች መካከል 93 በመቶ ለሚሆኑ ሥልጠና መሰጠቱን፣ ከታቀደው 18 ሺህ ኩንታል ማዳበሪያ ውስጥ 11 ሺህ ኩንታል በቀበሌ ማኅበራት በኩል በየቀበሌው እንዲደርስ እየተደረገ መሆኑን፣ ከኦሮሚያ ምርጥ ዘር ኢንተርፕራይዝ የተገኘ ምርጥ ዘር በወረዳው በሁለት ማዕከል ቀርቦ አርሶ አደሮች እየገዙ መሆናቸውን፤ በድርቁ ጉዳት የደረሰባቸውና በወረዳው አነስተኛ ገቢ ያላቸው 1,440 አርሶ አደሮች  ተለይተው፣ ከኦሮሚያ አነስተኛና ብድርና ቁጠባ፤ ብድር እንዲያገኙ እየተመቻቸ መሆኑን እንዲሁም ባለፈው ዓመት በድርቅ ለተጎዱ አርሶ አደሮች መንግሥት 4 ሺህ ኩንታል እህል ሰጥቶ መከፋፈሉን ተናግሯል፡፡
ም/ኃላፊው፤ በተለያዩ ምርቶች 89 ክላስተሮች ለማደራጀት አቅደው፣82 ክላስተሮች በማደራጀት ልጠና መሰጠታቸውን፤ በአራት ቀበሌዎች አርሶ አደሩ በገበያ ተፈላጊ የሆኑ ምርቶች እንደሚያመርት፣ አምና በተለያዩ ቀበሌዎች ያባዙት 7,921  ኩንታል ዘር ስላለ፣. ይህንን ዘር ከኦሮሚያ ምርጥ ዘር ኢንተርፕራይዝ ከገዙት ጋር እንዲጠቀሙ እንደሚደረግ ገልጿል፡፡ አንዳንድ አርሶ አደሮች የማዳበሪ ዋጋ ተወዷል ያሉትን አቶ ጁሐር አይቀበለውም፤ እንዲያውም ከአምናው የቀነሰ ነው ብሏል፡፡
ከዘንድሮ እርሻ 13 ሚሊዮን ኩንታል አንጠብቃለን
በዶዶላ ወረዳ ከባድ ዝናብ ጥሎ ኮረብታ ሰር ባለው በቀጨማ ጨፌና ገነታ ቀበሌዎች በ198 ሄክታር መሬት ላይ የተዘራ የስንዴ ማሳያ ያወደመው ሐምሌ 9 ቀን 2008 ዓ.ም ነው፡፡ ዝናቡ ከባድ መሆኑን፣ 2 ኪ.ሜ ከፍ ብሎ የሚገኘውን ወንዝ ድልድይ ሰብሮ ማሳዎቹን ማጥለቅለቁን በአደጋው ማግስት ከባሌ ዞን ስንመለስ በስፍራው ተገኝተን ተመልክተናል፡፡
ወ/ሮ ዲንሾ ብርቢሳ ማሳቸው በጎርፍ ከወደመባቸው አርሶ አደሮች አንዷ ናቸው፡፡ ድጋሚ ጎርፍ መጥቶ እርሻቸውን እንዳያወድም ከቤተሰቦቻቸው ጋር በማሳቸው አናት ቦይ ሲሰሩ ነው ያገኘናቸው፡፡ የወ/ሮ ዲንሾ መሬት 3 ሄክታር ተኩል ነው፡፡ 3 ኩንታል ማዳበሪያ ተጠቅመው ነበር ምርጥ ዘር ስንዴ የዘሩት፡፡ አሁን በእጃቸው ምንም ገንዘብ ያላቸውም፡፡ ወቅቱ ሳያልፍባች መልሰው ለመዝራት የመንግሥትን ድጋፍ ነው የሚጠብቁት፡፡ የ12 ልጆች እናት የሆኑት ወ/ሮ ዲንሾ በምን ያህል ገንዘብ እንዲሸጡ አያስታውሱም እንጂ ከአምናው እርሻ 190 ኩንታል እህል ነው ያገኙት፡፡ጎርፍ የተከሰተው ሌሊት ነው፡፡ ጧት ሰዎች መጥተው የሆነውን ነገሩን፡፡ ከግብርና ባለሙያዎች ጋር መጥተን ስናየው በ198 ሄክታር መሬት ላይ የተዘራው ሰንዴ ወድሟል፡፡ ያለው የዶዶላ ወረዳው ም/አስተዳዳሪና የግብርና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ፌኔት አማን ነው፡፡ እነዚህን አርሶ አደሮች ጊዜው ሳያልፍባቸው መልሰው እንዲዘሩ ወራዳው ዘርና ማዳበሪያ በነፃ ለመስጠት ወስኗል፡፡ ስለዚህ ማሳቸው የወደመባቸውን አርሶ አዳሮች እየለየን ነው ብሏል፡፡
