Administrator

Administrator

የአየር ሃይል አዛዡና ሌሎች ባለስልጣናትም በ74 ሚ. ዶላር ሙስና ተከስሰዋል

   የናይጀሪያው ፕሬዚዳንት ሙሃመድ ቡሃሪ ልዩ ጠባቂ የሆነው ሃሰን አሚኑ የተባለ የአገሪቱ የደህንነት አባልና ሌሎች ለፕሬዚዳንቱ ቅርበት ያላቸው የደህንነትና የጦር ሃይል አባላት አገሪቱን በሽብር ከሚያምሰው ጽንፈኛው ቡድን ቦኮ ሃራም ጋር ንክኪ አላቸው በሚል ተጠርጥረው ባለፈው ረቡዕ አቡጃ ውስጥ በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋላቸው ተዘገበ፡፡
የአገሪቱ መንግስት የደህንነት ልዩ ግብረ ሃይል ለፕሬዚዳንቱ ቅርበት ያላቸውን ግለሰቦች የጀርባ ማንነትና ድብቅ አጀንዳ በመመርመር ላይ እንደሚገኝ የዘገበው ናሽናል አኮርድ ኒውስ ድረገጽ፤ይሄው የፕሬዚዳንቱ ጠባቂና የደህንነት አባላትም ከአሸባሪው ቡድን ጋር የድብቅ ግንኙነት እንዳላቸው በመረጋገጡ መታሰራቸውን ገልጧል፡፡ግለሰቡና ግብረ አበሮቹ ከቦኮ ሃራም ጋር ግንኙነት እንዳላቸው መረጋገጡንና በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ተከትሎ፣ ሽብርተኞች በፕሬዚዳንቱ ጠባቂዎችና ለቤተመንግስቱ ቅርበት ባላቸው ግለሰቦችና ሰራተኞች አማካይነት ጥቃት እንዳይፈጽሙ ለመከላከል የተጠናከረ ክትትል እየተደረገ መሆኑም ተነግሯል፡፡ የፕሬዚዳንቱ ጠባቂና የደህንነት አባላቱ ከቦኮ ሃራም ጋር ግንኙነት እንዳላቸው መረጋገጡ፣ አሸባሪ ቡድኑ ከሽምቅ ውጊያ ባለፈ ምን ያህል እስከ ቤተ መንግስቱ የሚደርስ የጥቃት ሰንሰለት እንደዘረጋ ያመላክታል ተብሏል፡፡በተያያዘ ዜናም፣ የቀድሞው የናይጀሪያ አየር ሃይል አዛዥና ሌሎች ሁለት የጦር ሃይል ባለስልጣናት በሚሊዮን ዶላሮች የሚቆጠር  የህዝብ ገንዘብ ለግል ጥቅማቸው አውለዋል በሚል ተከስሰው ፍርድ ቤት መቅረባቸውን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡ የቀድሞው የአገሪቱ የአየር ሃይል ላይ አዛዥ ማርሻል ጃኮብ ቦላ አዲጉን እና ሌሎች በቁጥጥር ስር የዋሉት ባለስልጣናት በድምሩ 74 ሚሊዮን ዶላር የህዝብ ገንዘብ መዝብረዋል በሚል ነው የተከሰሱት፡፡

