Administrator

Administrator

ለጋዜጦች፣ መጽሃፍት፣ መጽሄቶች፣ ደረሰኞች--- ህትመት የሚሆኑ ወረቀቶችን ያመርታል

     “ፒዩርውድ ፐልፕ ፔፐር ኤንድ ፓኬጂንግ” ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ፣ በአንድ ቢሊዮን ብር አጠቃላይ የኢንቨስትመንት ካፒታል ግዙፍ የወረቀትና የማሸጊያ ካርቶን ማምረቻ ፋብሪካ በዱከም አካባቢ ሊገነባ መሆኑን በተለይ ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ አስታወቀ፡፡
በኢትዮጵያውያን፣ በውጭ አገራት በሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና በቻይናውያን ባለሃብቶች የጋራ ጥምረት የተቋቋመው ኩባንያው፤ ፕሮጀክቱን በተመለከተ ከኢንቨስትመንት ኮሚሽን ጋር የመግባቢያ ሰነድ መፈራረሙንና በኦሮምያ ክልል በዱከም ከተማ አካባቢ በሚገኘው የኢንዱስትሪ ዞን፣ ለፋብሪካው ግንባታ የሚውል 68 ሄክታር ቦታ መረከቡን በመጠቆም፣ የፋብሪካው ግንባታ በቅርቡ እንደሚጀመርም ገልጧል፡፡
ግንባታው በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ተጠናቅቆ ማምረት ይጀምራል ተብሎ የሚጠበቀው ፋብሪካው፤ ዘመኑ የደረሰበትን የማምረቻ ቴክኖሎጂ በመጠቀም ጥራት ያላቸው የተለያዩ አይነት ምርቶችን በማምረት በስፋት ለገበያ እንደሚያቀርብ ኩባንያው በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡ ኩባንያው ቀዳሚ ትኩረቱን የሚያደርገው ከውጭ አገራት ጥቅል የመጸዳጃ ቤትና የህትመት ወረቀቶችን እያስመጡ በጥሬ እቃነት ለሚጠቀሙ የአገር ውስጥ ፋብሪካዎች የተለያዩ አይነት ጥቅል ወረቀቶችን በማቅረብ ላይ እንደሆነ የጠቆሙት የኩባንያው ስራ አስኪያጅ አቶ ማሂር ኢስማኤል፤ ፋብሪካው በአመት 32 ሺህ 500 ቶን ያህል የተለያዩ አይነት የንጽህና መጠበቂያና የህትመት ወረቀቶችን እንዲሁም የማሸጊያ ካርቶኖችን የማምረት አቅም እንደሚኖረውም ገልጸዋል፡፡
ፕሮጀክቱ ለ700 ያህል ዜጎች ቋሚ የስራ እድል እንደሚፈጥር የጠቆሙት ስራ አስኪያጁ፤ ፋብሪካው የሸንኮራ አገዳ ተረፈ ምርትንና ጥቅም ላይ የዋሉ ወረቀቶችን መልሶ በጥሬ እቃነት የሚጠቀም በመሆኑ ለአካባቢ ጥበቃ የራሱን ሚና እንደሚጫወትም ገልጸዋል፡፡ ለንጽህና መጠበቂያና ለመጸዳጃ ቤት አገልግሎት ከሚውሉ ለስላሳ ወረቀቶች በተጨማሪ ለጋዜጦች፣ ለመጽሃፍት፣ ለመጽሄቶች፣ ለደረሰኞች፣ ለቀን መቁጠሪያዎችና ለሌሎች የህትመት ስራዎች የሚውሉ የተለያዩ አይነት ወረቀቶችን እንዲሁም የማሸጊያ ካርቶኖችን እያመረተ ለገበያ የሚያቀርበው ፋብሪካው፤ ለአገር ውስጥ የወረቀት አምራቾች ጥቅል ወረቀቶችን የማቅረብ እቅድ እንዳለውም ተነግሯል፡፡
በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ የመጣውን የወረቀት ፍላጎት በአገር ውስጥ ምርት መሸፈን ባለመቻሉ፣ አገሪቱ የወረቀት ምርቶችን በከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ከውጭ አገራት እየገዛች ለመጠቀም ተገድዳ መቆየቷን የጠቆሙት አቶ ማሂር፤ የዚህ ግዙፍ ፋብሪካ መገንባት ለወረቀት ግዢ የሚወጣውን በመቶ ሚሊዮኖች ዶላር የሚቆጠር የውጭ ምንዛሬ በማዳን ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረውም ገልጸዋል፡፡

Saturday, 24 December 2016 12:46

የፖለቲካ ጥግ

- ፖለቲካ ከፊዚክስ የበለጠ አስቸጋሪ ነው፡፡
     አልበርት አንስታይን
- ፖለቲኞች የትም ቦታ አንድ ናቸው፡፡ ወንዝ በሌለበትም እንኳን ድልድይ ለመገንባት ቃል ይገባሉ፡፡
     ኒክታ ክሩስቼቭ
- እውነት በአብላጫ ድምፅ አይወሰንም፡፡
     ዱግ ግዊን
- ኮንሰርቫቲቭ፤ምንም ነገር ለመጀመሪያ ጊዜ መደረግ እንደሌለበት የሚያምን ሰው ነው፡፡
     አልፍሬድ ኢ.ዊጋም
- አንዳንድ ሰዎች ለመርሃቸው ሲሉ ፓርቲያቸውን ይለውጣሉ፤ ሌሎች ደግሞ ለፓርቲያቸው ሲሉ መርሃቸውን ይለውጣሉ፡፡
    ዊንስተን ቸርቺል
- ፖለቲካ ጨዋታ ሳይሆን ከባድ ሥራ ነው፡፡
    ዊንስተን ቸርቺል
- ለአሜሪካ ነፃነት ትልቁ አደጋ ህገ መንግስቱን ችላ የሚል መንግስት ነው፡፡
    ቶማስ ጀፈርሰን
- ሁሉም ሰዎች ሲፈጠሩ ተመሳሳይ ናቸው - ከሪፐብሊካኖችና ዲሞክራቶች በስተቀር፡፡
    ግሮቾ ማርክስ
-የማታ ማታ የምናስታውሰው የጠላቶቻችንን ንግግር ሳይሆን የወዳጆቻችንን ዝምታ ነው፡፡
    ማርቲን ሉተርኪንግ
- በፖለቲካ፣ ምላሽ ያልተሰጠው ውሸት፣ በ24 ሰዓት ውስጥ እውነት ይሆናል፡፡
   ዊሊ ብራውን
- በፖለቲካ ውስጥ አለመሳተፍ ከሚያስከትላቸው ቅጣቶች አንዱ ካንተ ባነሱ ሰዎች መተዳደርን ነው፡፡
   ፕሌቶ
- በዝግታ እራመዳለሁ፤ ነገር ግን ፈፅሞ ወደ ኋላ አልራመድም፡፡
    አብርሃም ሊንከን
- ልጆቼ ሂሳብና ፍልስፍና የማጥናት ነፃነት እንዲያገኙ፣ እኔ ፖለቲካና ጦርነት ማጥናት ይኖርብኛል፡፡   
   ጆን አዳምስ

Sunday, 25 December 2016 00:00

የፍቅር ጥግ

- ወዳጆች ፍቅራቸውን የሚያሳዩት በደስታ ጊዜ አይደለም፤ በመከራ ጊዜ ነው፡፡
     ዩሪፒዴስ
- ፍቅር የሚባለው የሌላው ሰው ደስታ ከራስህ ደስታ ሲልቅብህ ነው፡፡
    ኤች.ጃክሰን ብራውን ጄአር.
- ሁሉንም ውድድ፤ጥቂቶችን እመን፤ በማንም ላይ ክፉ አትስራ፡፡
    ዊሊያም ሼክስፒር  
- ህይወትን ከወደድካት፣ መልሳ እንደምትወድህ ተገንዝቤአለሁ፡፡
    አርተር ሩቢንስቴይን
- በፍቅር ለመውደቅህ ስበትን ሰበብ ማድረግ አትችልም፡፡
    አልበርት አንስታይን  
- አንዳንዴ ልብ ለዓይን የተሰወረውን ያያል፡፡
    ኤች. ጃክሰን ብራውን ጄአር  
- አንድ ሰው የሚፈቀረው ስለተፈቀረ ነው፡፡ ለማፍቀር ምክንያት አያስፈልግም፡፡
    ፓውሎ ኮልሆ
- ህይወት መዝሙር ነው - ዘምረው፡፡
 •  ህይወት ጨዋታ ነው - ተጫወተው፡፡          
 • ህይወት ፈተና ነው - ተጋፈጠው፡፡
 • ህይወት ህልም ነው - እውን አድርገው፡፡
 • ህይወት መስዋዕት ነው - ሰዋው፡፡
 • ህይወት ፍቅር ነው - አጣጥመው፡፡
     ሳይ ባባ
- የድሮ ነገሮች ሁሉ እወዳለሁ - የድሮ ጓደኞች፤ የድሮ ዘመን፣ የድሮ ባህርይ፣ የድሮ መፃህፍት፣ የድሮ ወይን ጠጅ፡፡
    ኦሊቨር ጎልድስሚዝ  
- ፍቅር አንደ ቫይረስ ነው፡፡ በማንኛውም ጊዜ በማንም ሰው ላይ ሊከሰት ይችላል፡፡
    ማያ አንጄሎ  
- ፍቅር እውነተኛ እጣ ፈንታችን ነው፡፡ የህይወትን ትርጉም ለብቻችን አናገኘውም። ከሌሎች ጋር ሆነን እንጂ፡፡
    ቶማስ ሜርቶን
- ሰዎች ይወዱኛል፡፡ ደግሞ ታውቃላችሁ… በጣም ስኬታማ ነኝ፡፡ ሁሉም ይወደኛል፡፡
    ዶናልድ ትራምፕ  
- በሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች ያለ ፍቅር ኖረዋል፤ አንድም ሰው ግን ያለ ውሃ አልኖረም፡፡
   ደብሊው.ኤች.ኤዩደን
- የተገኘነው ከፍቅር አብራክ ነው፤ ፍቅር እናታችን ናት፡፡
    ሩሚ  