ከዘንድሮ እርሻ 13 ሚሊዮን ኩንታል እህል እንጠብቃለን ያሉት ደግሞ የምዕራብ አርሲ አስተዳደርና የግብርና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ቶላ ገዳ ናቸው፡፡ አቶ ቶላ ስለ አምናው ድርቅ፣ ለዘንድሮው እርሻ አርሶ አደሩ እያደረገ ያለውን ዝግጅት ፤ ስለግብአት  አቆርቦት እንዲህ ሲሉ አጫውተውናል፡፡አምና በምዕራብ አርሲ ዞን ከ12 ወረዳ 7ቱ በድርቅ የተመቱ ነበር፡፡ ሁለት ወረዳዎች ደግሞ በዝናብ ብዛት ተጎድተዋል፡፡ አምናል በድርቅ የተጠቁ 126 ቀበሌዎች ሲሆኑ 307 ሺህ ሕዝብ ተጎድቷል፡፡ ሕዝቡ ከቤቱ እንዳይፈናቀል፤ ከቤቱ ርቆ እዳይሰደድ ከመንግሥትና መንግሥታዊ ካልሆኑ ድርጀቶች ጋር ብዙ ሥራ ሰርተረናል፡፡ ሕዝቡ በምግብ እጥረት እንዳይጎዳ በተለይ ሴቶችና ሕፃናት የምግብ አቀርቦት እንዲያገኙ ተደርጓል፡፡ ዘንድሮ በድርቅ ለተጎዱት ቀበሌዎች ምርጥ ዘርና ማዳበሪ በነፃ ሰጥተናል፡፡ በአጠቃላይ በእኛ ዞን 28 ሚሊዮን ብር ተመድቦ ስንዴ፣ በቆሎ፣ ጤፍ፣ ገብስ፣… የመሳሰሉን እህሎች ገዝተን ለዘር ሰጥተናል፡፡ መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅቶችም ይህን ያህል ገንዘብ አዘጋጅተው 13,600 ኩንታል ምርጥ ዘር በሁሉም ወረዳ አከፋፍለናል፡፡
በአምናው ድርቅ የሞተ ሰው የለም፡፡ በጎርፍ ግን ዘጠኝ ሰዎች ሞተዋል፡፡ 806 አባወራዎች ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ወደ ቤታቸው መመለስ ያልቻሉ 39 አባወራዎች አስፈላጊውን ድጋፍ እያደረግን ነው፡፡ በጎርፍ የተጠቁ ወረዳዎች ሻላ፣ ሰራሮ በከፊል ሻሸመኔ በተወሰነ ደረጃ ደግሞ ዶዶላ እንዲሁም በዚህ ሳምንት የተከሰተ በገደብ አሳሳ ወረዳዎች ነው፡፡ በምርጥ ዘርና በማዳበሪያ አቅርቦ ምንም ችግር የለም ማለት ይቻላል፡፡ የማደበሪያ አቅርቦት ትንሽ ዘግይቶ ነበር፡፡ በአሁኑ ወቀት ከአቅዳችን 91 በመቶ አስገብተን 64 በመቶ ደግሞ አከፋፍለናል፡፡
በምርጥ ዘር በኩል ምንም ችግር የለም፡፡ በዞኑ 252,445 አርሶ አደር አለ፡፡ በበልግ 1.3 ሚሊዮን ኩንታል አንጠብቅ ነበር፡፡ ነገር ግን በድርቁ ምክንያት 900 ሺህ ኩንታል ነው ያገኘነው፡፡ በመኸር 13 ሚሊዮን ኩንታል እህል ለማግኘት አቅደናል፡፡ በዚህ ደግሞ በቂ ዝግጅትና ክትትል አድርገናል፡፡ ለዚህ የክረምት ወቀት 346 ሺህ ሄክታር መሬት የተዘጋጀ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 97 በመቶው ታርሷል፤ 61 በመቶው ተዘርቷል፡፡ ቀሪውን ደግሞ በቀጣይ ጊዜ እንሸፍናለን፡፡›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡

    የደቡብ ሱዳን ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር፣ ባለፈው ሳምንት ከምክትል ፕሬዚዳንትነታቸው ካነሷቸው ተቀናቃኛቸው ሬክ ማቻር ጋር ግንኙነት አላቸው የሚሏቸውን ስድስት ሚኒስትሮች፣ባለፈው ማክሰኞ ከስልጣናቸው ማባረራቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡በአገሪቱ ተቀናቃኝ ሃይሎች መካከል የተደረሰውን የሰላም ስምምነት በሚጻረር መልኩ ሹም ሽር አድርገዋል በሚል ሲተቹ የሰነበቱት የአገሪቱ ፕሬዚደንት ሳልቫ ኬር፤እነዚህን ሚኒስትሮች ማባረራቸው አገሪቱን ወደ ከፋ ቀጣይነት ያለው ግጭት ሊያስገባት እንደሚችል እየተነገረ ነው ብሏል ዘገባው፡፡ ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር ከስልጣናቸው ያባረሯቸው ሚኒስትሮች፡- የአገሪቱ የነዳጅ፣ የከፍተኛ ትምህርት፣ የአገር ውስጥ ጉዳይ፣ የሰራተኞች፣ የውሃ እንዲሁም የመሬትና የቤቶች ልማት ሚኒስትሮች እንደሆኑ የጠቆመው ዘገባው፤ሚኒስትሮቹ እንዲባረሩ ሃሳብ ያቀረቡት ከሰሞኑ በፕሬዚዳንቱ አነጋጋሪ ውሳኔ በምክትል ፕሬዚዳንትነት የተሾሙት ታባን ዴንግ ጋኢ መሆናቸውንም ገልጧል፡፡ባለፉት 2 አመታት በአገሪቱ በተከሰቱ ግጭቶች፣በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ ዜጎች መሰደዳቸውን ያስታወሰው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፤ከሶስት ሳምንታት በፊት በሁለቱ ሃይሎች መካከል ዳግም ግጭት ማገርሸቱን ተከትሎም ተጨማሪ 60 ሺህ ያህል ደቡብ ሱዳናውያን አገር ጥለው ተሰደዋል ማለቱን ዘገባው ገልጧል፡፡

ደራሲ ጄምስ ፓተርሰን በ95 ሚ. ዶላር ቀዳሚነቱን ይዟል
    ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት፤በድርሰት ስራዎቻቸው ከፍተኛ ገቢ ያገኙ የአመቱ የዓለማችን እጅግ ሃብታም ደራሲያንን ዝርዝር በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ ይፋ ያደረገ ሲሆን ባለፉት 12 ወራት ብቻ 95 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ያገኘው ታዋቂው ደራሲ ጄምስ ፓተርሰን በአንደኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል፡፡ በወንጀል ነክ ድርሰቶቹ የሚታወቀው ጄምስ ፓተርሰን፤ ባለፉት ሶስት አመታት በፎርብስ የሃብታም ደራሲያን ዝርዝር ውስጥ ቀዳሚነቱን ይዞ መዝለቁን የጠቆመው መጽሄቱ፤ይሄው ደራሲ በቀጣዩ አመትም ክብሩን እንደጠበቀ ይዘልቃል ተብሎ እንደሚገመት አስታውቋል፡፡
በ2016 የአለማችን ሃብታም ደራሲያን ዝርዝር ውስጥ ሁለተኛ ደረጃን የያዘው 19.5 ሚሊዮን ዶላር ያገኘው የህጻናት መጽሃፍት ደራሲው ጄፍ ኬኒ ሲሆን  ሃሪ ፖተር በሚለው ተከታታይ መጽሃፏ አለማቀፍ ዝናን ያተረፈቺው ጄ ኬ ሮውሊንግ ደግሞ በ19 ሚሊዮን ዶላር ሶስተኛ ደረጃን ይዛለች፡፡ ጆን ግሪሻም በ18 ሚሊዮን ዶላር አራተኛ፣ ስቴፈን ኪንግ፣ ዳንኤላ ስቲልና ኖራ ሮበርትስ ደግሞ በተመሳሳይ በ15 ሚሊዮን ዶላር አመታዊ ገቢ አምስተኛ ደረጃን ይዘዋል፡፡ በዝርዝሩ ውስጥ ከተካተቱት ሌሎች ደራሲያን መካከልም ጆን ግሪን፣ ዳን ብራውንና ቬሮኒካ ሮዝ ይገኙበታል ተብሏል፡፡
የተለያዩ የአለማችን አገራትን ደራሲያን አመታዊ የመጽሃፍ ሽያጭና ገቢ በማስላት የላቀ ገቢ ያገኙ ደራሲያንን ዝርዝር ይፋ የሚያደርገው ፎርብስ መጽሄት፤ባለፉት 12 ወራት ከፍተኛ ገቢ ያገኙ በሚል በዝርዝሩ ያካተታቸው 14 የተለያዩ የአለማችን አገራት ደራሲያን በድምሩ 269 ሚሊዮን ዶላር ማግኘታቸውን አስታውቋል፡፡

የወርቅ ዋጋ መናር ለትዳር ፈላጊ ወንዶች ፈተና ሆኗል ተብሏል
     በግብጽ የወርቅ ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ እየናረ መምጣቱን ተከትሎ፣ የአገሪቱ ወንዶች ለሚያገቧት ሴት የወርቅ ጥሎሽ የሚሰጡበት ባህላዊ ልማድ እንዲቀር ለማድረግ የተጀመረው ዘመቻ ተቀባይነት እያገኘ መሆኑን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ሻብካ በተባለው የግብጻውን ባህላዊ የሰርግ ልማድ መሰረት፣ አንድ ወንድ ሊያገባት ለሚፈልጋት ሴት የወርቅ ጌጣ ጌጦችን መስጠት እንደሚጠበቅበት የጠቆመው ዘገባው፣ አሁን አሁን ግን የወርቅ ዋጋ እየናረ መምጣቱ ለትዳር ፈላጊ ወንዶች ፈተና መሆን መጀመሩን ገልጧል፡፡በግብጽ የአንድ ግራም ባለ 24 ካራት ወርቅ ዋጋ 50 ዶላር ያህል መድረሱን የጠቆመው ዘገባው፤ይህም የትዳር ፈላጊ ወንዶችን አቅም እየተፈታተነ በመሆኑ በማህበራዊ ድረገጾች የወርቅ ጥሎሽ ባህሉ እንዲቀር ዘመቻ እንዲጀመር ምክንያት መሆኑን አስታውቋል፡፡ ዘመቻው መጀመሩን ተከትሎ በሺዎች የሚቆጠሩ ግብጻውያን፣ልማዱ አንዲቀር ድጋፋቸውን ማሳየታቸውን የጠቆመው ዘገባው፤የዘመቻው ደጋፊዎች በወርቅ ምትክ ብር ወይም ሌላ ውድ ያልሆኑ ጌጣጌጦች በጥሎሽ መልክ ቢሰጥ መልካም ነው ሲሉ አስተያየታቸውን እንደሰነዘሩ ገልጧል፡፡የወርቅ ጥሎሽ እንዲቀር ድጋፋቸውን የሰጡ አብዛኞቹ የዘመቻው ተሳታፊዎች ወንዶች ቢሆኑም፣በርካታ ግብጻውያን ሴቶች ይህንን ሃሳብ በመደገፍ ከወንዶች ጎን መሰለፋቸውንም ቢቢሲ ዘግቧል፡፡