   ለታሪክና ለባህላዊ ጥናቶች ትልቅ ዋጋ ያለው ሥራ፤ የተባለለት ‹‹እጨጌ ዕንባቆም - ከየመን እስከ ደብረ ሊባኖስ›› በሚል ርእስ በዲያቆን ዳንኤል ክብረት የተዘጋጀው አዲስ መጽሐፍ ታትሞ በያዝነው ሳምንት ለንባብ በቅቷል፡፡ ብዙ ምስቅልቅል፣ ጦርነቶች፣ ከፍተኛ የሕዝቦች እንቅስቃሴና መፈናቀል የተከሠተበትን የኢትዮጵያን የ16 ኛውን ክፍለ ዘመን ታሪክና አስተዳደራዊ መልክዓ ምድር (ጂኦግራፊ) ለመረዳት ያስችላል የተባለው ይኸው መጽሐፍ፤
ዋጋው ብር 60.00 ሲሆን፤ በመጪው ሳምንት ቅዳሜ (ሐምሌ 9) ከሰዓት በኋላ ከ 8፡30 እስከ 12፡00 ሰዓት፤ በዋቢ ሸበሌ ሆቴል አዳራሽ የታሪክ ምሁራንና ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት እንደሚመረቅ ተገልጿል፡፡ አዲሱ ጽሐፍ የዲያቆን ዳንኤል ክብረት 23ኛ ሥራ መሆኑ ታውቋል፡፡ ዲያቆን ዳንኤል የአዲስ አድማስ ቋሚ አምደኛ መሆናቸው ይታወቃል፡፡

Saturday, 02 July 2016 12:37

‘Fikru’….‘ፍቅሩ’

የሥዕል ትርዒት ዳሰሳ (Exhibition Review)
የትርዒቱ ርዕስ፡ ፍቅሩ
ሠዓሊ፡ ፍቅሩ ገ/ማርያም
የትርዒቱ አይነት፡ የግል፤ የቀለም ቅብ ስራዎች
ብዛት፡ 25 የቀለም ቅብ፤ ስራዎች
የቀረበበት ቦታ፡ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየም ጊዜያዊ የስዕል ማሳያ አዳራሽ አዲስ አበባ
ጊዜ፡ ሰኔ 06 - ሐምሌ 7: 2008 ዓ.ም
ዳሰሳ አቅራቢ፡ ሚፍታ ዘለቀ(የሥነ-ጥበብ አጋፋሪ)

“ፍቅሩ”
ለግል የሥዕል ትርዒት ስያሜነት ከሚውሉ አሰያየሞች መካከል መጠሪያ ስምን ለትርዒት ስያሜ ማድረግ ከተለመዱት መሃል አንደኛው ነው፡፡
ይህን ማድረግ ራሱን የቻለ መደንግግ ነው፡፡ ሠዓሊ ፍቅሩ ገብረማርያም ለዚህኛው ብቻ ሳይሆን በላጮቹንና አብዛኛዎቹን የግል የሥዕል ትርዒቶቹን መጠሪያ በስሙ ‘ፍቅሩ’ በሚል ነው ለህዝብ እይታ የሚያበቃው፡፡ ይህ ደግሞ መደንግግነቱን እንድናስተነትንና ‘ፍቅሩ’ የሚለውን ስያሜ በድግምግሞሽ እንዲጠቀም ያስቻለውን አመክንዮ ለመረዳት ቆፈር ቆፈር እያደረግን እንድንፈትሽው በር ከፋች ነው ባይ ነኝ፡፡ አሃዱ፡ ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም ‘ፍቅሩ’ ነቱ ላይ ችክ ያለ ሠዓሊ መሆኑን መረዳት እንድንችል እየነገረን ሊሆን ይችላል፡፡ ክልኤቱ፡ ሠዓሊው ገና የ’ፍቅሩ’ነቱን ፍቅር አጣጥሞ አለመጨረሱን እንድንጠረጥር በገቢርም ሆነ በነቢብ የማርያም መንገድ እየሰጠን ይሆናል፡፡ ሰልስቱ፡ ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም ራሱ ፍቅሩን ወይም የፍቅሩንነቱን ጥግ፣ልክ፣ጥልቀትና ርቅቀት ገና ዳሰሶ ወይም ፈልጎ አለመጨረሱንና አለማግኘቱን ለመጠቆም፤ ይልቅስ በፍለጋው ሂደት ያገኘውን ወይም የደረሰበትን ፍቅሩን እንካችሁ ማለቱ ሊሆን ይችላል፡፡ አርባዒቱ፡ ሠዓሊው በደረሰበት ወይም ባገኘው ፍቅሩነት እርግጠኛ ሆኖ፣ እነሆ ፍቅሩ መጥቷልና ከበረከቱ ትካፈሉ ዘንድ ትርዒቱን እንካችሁ እያለም ይሆናል፡፡ ሐምስቱ፡ መ ሁሉም መልስ ነው፣ አልተሰጠም ወይም መ መልስ የለውም የሚል መደምደሚያ ላይ ልንደርስ እንችላለን፡፡ ወደ ትርዒቱ፡-
በትርዒቱ ከቀረቡት ስራዎች ሰባ በመቶ የሚሆኑት በአውታረ መጠናቸው ብቻ የሚናገሩት ሃቅ አለ፡፡ የሥራዎቹ የጎን ስፋትና ቁመት ተቀራራቢነት ያላቸው፤ ወደ ስኩዌር ካሬነት የሚያዘነብሉና መሃከለኛና በብዛት ትልቅ መጠን ያላቸው የሥዕል ሰሌዳዎችን ነው የሚጠቀመው፡፡ እንዲህ አይነቱ አውታረ መጠን በተለምዶ ግዘፍ የሚነሳ፤ ዓይን የሚሞላና ደርፈጭ ያለ ወይም (bald) እንደሆነ ይነገራል፡፡ አንድ ሠዓሊ ይህን አይነት አውታረ መጠን ሲጠቀም ግዘፍ የሚነሱና ስለ ራሳቸው በልበ ሙሉነት የሚናገሩ ሀሳቦችን በማንሸራሸር እንዲያግዘው ሆን ብሎ የሚመርጠው እንደሆነ ይታመናል፡፡ በዚህ ትርዒት የቀረቡ አብላጫዎቹ ስራዎች በዚህ አቀራረብ የተቃኙ እንደሆኑ ይስተዋላል፡፡ ሆኖም እንዲህ አይነት ዝንባሌ ያላቸው ስራዎች በአንድ ላይ ለዕይታ ሲቀርቡ፣ ሲደረደሩና ሲሰቀሉ ሰዓሊውም ሆነ የትርዒቱ አጋፋሪ (curator) በጥንቃቄ ማሰብና መከወን የሚገባውን ወሳኝ ነጥብ የሳተ አቀራረብ በዚህ ትርዒት ይስተዋላል፡፡ ይኸውም ትርዒቱ ከሚታይበት ህንፃ ውስጥ ፎቅ ላይ ባለው የመጨረሻውና ሰፊው የሥዕል ማሳያ አዳራሽ ውስጥ የተሰቀሉት ሳይሆን የተገጠገጡት ሊባል በሚያስችል ደረጃ እንደ ሱቅ በደረቴ በአንድነት ተቸምችመው ያሉት አምስት ስድስት ሰራዎች የግዙፍነታቸውን ብቻ ሳይሆን ያመቁትን የሃሳብና የስሜት  ጥቅጥቅነት (density) ከግምት ያላስገቡ ናቸው፡፡ ሠዓሊው ፍቅሩ ገ/ማርያም፤ በፍቅር የወደቀላቸውን ስራዎች ለማሳየት በጉጉት ሲጣደፍ አሰቃቀሉ ለዕይታ እንደሚጎረብጥ እንኳ ማስተዋል እንደነሳው ማየት እንችላለን፡፡ ለአንድ ነገር ፍቅር ብቻ ሲቸረው የሚያስከትለው ችግር ይኖራል፡፡ ምናልባትም በ’ፍቅሩ’ነቱ ጥግና ልክ እርግጠኛ የሆነ ቢሆን ኖሮ እንዲህ ከመገጥገጥ ይልቅ አንድ ወይ ሁለት ስራዎቹን ብቻ “ገጭ” አድርጎ ሰቅሎ ሙሉ “ፍቅሩ”ነቱን በልበ-ሙሉነት መንፈስ ጀባ ሊለን ይቻለው ነበር የሚል ሙግት አመክንዮ እንዳነሳ የሚጋብዝ ፍንጭ በተለይ ከተጠቀሰው የሥራዎቹ አውታረ መጠናቸውን መሰረት በማድረግ፣ሥራዎቹ ከተሸከሙት የሀሳብና የስሜት ጥቅጥቅነት በመነሳት ለተመልካች እይታ ብሎም መረዳት ትግዳሮት (problem) የሚፈጥረውን የትርዒቱን ባህሪ ማየት ይቻላል፡፡ በመሰረቱ እንዲህ አይነት ጥቃቅን የሚመስሉ ነገር ግን ለአንድ የሥዕል ትርዒት ምሉዕነት ጉልህ ሚና ያላቸውን የአቀራረብ ባህሪያት ከግምት ውስጥ አስገብቶ የሚሰራ የሥነ-ጥበብ አጋፋሪ ከሌላው ትርዒት የሚጠበቅ ህፀፅ ቢሆንም እንደ ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም በዓለም አቀፍ መድረኮች፣ በታላላቅ ሙዚየሞችና ጋለሪዎች ዓለማችን ካፈራቻቸው ምርጥ ሠዓሊያን ጎንና በአንድነት ስራውን ካቀረበ ሠዓሊ የማይጠበቅ በመሆኑም ነው ይህን ያህል ትኩረት ሰጥቼው የነካካሁት፡፡ በአንፃሩም የትርዒት ማሳያው አዳራሽ አስተዳደርም ቢሆን ለአዳራሹ ኪራይ አይሉት አበል ለፅዳትና ጥበቃ አንዳንዴም የአዳራሹን በርና መስኮት ከፍቶ ለሚዘጋው ሰው አበል በሚል ሰበብ ለሚሰበሰበው ገንዘብ ትኩረት ከመስጠት ውጪ ለእንዲህ አይነት ሙያዊ እገዛዎችም ሆነ የአዳራሹን ግድግዳዎች ለማደስ፣ የሥዕል አስቃቀልንና ዕይታን ለሚረብሹት እንዲያው እንደዘበት አቡጂዲ ጨርቅ በመስኮቶቹ ላይ ጣል ከማድረግ ውጪና አንድ የሥዕል የተሳካ ለሚያደርጉት የብርሃን አምፑሎች “በዕድላቸው” እንዲበሩ ከመተው የዘለለ መፍትሔ ከማቅረብ ሌላ ዳተኝነቱን በተከታታይ እየተዘጋጁ ካሉ ትርዒቶች ለመረዳት ችለናል፡፡ እናም ከዚህ ዓይነት የአዳራሹ አስተዳደር የሥነ-ጥበብ አጋፋሪ (curator) መጠበቅ “እዬዬም ሲደላ ነው” ሊሆንብን ይችላል፡፡ ሆኖም የኢትዮጵያ ብሔራዊ … የሚል ሁለት ከባባድ መጠሪያዎችን ከተሸከመ የሥዕል ማሳያ አዳራሽ እንዴት “እዬዬም ሲዳላ” ይሆናል የሚል ሀሳብ ዘወትር ወደ አዳራሹ ጎራ ባልኩ ቁጥር የሚነዘንዘኝ ሃሳብ በመሆኑና መተቸት የሚገባው እንደሆነ ስለማምንበት ነው ያነሳሁት፡፡ አስተዳደሩ አዳራሹን ለተከታታይ ትርዒት ክፍት ከማድረጉ ባሻገር በዚህ በ “ፍቅሩ” ትርዒት ሙዚየሙና የአዳራሹ አስተዳደር ካሳየው አበረታች ጅምሮች መሃከል የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን አቶ ዮናስ ደስታ በትርዒቱ መክፈቻ ተገኝተው ስለ ትርዒቱና ስለ ሥነ-ጥበብ እንዲሁም ባለስልጣን መ/ቤቱ ለሥነ-ጥበብ ስለሚያደርገው ድጋፍ የሰጡት ጠንካራ የመክፈቻ ንግግር ነው፡፡ በተለይ ባለስልጣን መ/ቤቱና የአዳራሽ አስተዳደር ከላይ የተጠቀሱት አይነት ችግሮችን በጊዜ ሂደት እየቀረፈ ቢሄድ ይበል የሚያስብል ማለፊያ ማበረታቻ ነው፡፡ ወደ “ፍቅሩ” እንመለስ፡-
ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም በ1987 ዓ.ም ነው ከአሁኑ የአዲስ አበባ ዮኒቨርስቲ  አለ የሥነ-ጥበብና ዲዛይን ት/ቤት  በቀለም ቅብ በዲፕሎማ የተመረቀው፡፡ ለዲፕሎማው አራት ዓመታትን፣ ከዚያ በፊት ት/ቤቱ ይሰጥ በነበረው የማታ ትምህርት ክፍለ ጊዜ ለሁለት ዓመታት፣ እንደገና ከእነዚህ ሁለት ዓመታት በፊት ለአራት ዓመታት በተከታታይ የክረምት ትምህርት ክፍለ ጊዜ በት/ቤቱ ተከታትሏል- አስር ዓመታትን በድምሩ የሥዕል ትምህርት ሲማር ቆይቷል ማለት ነው፡፡ ተመርቆ ከወጣ በኋላ እስካሁን ባሉት ሀያ አንድ ዓመታት ውስጥ ደግሞ  በስቱዲዮ ሠዓሊነት ቆይቷል፡፡ ሥዕል የተማረበትና የሰራበት ዓመታት ሲደመሩ የአንድ ትውልድ እድሜ ይተካከላሉ ማለት ነው፡፡ የሥዕል ትምህርት መማር ሠዓሊ አያደርግም፤ምናልባት ሥዕል ለመስራት ያግዝ ይሆናል እንጂ፡፡ የሥዕል ትምህርት አለመማምርም ከሠዓሊነት አያግድም፡፡ በሀገራችን ብቸኛው የሥነ-ጥበብ ተቋም ሆኖ ከግማሽ ምዕተ ዓመታት በላይ የዘለቀው የአለ የሥነ-ጥበብና ዲዛይን ት/ቤት፣ ሲያስተምርበት የቆየውንና አሁንም ከሞላ ጎደል እያስተማረበት የሚገኘውን የትምህርት አሰጣጥ ዘዬና ፍልስፍና እጅጉን ክሊሎት (skill) ላይ መሰረት ያደረገና ቆይታው ያዳበረው ልምድ ብቻቸውን ወደ አንድ ከዚህ ቀደም ሲሰራ ከቆየበት ወደ ተለየ የአሰራር አቅጣጫ እያመጡት እንደሆነ በዚህ ትርዒት ላይ መመልከት እንችላለን፡፡
 ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም አበድ፣ሰከር፣ቆፍጠንና ፈጠን ያለ ድፍረት በዚህ ትርዒት አሳይቶናል፡፡ እብደቱ ስካሩ ነፃነቱን፤ፍጥነቱና ቆፍጣናነቱ ደግሞ ሩቅ አላሚነቱን ያመለክታሉ፡፡ ጭልጥ አድርጎ ከመጠጣት ሳይሆን ቀስ በቀስ፣ ያውም የአስር ዓመታት ትምህርትንና ሃያ የሚሆኑ የሠዓሊነት ዓመታት ልምዶችን በዝግታ በማጣጣምና በማሰላሰል ከሚመነጭ ድፍረት