Sunday, 25 December 2016 00:00

የዘላለም ጥግ

(ዝነኞች በመሞቻቸው ሰዓት የተናገሩት)

· ‹‹የመጨረሻ ቃል የሚያስፈልገው በህይወት ሳሉ በቅጡ ሳይናገሩ ለቀሩ ጅሎች ነው፡፡››
      ካርል ማርክስ (ፈላስፋ)  
· ‹‹ከሸክላ የተገነባች ሮም አገኘሁ፤ እምነበረዷን ሮምን ትቼላችሁ እሄዳለሁ፡፡››
      አጉስተስ ቄሳር
   (የመጀመሪያው የሮማ ንጉስ፣ ለህዝቡ የተናገረው)
· ‹‹ለመሞት ቅንጣት ታህል አልፈራሁም።››
      ቦብ ማርሊ (ሙዚቀኛ)  
· ‹‹እግዚአብሔርንና የሰው ልጅን አስቀይሜአለሁ፤ ምክንያቱም ሥራዬ ሊኖረው የሚገባው የጥራት ደረጃ ላይ አልደረሰም››  
     ሊዮናርዶ ዳ ቪንቺ  (ፈልሳፊና ሰዓሊ)
· ‹‹ዛሬ ማታ እሄዳለሁ››
     ጄምስ ብራውን (ሙዚቀኛ)
· ‹‹ሁሉም ደስተኛ ነው? ሁሉም ሰው ደስተኛ እንዲሆን እሻለሁ፡፡ እኔ ደስተኛ መሆኔን አውቃለሁ››
    ኢቴል ባሪሞር (ተዋናይት)
· ‹‹አሁን ልተኛ ነው፤ ደህና እደሩ››
    ሎርድ ጆርጅ ባይሮን (ፀሐፊ)
· ‹‹መግባት አለብኝ፤ ጉሙ እየገለጠ ነው››
    ኢሚሊ ዲክንሰን (ገጣሚ)  
· ‹‹እዚያ በጣም ውብ ነው››
   ቶማስ አልቫ ኤዲሰን (ፈልሳፊ)  
· ‹‹አዎ ከባድ ነው፤ ኮሜዲ የመስራት ያህል ግን አይከብድም››   (መሞት ከባድ እንደሆነ ተጠይቆ የመለሰው)
    ኢድመንድ ግዌን (ተዋናይ)
· ‹‹ጥቁር ብርሃን ይታየኛል››
    ቪክቶር ሁጎ (ፀሐፊ)  
· ‹‹ንግስት ነኝ፤ ነገር ግን ክንዶቼን የማንቀሳቀስ ሃይል የለኝም››
    ሉይስ (የፐርሽያ ንግስት)
· ‹‹ምስኪን ነፍሴን ጌታ ይርዳት››
    ኤደጋር አላን ፓ (ፀሐፊ)
· ‹‹ምንም ያልተበረዘ 18 መለኪያ ውስኪ ገልብጫለሁ፤  ይሄ አዲስ ክብረ ወሰን ይመስለኛል….››
    ዳይላን ቶማስ (ገጣሚ)

Sunday, 25 December 2016 00:00

አስገራሚ እውነታዎች!!!

· በቀን ለ24 ሰዓት እየቆጠራችሁ፣1 ትሪሊዮን ላይ ለመድረስ፣
 • 31ሺ 688 ዓመት ይፈጅባችኋል፡፡
· የኤሌክትሪክ ወንበር የተፈለሰፈው በአንድ የጥርስ ሀኪም ነው፡፡
· የዶሮ ረዥሙ የተመዘገበ የአየር ላይ በረራ 13 ሰከንድ ነው፡፡
· የጥንት ግብፃውያን ከድንጋይ በተሰራ ትራስ ላይ ይተኙ ነበር፡፡
· እስከ 1976 ዓ.ም (እኤአ) በአሜሪካ ፍራንክሊን በሚል የሚጠራ ግዛት ነበር፡፡
• ዛሬ ያ ግዛት ቴኒዝ በመባል ይታወቃል፡፡
· በዓመት ከ10 ሺ በላይ አዕዋፋት ከመስተዋት መስኮቶች ጋር በመጋጨት ይሞታሉ፡፡
· በምድር ላይ ከአንድ ሚሊዮን በላይ የእንስሳት ዝርያዎች አሉ፡፡
· ከአራት አሜሪካውያን አንዱ በቴሌቪዥን መስኮት ታይቷል፡፡
· አምፑል ፈልሳፊው ቶማስ ኤዲሰን ጨለማን ይፈራ ነበር፡፡
· ሰውነታችን በሰከንድ 15 ሚሊዮን ቀይ የደም ሴሎችን እየፈጠረ ይገድላል፡፡
· ማር አይበላሽም፡፡ 3ሺ ዓመት ያስቆጠረ ማር ለምግብነት ይውላል፡፡

    ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ንሥርና አንዲት ቀበሮ እጅግ የሚዋደዱ ጓደኞች ይሆናሉ፡፡ አንዳችን ላንዳችን የምናስብ፣ በቅርብ የምንተጋገዝ ወዳጆች መሆን አለብን ተባብለው በአንድ ዛፍ ዙሪያ መኖር ይጀምራሉ፡፡ እርስ በርሳቸው በቅርብ በተያዩ ቁጥር የበለጠ ጓደኛሞች እንሆናለን ብለው አሰቡ፡፡
ንሥር፤
‹‹አደራ ቀበሮ፤ እኔ በሌለሁ ጊዜ ልጆቼን ላንቺ ነው ጥዬልሽ የምሄደው፡፡ አንቺም ራቅ ያለ ቦታ የመሄድ አጋጣሚ ቢመጣብሽ ላንቺ ልጆች እኔ አለሁልሽ›› አለች፡፡
ቀበሮም፤
‹‹አይዞሽ፤ እኔም አንቺ ምንም ነገር አጋጥሞሽ ልጆችሽን መጠበቅ ቢያስፈልግ ምንጊዜም ከጎንሽ ነኝ፡፡›› አለቻት፡፡
ስምምነታቸው እንደተጠበቀ ሆኖ፤ ንሥር በረዥሙ ዛፍ ጫፍ ላይ ጎጆዋን ሠራች፡፡ በአንፃሩ ቀበሮ ከዛፉ ግርጌ ችፍግ ባለው ቁጥቋጦ ማህል ሠፈረች፡፡ እዚያም ግልገሎችን ፈለፈለች፡፡ ብዙ ጊዜ ከንሥር ጋር በጎረቤትነት አብረው ኖሩ፡፡
አንድ ቀን፤ ቀበሮ ለግልገሎቿ ምግብ ፍለጋ ራቅ ወዳለ ቦታ ሄደች፡፡
ይህን ያስተዋለችው ንሥር፤ ወደ ዛፉ ግርጌ በርራ ወርዳ፡- እሷም ለጫጩቶቿና ለራሷ ምግብ ያሻታልና፤ የቀበሮን ግልገሎች አንጠልጥላ ወደ ዛፉ ጫፍ ወጣች፡፡
ቀበሮ ተመልሳ የሆነውን ሁሉ አየች! ሆኖም ዛፉ ጫፍ ላይ መውጣት እንደማትችል ስትገነዘብና በምንም መንገድ መበቀል እንደማይሆንላት ስታስብ ከልቧ አዝና ተቀመጠች፡፡ በየጊዜው ቀና ብላ መራገሟን ግን ቀጠለች፡፡
ንሥርም፤
‹‹እመት ቀበሮ፤ ምን ሆነሽ ነው የእርግማን መዓት የምታወርጂው?›› ስትል ጠየቀቻት። እንዳልገባት ሆና ለነገሩ እንግዳ ለመምሰል ነው፡፡
ቀበሮም፤
‹‹አይዞሽ ምንም ካላረግሽ እርግማኔ ሊያስፈራሽ አይገባም፡፡ እኔ እማምነው ግን አንድ ነገር ብቻ ነው፡፡››
ንሥር፤
‹‹ምን?›› ብላ በችኮላ ጠየቀች፡፡
‹‹አለመታመንን የሚያጠብቅ ወንጀለኛ፤ ከሰው ልጅ ቅጣት ሊያመልጥ ይችላል፡፡ የአምላክን ቅጣት ግን ፈፅሞ ለማምለጥ አይችለም!›› አለቻት፡፡
እመት ቀበሮ ገና ይሄን ብላ ከመጨረሷ፤ የሆኑ ሰዎች አንዲት ፍየል ወደ ዛፉ አቅራቢያ እየነዱ መጡ፡፡ ፍየሏን በማረድ ለመስዋዕትነት ሊያቀርቡ ነው ዓላማቸው፡፡ አረዷትና ሥጋዋን መጥበስ ጀመሩ፡፡ ንሥር ዛፍ ላይ ሆና የሚሆነውን ስታይ ቆይታ፣ ቁልቁል በርራ አንዱን ሙዳ ከነእሳቱ መንትፋ ወደ ጫጩቶቿ በርራ ገባች፡፡ ይሄኔ አንድ ያልታሰበ ነገር ተከሰተ፡፡ ከባድ አውሎ ንፋስ ተነሳ፡፡ ከሳር የተሰራው የንስሯና የቤተሰቧ ጎጆ በእሳት ተያያዘ፡፡ የንስሯ ትናንሽ ጫጩቶች ግማሽ በግማሽ በእሳት ተጠብሰው፣ ከዛፉ ላይ ወድቀው ቀበሮዋ ፊት አረፉ፡፡ እመት ቀበሮም፤ ንስሯ ዐይኗ እያየ፤ ተጠብሰው የመጡላትን ጫጩቶች ቅርጥፍ አድርጋ በላቻቸው!!
*         *       *
በመተማመን ላይ የተመሰረተን የቆየ ወዳጅነት ማፍረስ ዋጋ ያስከፍላል፡፡ ከሰው ባይገኝ ከመለኮት በቀሉ ተግባራዊ ይሆናል፡፡ የሰው በልቶ አያድሩም ተኝቶ የሚለው ተረት የዋዛ አይደለም። ለምናደርገው ነገር ሁሉ ምክንያታዊ መሆን ብቻ ሳይሆን ቀና ልቦና ልንጨምርበት ይገባል፡፡ ምክንያቱም የምንፈጥረው ሰበብ ምንም ዓይት አመክኖአዊ ስሌት ይኑረውና ያሳምን፤ ውስጡ ተንኮል ሊኖርበት ይችላልና ነው፡፡ ተንኮል ያለበት ነገር ቢያንስ ውሎ አድሮ ህሊናን ይወጋል፡፡ ቃልን አለማክበር የሀገራችን አባዜ ሆኖ ቆይቷል፡፡ አብዛኞቹ ጥያቄዎቻችን እምንመልሰው ለጊዜው ከውጥረት ለመገላገል ከሆነ፣ ስር የሰደደው ችግር ሳይነቀል ይቀራል። መፍትሄአችን ዋናው መንገድ ሲበላሽ መተንፈሻ ተብሎ እንደሚሰራው መጋቢ መንገድ ብቻ ሊሆን አይገባውም። ምነው ቢሉ፤ መተንፈሻ ብለን የሰራነው መንገድ ዋና ሆኖ ሊቀር ይችላልና! ከዚያ ወዲያ አውራ ጎዳናውን እንረሳዋለን፡፡
የዚህ አይነቱ አሰራር በየቦታው ሲከሰትና ሲጠራቀም አገር - ሙሉ የመንገድ ችግር ያጥለቀልቀናል፡፡ ስለዚህ የዋናና የማስተንፈሻ መፍትሄዎቻችንን ባህሪ መመርመር ትልቅ ቁም ነገር መሆኑን እንገንዘብ፡፡
ችግሮቻችንን ለማስወገድ ጥረትና ትግል የማስፈለጉን ያህል፣ ውስጣዊ ዲሞክራሲን ያለ አንዳች ሽንገላና ይስሙላ መገንባት አማራጭ የለውም፡፡ አለበለዚያ ዋጋ ያስከፍለናል፡፡ በማናቸውም ጠንካራ የትግል እንቅስቃሴ ባለበት ቦታ ሁሉ ሁለት መሰረታዊ አካሄዶች ተጠቃሽ ናቸው። እነዚህም ውስጠ ፓርቲ ትግልና በፓርቲዎች መካከል የሚደረጉ ትግሎች ናቸው፡፡ እነዚህን በድርጅቶችም አናፅሮ ማየት አይከብድም፡፡ (ፈረንጆቹ፣ በተለይም የጥንት አበው ፖለቲከኞች፤ Inter - party and Intra - party struggle የሚሉት መሆኑ ነው፡፡)
ስም ተግባር አይሆንም፡፡ ራስን ማየትን የመሰለ ነገር የለም፡፡ it is all nomenclature, but it is practice that matters - ከስሙ ምን አለህ፤ ዋናው ተግባር ነው እንደማለት ነው፡፡ “ግምገማ”፣ “ውይይት”፣ “ተሀድሶ”፣ “ጥልቅ - ተሃድሶ” … ወዘተ ስሞችና የስም ማሻሻያዎች ብቻ እንዳይሆኑ ተግባራቸውን እንፈትሽ! ከአንደበት ወጥተን ድርጊትን እናድምቅ፡፡ የሀገራችን ፍቱን ጉዳይ የሀብትና የስልጣን ፍትሃዊ ድልድል ነው! መፍትሄዎችን ለነገ አንበል (Procrastination):: የእኔ ጥፋት አይደለም፤ የውጪ ኃይሎች ነው አንበል (No externalization) በሌሎች አናሳብ (No blame - shifting) በአዲሱ የወጣቱ ትውልድ እንመን (The new is invincible) የመንግስት ባለስልጣናት ንግድ  ውስጥ እንዳይገቡ እንታገል (fight bureaucratic capitalism)፡፡ የሁሉም መጠቅለያ ግን ህዝብን የሚያሳትፍ ዲሞክራሲን ዕውን ማድረግ ነው!! አሮጌውን ሥርዓት መታገል ግድ ነው፡፡ አዲሱ እንዲፈልቅ መሳል ተገቢ ነው፡፡ (Fight conservatism Accept the invincibility of the new) ዋናው አገር የሚያድን ይሄ ነው፡፡ ‹‹ሁለት ባላ ትከል፣ አንዱ ቢሰበር ባንዱ ተንጠልጠል›› ዛሬ አያዋጣም፡፡ ያ ከሆነ፤ ‹‹አሮጊት ሚስቱ ጥቁር ፀጉን ስትነቅል፣ ወጣት ሚስቱ ነጭ ፀጉሩን ስትነቅል፤ መላጣ ሆነና አረፈው!›› የሚለው ተረት ዕውን ይሆናል፡፡ በወጉ እንጓዝ! አገር በወጉ እንድትለወጥ መላ እንምንታ!

Sunday, 25 December 2016 00:00

ስታድዬሞቻችን ያዋጣሉ?!

 • የመሀመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ ስታድዬም ጥር 6 በወልዲያ ከተማ ይመረቃል፡፡
                  • በኢትዮጵያና በኢትዮጵያውያን ስታድዬሞች ይገነባሉ፡፡ ሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ

       በሳምንቱ አጋማሽ ላይ በሸራተን አዲስ የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ቺፍ ኤክዚዮከቲቭ አፊሰር ዶክተር አረጋ ይርዳው ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተው ነበር፡፡ መግለጫው በክቡር ዶክተር ሼህ መሀመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ የገንዘብ ወጭ ግንባታው ተጠናቅቆ፣ በጥር 6 በወልዲያ ከተማ የሚመረቀውን አዲስ ስታድዬም ይመለከታል፡፡ መሀመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ ስታድየም እና የስፖርት ማዕከል ተብሎ ተሰይሟል፡፡ ዶ/ር አረጋ ይርዳው እንደገለፁት ስታድየሙ ስያሜውን ያገኘው በከተማው ህዝብ ውሳኔ ነው፡፡  ስታድዬሙ በጥር 6 /2009 ዓ.ም በይፋ ከመመረቁ በፊት በአጠቃላይ 567 ሚሊየን ብር ወጭ ሆኖበታል፡፡ በወጭው ከፍተኛነት በኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ የሚጠቀስ ይሆናል። ‹‹ስታድዬሙ የኢትዮጵያ ህዝብ ሃብት  ነው›› ያሉት ዶ/ር አረጋ፤ ‹‹ለዞኑ፣ እና ለከተማው መስተዳድር በኃላፊነት የሚሰጥ፣ የህዝብ ንብረት  ይሆናል›› ብለዋል፡፡  ወልዲያ ከአዲስ አበባ 520 ኪ.ሜ ርቀት ላይ ትገኛለች፡፡  በተራራ የተከበበች ውብና የደጎች ከተማ ይሏታል፡፡  የወልዲያ ህዝብ ለስፖርት ያለው ፍቅር የእህል ውሃ ያህል ነው፡፡ ስታድዬሙ ሊሠራ የቻለው በከተማው ህዝብ በተቆሰቀሰ ፍላጎት ነበር። በመጀመርያ በተደረገው እንቅስቃሴ የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት ተድርጎ እስከ 30 ሚሊዮን ብር  ተሰባስቧል፡፡ ይህ ገንዘብ በቂ አልነበረም፡፡ እናም በሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ አማካኝነት በሸራተን አዲስ ሌላ የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ተዘጋጀ፡፡  ‹‹የወልዲያ ልጆች ስታድዬሙን እኔ እገነባለሁ። ለዶ/ር አረጋ ደግሞ ኃላፊነቱን ሰጥቸዋለሁ፡፡›› በማለት ሼህ መሀመድ 100 በመቶ ወጭውን በመሸፈን እንደሚያሰሩ ቃል ገቡ፡፡ ከዚያም የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ፕሮጀክቱን የመነሻ ዲዛይኑን በመቀየር በዕጥፍ ዋጋ በፊፋ መስፈርቶች የተቀረፀ ዲዛይን  በድጋሚ አሠራ፡፡
ኦርጋኒኩ፤ መሃመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ ስታድዬም
የመሀመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ ስታድየም በወልዲያ ከተማ መቻሬ ሜዳ በተባለው ቦታ 177 ሺ ካ.ሜ  ላይ ተቀምጧል፡፡ ከባህር ወለል በላይ 2000 ሜት ከፍታ ላይ የተገነባው ስታድዬሙ በዘመኑ ቴክኖሎጂ የታነፀ ሲሆን ከበጋ እስከ ክረምት ውድድሮችን ማስተናገድ ይችላል። 25115 ወንበሮች ላይ ተመልካቾች የሚይዝ ሲሆን ሙሉ ለሙሉ የተሰሩት በአገር ውስጥ ነው፡፡  በኢትዮጵያ ዙሪያ ገጠም የሆነ ጥላ ፎቅ የተሰራለት የመጀመርያው ስታድዬምም ሆኗል፡፡ በሚያስፈልግ መጠን ብርሃን ሙቀት የሚሰጥና የሚቀንስ  ነው፡፡  በዙርያው ከ156 በላይ ፓውዛ መብራቶች ተገጥመውበታል፡፡ የፊፋን መስፈርት ሙሉ ለሙሉ ያሟላ ነው፡፡ የመሮጫ ትራክም ያለው ሲሆን በዘመናዊ ደረጃ የተዘጋጀው ይህ የአትሌቲክስ ትራክ በመሙ እስከ 8 አትሌቶችን በአንድ የልምምድ መርሃ ግብር ሊያስተናግድ የሚችል ነው፡፡ ዘመናዊ ሜዳ በአንድ ጊዜ አራት ቡድኖች ያስተናግዳል፡፡ ጨዋታዎች በተከታታይ ሊደረጉበት ይችላሉ፡፡ አራት የመልበሻ ክፍሎች እና ሁለት የማሟሟቂያ ሜዳዎች ተሰርተውለታል፡፡ በተጨማሪ ልዩነት የሜዳው ሣር ነው፡፡ ከው ዘርያ ጋር የተዳቀለ የሳር ተከላ ተደርጎለታል። ከሣሩ ስር ባንቧዎች ተቀብረዋል፡፡ ውሃ የሚቋጥር ሜዳ አይሆንም፡፡ በስታዲየሙ ውስጠኛ ክፍል ሁለት ግዙፍ ስክሪኖች ተገጥመዋል፡፡ ሁለት የልዩ እንግዶች (ቪአይፒ) ቦታዎች ተዘጋጅተውለታል፡፡ አንደኛው በመስታውት የተከለለና ለደህንነት አስተማማኝ ሲሆን ሌላኛው ደግሞ መስታውት የሌለው የቪአይፒ መቀመጫዎች ስፍራ ነው፡፡8 ሳውንድ ፕሩፍ ስቱድዮች ያሉት  ሚዲያ ትሪቢዮን አለው። በውስጡ ከ300 በላይ መኪኖች ያቆማል፡፡ የመብረቅ መከላከያ ተገጥሞለታል፡፡  10 በሮች አሉት፡፡ 7 አምቡላንስ ያስገባሉ የአካባቢውን ባህል፣ አኗኗር ታሪክ ለመግለፅ እንዲያመች በሮቹ ስም ተሰጥቶቸዋል፡፡ ለምሳሌ ዳና፣ ላሊበላ…  እንደማዕከልም የመቀጠል ተጨማሪ ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ ሌሎች መሰረተ ልማቶች ስላሟላ ነው።  በውጭኛው ስታድየም ክፍል የዋና ገንዳ፣ የቅርጫት ኳስ፣ መረብ ኳስ፣ እጅ ኳስ እና የሜዳ ቴኒስ ሜዳዎች እንዲሁም ለ34 ሰዎች የሚሆን የእንግዳ ማረፍያ አካቷል፡፡ በዙርያው ከመቶ በላይ የንግድ ሱቆች የተዘጋጀለትም ነው፡፡ ስታድየም የሄሊኮፕተር ማረፍያ፣ በቂ የመኪና ማቆምያ እና ውብ አረንጓዴ ቦታዎች አሟልቷል፡፡ በ2009 ዓም ፕሪሚዬር ሊግን የተቀላቀለው ወልድያ ስፖርት ክለብ በዚሁ ዘመናዊ ስታድየም የሚጫወት ሲሆን ከባህርዳር ስታድዬም ቀጥሎ በክልሉ ሁለተኛው ስታድዬም ሆኖ ይመዘገባል፡፡የወልዲያ ስፖርት ክለብ በሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ይደገፋል፡፡ ስታድዬሙ ከማለቁ በፊት በመልካ ቆሬ ስታድዬም ይጫወት ነበር፡፡ ወደ ፕሪሜርሊጉ ማለፉን ተከትሎም በሚድሮክ ዘርፈ ብዙ ድጋፍ እየተሰጠ ነው፡፡  የመሀመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ ስታድዬም በጥር 6 ተመርቆ ስራውን ከጀመረ በኋላ ክለቡ ሜዳው አድርጎ ይጫወትበታል፡፡ ሚድሮክ ቴክኖሎጂ የክለቡን ሎጎ አሰርቷል፡፡ የስፖርት ትጥቅ፣ የመጓጓዣ አውቶብስ  ድጋፎች ከማረጉም በላይ በአዲስ አበባ የተጨዋቾች ካምፕ አዘጋጅቶ አደራጅቶታል፡፡
በጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የመሐመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ ስታድዬም ኦርጋኒክ ነው በማለት ዶ/ር አረጋ ደጋግመው ይናገሩ ነበር፡፡ ስታድዬሙ በስፖርት መሠረት ልማት ተምሳሌት የሚሆንበት ብዙ ውጤቶች ማስመዝገቡን ሲያብራሩ እንጅ ኦርጋኒክ ያሉት ያለምክንያት አልነበረም። በኢትዮጵያ አቅም የተገነባ ስለሆነ ነው፡፡ ከ95 በመቶ በላይ በስታድዬሙ ግንባታ ላይ የሠሩት መሃንዲሶች እና ሌሎች ባለሙያዎች፣ 90 በመቶ  የግንባታ ቴክኖሎጂዎችና ሌሎች ቁሳቁሶች በአገር ውስጥ በመመረታቸው ነበር፡፡ ለኢትዮጵያውያን በኢትዮጵያ የተሰራ በመሆኑ ስታድዬሙ ኦርጋኒክ ነው የሚሉት ዶክተር አረጋ ይርዳው  የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ አባል ከሆኑ 25 ኩባንያዎች፤ በተለይም 10 ያህሉ በአጋርነት ተሰልፈው ፕሮጀክቱን በ4 ዓመታት ውስጥ በማከናወን ስታድዬሙ  ሙሉ ለሙሉ ተገንብቶ ሊያበቃ መቻሉን ገልፀዋል፡፡ ሼህ አላሙዲ ገንዘብ መድበዋል። ሁዳ ሪል ስቴት ዋናው የኮንስትራክሽኑ ስራ ተቋራጭ ነበር።  ኩባንያዎቹ በየዘርፉ የኮንትራት ስራ እየተሰጣቸው ገንብተውታል፡፡ የስራ ልማዳቸውን አሳድገውታል፡፡፡ የሙያተኞች ብቃት ተሻሽሏል፡፡ በአገር በቀል መሀንዲሶች ለስታድዬም እና ሌሎች የስፖርት መሰረተ ልማት ግንባታዎች ኢትዮጵያዊ አቅም ተፈጥሯል፡፡ ከወልዲያው ስታድዬም ግንባታ በኋላ ሚድሮክ ሌላ ግንባታ ኮንትራት ለማግኘት ፈልጎ አልተሳካለትም፡፡ ወደፊት ዕድሎች እንደሚፈጥሩ እምነት ግን አለ በስታዲዬም ግንባታ የዕውቀት ሽግግር ለማድረግ ፍላጎት አለን ብለዋል፡፡ ቺፍ ኤክሲኪዩቲቭ ኦፊሰሩ በኢትዮጵያና በኢትዮጵያውያን 50 እና 60 ሺ ተመልካች የሚይዙ ስታዬሞች መገንባት ይቻላል፤ ያስፈልጋልም ብለዋል፡፡
በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ከአዲስ አድማስ ለሚድሮክ ቴክኖሎጁ ግሩፕ ኤክስኪዩቲቭ  ኦፊሰር ዶ/ር አረጋ ይርዳው  የቀረቡ 3 ጥያቄዎች የሚከተሉት ነበሩ፡፡  ስታዲየሞች በብዛት ያስፈልጋሉ ወይ፣ ከሆነስ በየትኞቹ ከተሞችና ክልሎች የሚለው የመጀመርያ ነበር..፡፡  ዶ/ር አረጋ ምላሽ ሲሰጡ “መቼ ነካውና፡፡ አገሪቷ ውስጥ ምን ስታድዬም አለና፡፡ 100 ሚሊዮን ህዝብ ያለባት - 70 በመቶ ወጣት ለሆነበት አገር። ስታድዬም ብዙ ነው የሚያስፈልገን፣ ለጊዜው ተጫዋች ላይኖሩ ይችላሉ፡፡ በየምሽቱ እንደምናየው የማንቸስተር፣ የአርሰናል ስታድዬም አይሟላ ይሆናል፡፡ የአቅም ጉዳይ፣ የስፖርቱ እድገት፣ የተመልካችነት ባህል መጨመር እነዚህን ሁሉ የሚጀምር ነው፡፡ እስከመቼ ድረስ ነው፡፡ በቴሌቪዥን ብቻ የሌላውን አገር ጨዋታ እያየን የምንዘልቀው።  ስታድዬሞች የት ይገንቡ፤ በሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጥናት ተደርጎበታል፡፡  በእያንዳንዱ ክልልና ከተማ ልክ ዩኒቨርሲቲዎች እንዳሉ ስታዲዬሞች መኖር አለባቸው።››
የወልዲያ ከተማ አየር ሁኔታን በተመለከተ እና መቼ ዓለም አቀፍ ጨዋታ ሊያስተናግድ ይችላል የሚሉት ሌሎቹ ከአዲስ አድማስ የቀረቡ  ጥያቄዎች ናቸው፡፡ ዶ/ር አረጋ በመጀመርያ ምላሻቸው ስለአየር ሁኔታው ‹‹የኢትዮጵያ አየር ለማንም ስፖርተኛ መጠናት የሚያስፈልገው አይደለም።  ከወደ በረሃ ለሚመጡ ቡድኖች  አስፈላጊ ነው፡፡ ከአዲስ አበባ ከፍ ያለች ከተማ ነች ወልዲያ … ተጋጣሚ ቡድኖችን እያስተናግደን ቶሎ ቶሎ ብናሸንፍ ጥሩ ነው፡፡›› ብለው ለመጨረሻው ጥያቄ “ስታድዬሙ የተረከበው አካል ይህን በቶሎ ቢያደርግ ማየት ደስ ይለኛል፡፡›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡
የስታዲየሙን ፋይዳ አስመልክቶ ዶ/ር አረጋ ሲናገሩ ወልዲያ ለላሊበላ ቅርብ በመሆኗ፣ ባቡር በከተማው ስለሚያልፍ፤ ለመቀሌ፣ ለጎንደር፣ ለጎጃም፣ ለደብረ ማርቆስ አዋሳኝ ከተማ በመሆኗ የቱሪዝም መስህብነቷን እንደሚጨምር በመጥቀስ ነው፡፡ በከተማው ስፖርትን ለማነቃቃት ከፍተኛ አቅም በስታድየሙ መኖር ይገኛል በማለትም አብራርተዋል፡፡
‹‹ስታድዬሙን ወልዲያ ከተማን ያስተዋወቃል በማለት በጋዜጣዊ መግለፃ ላይ የተናገሩት ዶክተር አረጋ ይርዳው፤ በካሊፎርኒያ ቤቨርሂልስ እንደሚገኘው ‹‹ሆሊውድ›› የተሰኘ ላንድ ማርክ ምልክት ቢሰራም የመሃመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ ስታድዬም የከተማው ምልክት ይሆናል ብለዋል፡፡ ስታድዬሙ አገር አቀፍና አህጉራዊ ውድድሮች በማስተናገድ  ፈርቀዳጅ እንደሚሆን የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ እንደሚያምንበት ከፍተኛ የገቢ አቅም ሊፈጥር የሚችል መሆኑንም አመልክተዋል፡፡ ስታዲየሙን የሚያስተዳድረው የከተማው አስተዳደር ነው፡፡ ስታዲየሙን በማከራየት፤ ከዩኒቨርስቲ ጋር በቅንጅት ለመስራት፣ ብዙ ፋይዳዎቹ ይኖሩታል፡፡ ሚድሮክ የስታዲየሙን የቅርብ ክትትል ያደርጋል ዕድሳቶችን በየጊዜው ያከናውናል፡፡
የስታድዬም መሰረተ ልማቶችና የውድድር መስተንግዶዎች
በኢትዮጵያ ስፖርት አንዱ ትልቁ ውጤት የስታድዬም መሰረተ ልማቶች መስፋፋት መሆኑን ባለፉት 3 ዓመታት በየክልሎቹ እና በየከተሞቹ ከሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ማስተዋል ይቻላል፡፡ በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት በተለያዩ የክልል ከተሞች ሙሉ በሙሉ ስራ የሚጀምሩ ከ12 በላይ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያላቸው ስታድዬሞች አገሪቱ ይኖሯታል። እስከ 60ሺ የሚያስተናግደው የባህርዳር ስታድዬም ግንባታውን በቀዳሚነት አጠናቅቆ አገልግሎት በመስጠት ፈርቀዳጅ ነው፡፡ የባህርዳር ስታድዬም የመላው ኢትዮጵያ ጨዋታዎች፤ ከዚያም የአፍሪካ ክለቦች ውድድሮችን እንዲሁም የብሄራዊ ቡድኑን ጨዋታዎች በማስተናገድ ስኬታማ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ አምና 38ኛው የሴካፋ ሲኒዬርስ ቻሌንጅ ካፕ ያስተናገደው በከፍተኛ የጥራት ደረጃ የተገነባው የሐዋሳ ስታዬም  እስከ 45ሺ ተመልካች የሚይዝ ነው፡፡ የሐዋሳ ስታድየም የሴካፋን የምድብ ጨዋታዎች በማስተናገድ በካ እውቅና እግኝቶ ከባህርዳር ስታዬም በመቀጠል ሁለተኛው ውጤታማ መሰረተልማት ሆኗል። ዋልያዎቹ 2ለ0 ሶማሊያን ያሸነፉበትን የመጀመርያውን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ኢንተርናሽናል ጨዋታ ለማስተናገድ የበቃ ሲሆን ከዚያም ለ2017 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ ከሲሸልስ ጋር የተደረገ ግጥሚያንም ያስተናገደ ነው። ካለፈው ዓመት ጀምሮ የሐዋሳ እና የባህርዳር ስታድዬሞች አገልግሎት መስጠትና በካፍ እውቅና ማግኘት በመጀመርያ የፈጠሩት መነቃቃት በሌሎች ከተሞችም በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታትም የሚቀጥል ይሆናል፡፡ በካፍ እና በፊፋ ዓለም አቀፍ እውቅና ያገኙ ስታዬሞች ደግሞ ብዛታቸው 5 ደርሷል፡፡ የአዲስ አበባው ይድነቃቸው ተሰማ ስታድዬም፤ አበበ ቢቂላ ስታድዬም ቀዳሚዎቹ ሲሆኑ ከዚያም ባለፈው ዓመት የባህርዳር ፤ የሃዋሳ ከነማ እና የድሬዳዋ ስታድዬሞች እውቅና በማግኘት አህጉራዊ ጨዋታዎችን አስተናግደዋል፡፡ በወልዲያ ከተማ የተገነባው ሼህ መሃመድ ሁሴን አሊ  አላሙዲ ስታድዬም ለዓለም አቀፍ እውቅና በመድረስ 6ኛው ስታድዬም ነው፡፡