ነው እብደቱና ስካሩ የተወለዱት፡፡ ቀጥ ብሎ ለመቆም፣አሻራውን ለመተው፣ምናልባትም ለመዝናናት፣ ፈታ ብሎ በስራዎቹ ሙከራ ለማድረግና እንደውም (ቀጣዩን ዓረፍተ ነገር ቡፍ ብሎ ከሚያመልጥ ሳቅ ጋር ነው ያሰብኩት)… እንደውም “ሥዕል ምናባቱ-የታባቱ አፈር ድሜ ማብላት ነው እንጂ” እያለ መስራ ከሚያስችል ድፍረት ውሰጥ የሚገኝ ሩቅ አላሚነት የከሰቱት ፍጥነትና ቆፍጣናነትም በስራው ማየት ይቻላል፡፡ በዚህ ትርዒት የቀረቡት ሥራዎች በሥነ-ጥበብና በሚሰራው ሥዕል ለመፈላሰፍና ለመዝናናት የሸሚዞቹን እጀታ ከክንዱ ከፍ አድርጎ የሰበሰበ ሰው የሚሰራቸው አይነት ስራዎቸ ይታዮኛል፡፡ ሥራዎቹ ቆፍጣናነትና ፍጥነት ካልተሞላባቸውም ለዘዝ ብለው ለዘመናት ሲመላለስበት ወደ ኖረበት ድግምግሞሽ ለመመለስ የፈራ የሚደፍረው ዓይነት ድፍረት ይስተዋላል፡፡ ይልቅስ ቆፍጠን ብሎ ፍጥነት በመጨመር ቢነጉድ አንድ ከፍታ ላይ ለመድረስ የሚያልም፣ነፍሱን የሳተ እብድና ሰካራም ጋላቢ ከሚደፍረው ድፍረት የመነጩ ስራዎች በትርዒቱ ይታያሉ፡፡
በትርዒቱ የቀረቡ አብዛኛዎቹ ሥራዎች ሙከራዊ (experimental) ቢሆኑም የአካዳሚክ (የሥዕል ትምህርት) ህግጋትን ለመጣስ የሚፍጨረጨሩ ናቸው፡፡ ከመማርም አልፎ በሥራ ያዳበረውን የአሳሳል መንገዶች ካላፈረስኩ ብሎ መታገል፣ እብደትና ስካር ካልታከለበት በቀር መድፈር አስቸጋሪ ነው፡፡ ብዙ ሠዓሊያን ይህን ድፍረት አጥተው ለተማሩት ትምህርት ብቻ እስረኛ ሆነው ቀርተዋል፡፡ በሥነ-ጥበቡም ሆነ በፍልስፍናው እመርታ ለማሳየት ሙከራ ወሳኝ ነው፡፡ ሠዓሊ ፍቅሩ ይህንኑ ነው እያደረገ ያለው፡፡ እየሞከረ፡፡ ሙከራውም አያሌ የዓለማችን ሠዓሊያን ከሞከሩት የተለየ አይደለም፡፡ አሜሪካዊው ሠዓሊ ዊሊያም ደኩኒንግን ማንሳት እንችላለን፡፡
የፍቅሩ ሙከራ ማፍረስ ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ የሚሰራቸውን ምስሎች እያጠፋ አንዳች ሥነ-ጥበባዊ ፋይዳ ለማግኘት ነው እየተጋ ያለ የሚመስለው፡፡ በዚህ ከቀጠለም ያለፈባቸውንና በስራዎቹ ይስተዋሉ ከነበሩ ተፅዕኖዎች ከመላቀቅና ነፃ ከማውጣትም ባሻገር እንደ ድግምት ከሚደጋግመው “ፍቅሩ”ነቱ ሲጎነጩት እሚያረካ ጣዕም ሊቸረን ይችላል፡፡ ይህን ትጋት ወደ አንድ ጥበባዊና ሰብዓዊ አላማ የማዞር ኃላፊነት እንዳለበትም የሚዘነጋው አይመስለኝም፡፡ ጥበብ ሃቀኝነትን ትሻለች፡፡ በሃቀኝነት የሚከወን ጥበብ፣ከሠዓሊው ባሻገር ሃገርን፣ዓለምንና ሰብዓዊነትን ያገለግላል፡፡ በዚህ ትርዒት የቀረቡ ሥራዎች ይህን ታላቅ ኃላፊነትና ዓላማ ለማሳኪያ በር ከፋች አድርጌ ብወስዳቸው እመርጣለሁ፡፡ ሠዓሊው ጊዜውን፣አትኩሮቱንና እድሜውን ሙሉ ሲለፋለት በኖረለት ሥነ-ጥበብ ውስጥም አንዳች ፋይዳ ከመፈለጉና … ይህን ፍላጎት ክብር መስጠት አስፈላጊ ሆኑ በማግኘቴ ይበል ከማለት ውጪ መጨረሻውን ለመተንበይ እንኳንስ እኔ ሠዓሊውም የሚያውቀው አይመስለኝም፡፡
 ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም ተማሪ በነበረበት ጊዜና ተመርቆ ከወጣም በኋላ የት/ቤቱ አስተማሪዎችም ሆኑ የሀገራችን ግንባር ቀደም ሠዓልያን ክሂሎት ላይ የተመረኮዘ የአሳሳል መንገድን ሲያቀነቅኑ ነው የኖሩት፡፡ ሠዓሊ ፍቅሩና በዚህ ትውልድ ውስጥ ያለፉ አብዛኞቹ ሠዓልያኖቻችን፣ይህን ዘፈን ሲያዜሙም ነው የኖሩት፡፡ በእርግጥ የዜማው ጥዑምነት ያማልላል ነፍስንም ይገዛል፡፡ ብዙ አቅም ያላቸው ነገር ግን የዜማውን ጥዑምነት ብቻ እያጣጣሙና እየነሆለሉ በዚያውም የዓለምና የዘመኑ የሥነ-ጥበብ ኮቴ እያሰማና እየፈጠረ ያለውን ንቅናቄ ማዳመጥ ተስኖአቸው በዚያው የጠፉና የቀሰሙ እንዲሁም በዚሁ አዘቅጥ ውስጥ ያሉ ሠዓሊያኖቻችንም አያሌ ናቸው፡፡ አዲሱን፣ዘመንኛውን፣ የዘመኑንና የአለምን የቅርብ ጊዜ ወይም ለእኛ አውድ “መጤ” የሆነውን የሥነ-ጥበብ ኮቴ ለመስማት ብለውም ለቀደመው ጥዑሙ ዜማ ጆሮና ሁለመናቸውን ደፍነው ያሉበት እስኪጠፋቸው እየተደናበሩ ያሉትንም  የስዕል ስቱዲዮ  ይቁጠራቸው፡፡ የወቅቱ የሀገራችን ሥነ-ጥበብ መመለስ ከሚገባው ጥያቄዎች አንዱም ይሄኛው ይመስለኛል፡፡ ሚዛን መጠበቅ አልያም ሚዛን መድፋት የሚችለውንም በጊዜ ሂደት የምናየው ይሆናል፡፡
ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም በሥነ-ጥበብ ት/ቤት ቆይታው ክሂሎቱን ሲያዳብር ለመቆየቱና በስቱዲዮ ሠዓሊነት ባሳለፋቸው ዓመታት የተማረውን ክሂሎት ሥዕል ለመስራት ሲጠቀምበት ለመቆየቱም አንዳች ጥርጣሬ የለኝም፡፡ የዳበረ ክሂሎቱን ብቻም ሳይሆን በት/ቤት ቆይታው በእሳት የተጠመቀባቸው እስኪመስል የተጣቡት የእነ ፒካሶና ጉጌይን ተፅዕኖዎች፤ በፍቅር ያንበረከከውና እንደ ድርሳን ለዓመታት ሲደጋግመው የኖረው የመምህሩና የሃገራችን ታላቁ ሠዓሊ የታደሰ መስፍን ተፅዕኖ በስራዎቹ ለዓመታት መታየታቸው