በግንባታ ላይ የሚገኙት 30ሺ ተመልካች የሚያስተናግደው ስታድዬም  የመቀሌ ስታድዬም ፤ ከ90 በመቶ በላይ ግንባታው የተጠናቀቀ እና 60ሺ የሚይዘው የነቀምቴ  ስታድዬም በመጨረሻ ምእራፍ ላይ በምደረሳቸው የሚጠቀሱ ይሆናል፡፡ የአዳማና ጋምቤላ ከተሞች ዘግይተው ቢጀምሩም 80ሺ እና 30ሺ ተመልካቾች የሚይዙ ስታድዬሞቻቸውን እንደ ቅደም ተከተላቸው እያስገነቡ ናቸው፡፡ የአዳማ ስታድዬም እስከ 1.7 ቢሊዮን ብር በሆነ ወጭ ተገንብቶ ሲጠናቀቅ በሚይዘው ተመልካች ብዛት ግዙፉ ሊሆን የሚበቃ ሲሆን እስከ 80ሺ በማስተናገድ ነው። እንዲሁም የጋምቤላው ስታድዬም እስከ 380 ሚሊዮን ብር ይወጣበታል፡፡ በሚገነቡ ስታድዬሞች የዘገየው የአዲስ አበባ ከተማ ነው፡፡  እስከ 60ሺ ተመልካች እንደሚይዝ የሚጠበቀው አደይ አበባ የሚል ስም የወጣለት ብሄራዊ ስታድዬም ዋናው የከተማ እቅድ ነው፡፡ ይህ ስታድዬም ከጎኑ የኦሎምፒክ መንደር የሚገነባለት መዋኛ፤ የመረብ ኳስ፤ የቅርጫት ኳስ ሜዳዎች እና ሌሎች የስፖርት መሰረተልማቶች ያሉት  60ሺ ተመልካች የማስተናገድ አቅም የሚኖረው  ይሆናል፡፡ የስታድዬሙ ዲዛይን በ40 ሚሊዮን  በኤምኤች የተሰራ ሲሆን በቻይና ስቴት ኢንጅነሪንግ  ኮርፖሬሽን በሁለት ደረጃዎች የሚገነባ የግንባታ ወጭው በመጀመርያው ምዕራፍ እስከ 2.4 ቢሊዮን ብር የተተመነ ነው፡፡ በተጨማሪም በአዲስ አበባ ከተማ በአምስት ዞኖች እያንዳንዳቸው   ለግንባታቸው 300 ሚሊዮን ብር ወጪ  አምስት ስታድዬሞች እንደሚታነፁ የተገለፀው ከሶስት ዓመት በፊት ነበር፡፡ በመተሳሳይ ወቅት በ1.3 ቢሊዮን ብር በጀት 60ሺ ተመልካች የሚያስተናግደው የአቃቂ ቃሊቲ ስታድዬም ዲዛይኑ በዮሃንስ አባይ ኮንሰልታንሲ ተሰርቶ በተክለብርሃን አምባዬ ኮንስትራክሽን እንደሚገነባም ተገልጿል፡፡ ሻሸመኔ፤ ድሬዳዋ፤ ሃረር፤ ጅማ ፤ ጎንደር፤ ስታድዬሞች መገንባት ያለባቸው ሌሎች ክልሎችና ከተሞች መሆናቸው ከዚህ ጋር ተያይዞ የሚነሳ ይሆናል፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ከወር በፊት ይፋ ባደረገው የ2008 በጀት ዓመት የገቢ ዝርዝር ትልቁን ድርሻ የሚወስደው ከስታድዬም ትኬት ሽያጭ የተገኘው ነው፡፡ በውድድር ዘመኑ ከብሄራዊ ቡድኑ ጨዋታዎች፤ ከሴካፋ እና ከፕሪሚዬር ሊግ ውድድሮች በተያያዘ የተገኘው ገቢ ከ13.6 ሚሊዮን ብር በላይ ነው፡፡
የስታድዬሞች መሰረተ ልማት መስፋፋት  
ኢትዮጵያ በአህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ውድድሮች የሚኖራትን ንቁ ተሳትፎ የሚያነቃቃ ይሆናል፡፡ አገሪቱ ለትልልቅ የስፖርት መድረኮች በመስተንግዶው፣ በትራንስፖርት አቅርቦት፤ በፀጥታና ደህንነት ያሏትብ አቅሞች  ከስታድዬሞቹ ግንባታ ጋር የሚፋጠን ነው። በተለይ ኢትዮጵያ በ2020 እኤአ የምታስተናግደው 6ኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ ቻን በስታድዬሞች መሰረተልማት በኩል ያላት ዝግጁነት የተረጋገጠ ነው።  እንደ ቻን አይነት አህጉራዊ የእግር ኳስ ውድድር ለማስተናገድ አምስት ደረጃውን የጠበቁ ስታድዬሞች በቂ ናቸው፡፡ ለአፍሪካ ዋንጫ ደግሞ በአማካይ 40ሺ ተመልካች የሚያስተናግዱ 4 ስታድዬሞች ከተገነቡ  ምናልባትም ኢትዮጵያ  የአፍሪካ ዋንጫን የምታስተናግድበት እድል በሚቀጥሉት 16 ዓመታት ሊሳካ የሚችል ይመስለኛል፡፡
ከ2020 እኤአ የቻን ውድድር መስተንግዶ በኋላ ትኩረቱ የአፍሪካ ዋንጫ እንዴት ይዘጋጃል? መሆን አለበት፡፡ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን ለአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅነት ብቁ የሚላቸው አገራት በሆቴል እና መስተንግዶ፤ ቢየያንስ አራት አለም አቀፍ ደረጃ የጠበቁ ስታድዬሞች ከእነ ልምምድ ስፍራቸው፤ በቂ የአየር እና የየብስ ትራንስፖርት አገልግሎት፤ አስተማማኝ ደህንነት እና ፀጥታን በዋና መስፈርቶቹ ይመለከታል፡፡
በአህጉራዊ ውድድር መስተንግዶ በሁሉም ከተሞች የሚገኙ ስታድዬሞች  ከአምስት በላይ ከብሄራዊ ኮሚቴው ጋር ተፈራርመው የሚሰሩ የመንግስት ተቋማት ከወዲሁ ማፈላለግ እና በአጋርነት የመስራት ስምምንት ማድረግ ይኖርባቸዋል፡፡ በአጠቃላይ ግንባታቸው ተጠናቅቆ ስራ እየጀመሩ የሚገኙት እና በግንባታ ላይ ያሉት ብዙዎቹ ስታድዬሞች በአፍሪካ ደረጃ ተመጣጣኝ ጥራት ያላቸው መሆናቸው የሚያበረታታ ነው፡፡ የስታድዬሞቹ በየክልሉ መስፋፋት ታላላቅ ውድድሮችን የማዘጋጀት አቅም፤ የየተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት የሚያነቃቃም ይሆናል። የስፖርቱን አስተዳደር ሁለገብ አቅም ያሳድጋል፡፡ አለም አቀፍ ትኩረት ይገኝበታል፡፡ የስፖርት መሰረተ ልማቶች እንዲስፋፉ ምክንያት ይሆናል፡፡ የስፖርት እድገትን ለማቀላጠፍ ያግዛል፡፡ አንድ አገር አህጉራዊ እና ዓለም አቀፋዊ የስፖርት መድረኮችን በማስተናገድ በቂ ተመክሮ እና አቅም እየገነባ ሲሄድ እንደ ዓለም ዋንጫ ኦሎምፒክ መድረኮችን ማዘጋጀት የሚቻልበት ምእራፍ ላይ የሚደረስ ይሆናል፡፡
ዎርልድ ስታድዬም ኢንዴክስ የሚባል የዓለም አቀፍ ሪፖርት አለ፡፡ በዳንሽ ኢንስቲትዩት ነው ስፖርት ስታዲስ የተሰራ ጥናት ነው “play the game” በሚል ርዕስ በለቀቀው ሪፖርቱ በ20 አገራት በሚገኙ 75 ስታዲየሞቹ ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ ከአውሮፓ ዋንጫ፣ ከዓለም ዋንጫ እና ከአፍሪካ ዋንጫ መስተንግዶዎች ጋር በተያያዘ  በ20 አገራት ባለፉት 15 ዓመታት የተገነቡት 75 ስታድየሞች በ14.5 ሲሆን ዶላር ነው፡፡ የዓለም ዋንጫን ለማስተናገድ የስታድዬም ግንባታና እድሳት በጀት እስከ 2.8 ቢሊዮን ዶላር ነው፡፡ በ2018 እ.ኤ.አ ራሽያ ለ21ኛው ዓለም ዋንጫ 3.8 ቢሊዮን ዶላር እንዲሁም በ2022 እ.አ.አ ኳታር ለ22ኛው ዓለም ዋንጫ እስከ 3 ቢሊዮን ዶላር በጀት የያዙት ከስታዬሞች ግንባታና ዕድሳት ጋር በተገናኘ ነው፡፡  በሌላ በኩል ደረጃውን የጠበቀ የኦሎምፒክ ሙሉ ስታዲየም እስከ 270 ሚ. ዶላር በጀት ይጠይቃል፡፡ በ2008 ዓ.ም ቤጂንግ 29ኛውን ኦሎምፒክ ያስተናደችው በ428 ሚ. ይዞር በተገነባው የወፍ ጎጆ ስታድዬም ነበር፡፡ ባለፉት 15 ዓመታት አፍሪካ ዋንጫን ያዘጋጁ አገራት በአማካይ ከ4-6 ስታድዬሞች እንዲገነቡ በካፍ የመስተንግዶ መስፈርት ይጠይቃሉ፡፡ ለአውሮፓ ዋንጫ መስተንግዶ 8 ስታድዬሞች ለዓለም ዋንጫ  ደግሞ ከ10-12 ስታዲዬሞች መገንባት መስፈርቱ ይጠይቃል፡፡ የአፍሪካ ዋንጫ ስታድየሞች ከፍተኛ 45ሺ ዝቅተኛ 15 ሺ ተመልካች የሚያስተናግዱ መሆን አለባቸው፡፡ የአውሮፓ ዋንጫ ስታድዬሞች  በአማካይ ከ30-50 ሺ ተመልካች የሚያስተናግዱ ናቸው፡፡  በዓለም ዋንጫ የመክፈቻና የዋንጫ ጨዋታዎች የሚያስተናግዱ ስታድዬሞች ያስፈልጋሉ፡፡ ባለፉት 5 የአፍሪካ ዋንጫዎች  አዘጋጅ አገራት በአማካይ ለመስተንግዷቸው ከ3 እስከ አምስት አዳዲስ   ስታድዬሞች ገንብተዋል፡፡ 

• በኹለቱ ዓመታዊ ክብረ በዓላት፣ ከ23   ሚ. ብር በላይ የስዕለት ገቢ ተሰብስቧል
• ማሠልጠኛዎች እንዲገነቡና የማኅበራዊ ልማት ተሳትፎው እንዲጠናከር ተጠይቋል

  በቁሉቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ውስጥ፣ እየተፈጸመ ነው በሚል ከምእመናን በተደጋጋሚ የቀረበው የሙስና  አቤቱታ፣ ተጣርቶ አስፈላጊው ርምጃ እንዲወሰድ፣ የምሥራቅ ሐረርጌ ዞን መስተዳደር ጽ/ቤት አሳሰበ፡፡ የመስተዳድሩ ጽ/ቤት ማሳሰቢያውን ያቀረበው፣ ባለፈው ወር መጀመሪያ ለፓትርያርኩ ቢሮ በጻፈው ደብዳቤ ነው፡፡ በዞኑ ሜታ ወረዳ ቁሉቢ ከተማ በሚገኘው የደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ውስጥ፣ “ኃይለኛ ሙስና እየተፈጸመ” መሆኑን በመጥቀስ ጉዳዩ እንዲጣራ የአጥቢያው ምእመናን ለቤተ ክርስቲያኒቱ ጥያቄ ሲያቀርቡ፣ ለመስተዳድሩም በግልባጭ አስታውቀው እንደነበር ጽ/ቤቱ አስታውሷል፡፡
አቤቱታውን ለማጣራት፣ ከገዳሙ አስተዳደርም ይኹን ከምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ እንዳልተደረገ፣ ከምእመናኑ በድጋሚ መረዳቱን የጠቀሰው የዞኑ መስተዳድር፤ “ለሕዝበ ክርስቲያኑ ክብር አለመስጠትን ያመለክታል፤” ሲል ተችቷል፡፡
“ጉዳዩ ወደ ሌላ አቅጣጫ እንዳያመራ”፣ በገዳሙ እየተፈጸመ ነው ስለተባለው ሙስና በቤተ ክርስቲያኒቱ አመራር በተገቢው መንገድ ተጣርቶ አስፈላጊው እርምጃ እንዲወሰድና ለሕዝበ ክርስቲያኑ እንዲገለጽ የፓትርያርኩን ቢሮ ጠይቋል፡፡ ጉዳዩ፣ በመንግሥት ደረጃ የፓትርያርኩ ቢሮ እስኪጠየቅ ድረስ ቸል መባሉ፣ በእጅጉ ቅር እንዳሰኛቸው የገለጹት የአጥቢያው ምእመናን፤ በአካባቢው በገዳሙ የተከናወነ ተጠቃሽ ማኅበራዊ ልማት አለመኖሩን፤ የአገልጋዮች ደመወዝ የገቢውን ያኽል አለመሻሻሉንና
ካህናቱ ከሚያሳዩት ትጋት ውጭ መንፈሳዊ አገልግሎቱን ለማጠናከር በአስተዳደሩ የሚደረገው ጥረት እዚህ ግባ የማይባል መኾኑን አስረድተዋል፡፡በየዓመቱ ታኅሣሥ 19 እና ሐምሌ 19 ቀን ለገዳሙ በስዕለት ከሚገባው ጥሬ ገንዘብና የተለያዩ ዓይነት ንዋያተ ቅድሳት ውጭ ባሉት ወርኃዊ በዓላትም ከፍተኛ ገቢ እንደሚገኝ ምእመናኑ ይናገራሉ፡፡ የኹለቱ ዓመታዊ ክብረ በዓላት ገቢ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤትና በዞኑ መስተዳድር አካላት ጥብቅ ቁጥጥር የሚደረግበትን ያኽል በሌሎቹም ወራት አለመደረጉ ለከፍተኛ ሙስና አጋልጦታል የሚሉት ምዕመናኑ፤ የጸበል ቦታው በብዙ መቶሺዎች እንዲታወቅ፣ ማረፊያዎችንና መጸዳጃዎችን ምቹ ማድረጉ እንኳ ትኩረት አልተሰጠውም፤ ሲሉ ቅሬታቸውን ይገልፃሉ፡፡የገዳሙ አስተዳዳሪ መልአከ ኃይል አባ ወልደ ጊዮርጊስ በበኩላቸው፤ የዞኑን ጥያቄ በተመለከተ ከጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጋር
መወያየታቸውንና የተሰጠውን ምላሽም ትላንት ለመስተዳድሩ ማድረሳቸውን ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል። “ጉዳዩ መታየት ያለበት በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ነው፤” ያሉት አስተዳዳሪው፣ የሙስና አቤቱታ አቅርበዋል የተባሉት ሰዎች ራሳቸው፣ በወንጀል
የሚፈለጉ መኾናቸውን ጠቅሰው፣ ለሕግ እንዲቀርቡ ጠይቀናል፤ ብለዋል፡፡
የገዳሙ ሒሳብ ሹሙ ወ/ሪት ወይንሸት ግርማም፣ አቤቱታ አቅራቢዎቹ ማንነታቸውን አለመግለጻቸውን ጠቅሰው፣ አቤቱታ የቀረቡባቸውን ጥያቄዎች ከሀገረ ስብከቱ ጋር ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በአካል አቅርበን በደብዳቤ የተሰጠውን ምላሽ ደግሞ፤ አዲስ አበባ ለሚገኘው ክልላዊ ቢሮና ለዞኑ ጽ/ቤት መስጠታቸውን አስረድተዋል፡፡
“ገዳሙ፣ በገቢረ ተኣምራቱ ያለውን ታዋቂነትና የገቢ መጠኑን ያኽል፣ መንፈሳዊ አገልግሎቱን ለከተማው ምእመናን ተደራሽ በኾነ አኳኋን እንዲያስፋፋ፤ ቀድሞም የነበሩት የካህናት ማሠልጠኛና የአብነት ት/ቤቶች በተደራጀ መልኩ እንዲከፈቱ፤ እንደ ድሬዳዋና ሐረር ባሉት ከተሞች ተጨማሪ ገቢ የሚያስገኙ የራስ አገዝ ግንባታዎችን በማካሔድ ማኅበረሰባዊ አገልግሎቱን የሚያጠናክርበት አቅም እንዲፈጥር” ጠቁመዋል ምዕመናኑ፡፡ ለዚኽም ገዳሙ፣ “ለረጅም ጊዜ ከቆዩት ሓላፊዎች ይልቅ፡- ሙስናን የሚጸየፉ፣ የተማሩና የነቁ አገልጋዮች” እንደሚያስፈልጉት ጠቁመዋል፡፡በዓመት ኹለት ጊዜ ለሚከበረው የቅዱስ ገብርኤል ክብረ በዓል፣ ከሀገር ውስጥና ከውጭ ወደ ገዳሙ ከሚጓዙ ተሳላሚዎች፣ ከ23 ሚሊዮን 587 ሺሕ ብር በላይ በስዕለት መግባቱን የሐምሌ 19 ቀን 2007 እና የታኅሣሥ 19 ቀን 2008 ዓ.ም. የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሪፖርት ያመለክታል፡፡ ይኸው ገቢ በጠቅላይ ጽ/ቤቱ የበጀት ዕቅድ እየወጣለት፥ ለቤተ ክርስቲያኒቱ የነገረ መለኰት ኮሌጆች፣ ለአብነት መምህራን፣ ለሰባክያነ ወንጌልና ለሠራተኞች ደመወዝ የሚከፈል ሲሆን የሙከራ ሥርጭት እያካሔደ ለሚገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቴሌቭዥን ጣቢያ የ9 ሚሊዮን ብር አስተዋፅኦ ማድረጉም በሪፖርቱ ተገልጿል። በስዕለት የሚሰበሰቡትን የተለያዩ ዓይነት ንዋያተ ቅድሳት፣ ዋጋ አጥንቶና ተማኝ ኮሚቴ አቋቁሞ የሚያሰራጭ የማደራጃ መምሪያ፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የተቋቋመ ሲኾን፤ ተጨማሪ ገቢ ማስገኛ ሕንፃ ለማሠራትም ዕቅድ መያዙን በሪፖርቱ አስታውቋል፡፡  

 ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጀት 95ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን ምክንያት በማድረግ በዛሬው ዕለት ለበጎ አድራጎ ድርጅቶች 132 ሺህ ብር የሚገመት የቁሳቁስ እርዳታ ያበረክታል፡፡
ድርጅቱ “ለቀጨኔ ሴት ህፃናት ማሳደጊያ ተቋም” እና “የወደቁትን አንሱ የአረጋውያን መርጃ ማህበር”፣ የአዲስ አበባ አስተዳደር ሴቶችና ህፃናት ጉዳዮች ቢሮ አመራሮችና ሰራተኞች በተገኙበት እርዳታውን ያበረክታል ተብሏል፡፡
ማተሚያ ድርጅቱ፤ ለእያንዳንዳቸው 66ሺህ ብር በመመደብ፡- 20 አልጋዎች፣ 20 ፍራሽ፣ 20 ብርድ ልብስ፣ 20 አንሶላና የትራስ ልብስ እንዲሁም ሌሎች ልዩ ልዩ ቁሳቁሶች እንደሚያበረክት አስታውቋል፡፡

የአዲስ አድማስ ጋዜጣ መስራች
የአቶ አሰፋ ጎሳዬ ገዳ የ12ኛ ዓመት መታሰቢያ ታህሳስ
6 ቀን 2009 ዓ.ም በቅዱስ ካቴድራል አማኑኤል
ቤተክርስቲያን በፀሎት ታስቦ ውሏል፡፡
አሴዋ ሁሌም እናስብሃለን ቤተሰቦችህ


አንድ ደርዘን ዕድሜ

አሴ!
ከቶም አንድ ደርዘን ዕድሜ፣ አለፈና ዘመን ሆነ
አዋቂውን እያከሳ፣ ድንቁርና እያደነደነ
የነበረው እንዳለ አለ
እንደ አፋር ጫማ ፊት ኋላውን፣ አቅጣጫው አልለይ እንዳለ፡፡
ያልተዘመረለት ነህ፣ ብዬህ ነበር ገና ያኔ
አሁንም ወሮናል አሴ፣ የዕውቀትና ብስለት - ጠኔ
ዛሬም ያልተዘመረለት፣ እንደገባ ነው ምናኔ!
“… አዎ አለ አንዳንድ ሰው
ጉቶ የሸፈነው የአገር ግዙፍ ዋርካ
መስፈሪያ የሌለው፣ ልቡ እማይለካ
… ያልተዘመረለት፣ እሱ ኖሯል ለካ!”
ያልኩህ ትዝ ይበልህ አሴ፣ ዛሬም ያው ጮካ ለጮካ
ኑሮ ሆኗላ እንካ በእንካ!
ዘመኔ መቀነቻ አጥቶ፣ ይሸነጋገላል ሰው ሁሉ
የአፉ ከሆዱ ተጣልቶ፣ ጠፍቶበታል ዕትብት ውሉ፡፡
ሰው ሲጠፋን ስለሰው፣ ማሰብ የማይቀር ዕውነት ነው
ያጎደሏትን አገር፣ መሙላት ጭንቁ መቶ አምሳ ነው
ቅጣቱ ራስን ማጉደል ነው!
አላዋቂው ከላይ ሰፍሮ
አዋቂ ታች ተቀርቅሮ
ዱሮ እንዳየኸው ነው ህይወት፣ ያው የግርምቢጡ ኑሮ!
ሰው ራሱን ለማየት ዛሬም ዐይኑ ጠፍቶበታል
እንንገርህ ብንል ደግሞ፣ ቀድ ጆሮውን ይዘጋል
ደምም መቅመስ አልሆነለት፣ ፍጥረቱ ለጣ’ም ጣም የለው
ስድስተኛ ስሜት አለው፣ ብለን ጥንት የጠረጠርነው
ከነአምስቱም ጠፍቶበታል፣ መደናበር ነው የያዘው!
አሴ እንዳልኩህ ጉቶው በዛ፣ ዋርካ እሚሆን ሰው ጠፋና
በግምገማ ብቻ ቀረን፣ ጧት ማታ እያወራን መና!
አሴ! ፈገግ በል እባክህ፣ ምንም አላጣህምና!
የምንፈልገውን ሳናውቅ፣ የምናውቀውን ሳንፈልግ
የሚሄደውን መራገም፣ ለመጣ ሁሉ ማደግደግ
ይህ ሆኗል የህሊና ሕግ!
አዲስ መውለድ ሲያቅተን፣ ያረጥነውን መናፈቅ
እርግማን ነው የቤት ጣጣ፣ ዘልቆ አገርን የማያዘልቅ
አሴ!
ትውልዱም እንዳስቀመጥከው
ዴሞክራሲም ያው እዚያው ነው
ንግዱ በጭንቅ፣ ኑሮው በጭንቅ፣ ባለቤት
የሌለው እልፍኝ
ከቶም ያልተግባብቶም አገር፣ የሆድ ያንጀት
እማያስገኝ
ወይ ከታሪኩ ያልሆነ፣ ወይ ልባም ታሪክ ያልሰራ
እንደው ሸርተት ሸተት ብቻ፣ የአንድ ደርዘን ዕድሜ ጎራ
ነውና አሴ አልቀረብህም፣ እዚያው ፈገግ ብለህ ኩራ!
ያ ፈገግታ ነው የናፈቀን፣ አሴ ሳቅልን አደራ!!
ከቶም ላልተዘመረለት፣ እንዘምርለት ያልነው
ከቶም ላልተነገረለት እንናገርለት ያልነው
ዛሬም ሀቁ እንደዚያው ነው
አስራ ሁለት ዓመት ሆነ፣ ደርዘን ፈገግታህ ይፍካ
ሁሌም እናስብሃለን፣ በቅን ፍቅራችን ተመካ!
ወደፊት እንሂድ እንጂ፣ ወደኋላ ማሰብ አይቀር
አለህ እውስጣችን አሴ፣ ስምህ የትም አይቀበር
ህዝቡ ይወቅ ብለሃል፣ ዕውቀት የፈራ ያቀርቅር
በዚህ ነው አንተ እምትኖር!
“መርሳት ለዘላለም ይኑር፣” የሚሉ እንዳሉ አቃለሁ
እኔ ግን በልብ ዕምነቴ፣ መርሳት ይሙት እላለሁ!!
(ለአሰፋ ጎሳዬ 12ኛ ሙት ዓመት
እና ለማንረሳቸው ሁሉ መታሰቢያ)
ነቢይ መኮንን