የእርግጠኝነቴ መሰረቶች ናቸው፡፡ ተፅዕኖቹ በአካዳሚክ ህይወቱና በመስራት ልምዱ የተፈጠሩ ናቸው፡፡ ከመስራትም ደጋግሞ በመስራት፡፡ እነዚህ ሁለት ተፅዕኖዎች መልካም ጎኖች እንዳሏቸውም ልብ ማለት ይኖርብናል፡፡ የመጀመሪያው ገንዘብና እውቅና፡፡ የሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም የሥነ-ጥበብ ልምምድ (practice) በትጋት የተሞላ ነው፡፡ ያለማቋረጥ ይሰራል፤ከዚህም ባሻገር ልፋቱ ተገቢው ቦታ ክብርና ዋጋ እንዲያገኝም ይለፋል፡፡ መሳል ብቻ ሳይሆን ሥራውን ለማስተዋወቅ ይጥራል፡፡ በዚህም የሀገራችን የሥነ-ጥበብ እንቅስቃሴ “ሙት” እንደሆነ ገና ድሮ ገብቶት የሚያገኛቸውን እድሎች ሁሉ እንደ መሰላል እየተጠቀመ፣ ሥራዎቹን ሞቅ ያለ የሥነ-ጥበብ እንቅስቃሴ ባላቸው የዓለማችን ሀገራት ጋለሪዎች ሙዚየሞችና አጋፋሪዎች ዘንድ ለማድረስ ቀና ደፋ ሲል ብዙ ተንከራቶ ተሳክቶለትማል፡፡  ገንዘብንና እውቅናንም በዓለም አቀፍ ደረጃ አግኝቷል፡፡ ተፅዕኖዎቹ ጠንካራ መሰረት ባይኖራቸው ማንኛውም ጋለሪ ሙዚየምና ኪዩሬተር ፊት እንደነሱት ነበር የሚኖረው፡፡ ዛሬ ለደረሰበት ደረጃም ላይበቃ ይችል ነበር፡፡ እነ ፒካሶና ጎጌይን የሰሩት ለዓለምና ለሃገራቸው አሁንም ድረስ ቤዛ እየሆነ ነው፡፡ ታደሰ መስፍንም ለሠዓሊ ፍቅሩ በቀጥተኛ መልኩ፣ ከሰላሳ ሶስት ዓመታት በላይ ለአስተማረበት ት/ቤትና ተማሪዎቹ በተለያየ መልኩ፣ለሀገራችን ሥነ-ጥበብ ደግሞ በጥቅሉ ቤዛ ነው፡፡
ሠዓሊ ታደሰ መስፍን እንደ “እድር አህያ” አንዴ በማስተማር፣ በሌላ ጊዜያት የስብሰባዎች ናዳ ሀገሪቱን ያሻሽሏት ይመስል እዚህም እዚያም በሚካሄዱት ስብሰባዎች ሲዶል በስቱዲዮው ጊዜ ለማሳለፍና ለመስራት መላ መምታት ተስኖት፣ በዘመናት ያዳበረውን ሥነ-ጥበባዊ እርምጃ አንድ ቦታ ማድረስ ቢሳነውም፤ ተማሪው የነበረው ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም ተፅዕኖው አርፎበት የተጀመረውን ለማስቀጠል እንኳን ባይሆን እንደ መሻገሪያ ተጠቅሞት ሊያተርፍበት ችሏል፡፡  ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም የተጠመቀባቸውና የተንበረከከባቸው እነዚህ ሁለት ተፅዕኖዎች፣ገንዘብና እውቅናን እንዲሸምትባቸው ከማስቻላቸውም በላይ አብዛኛው ሠዓሊ ስራውን ለመቀጠል ተግዳሮት ከሚሆንበት የገንዘብ  ጥያቄ ነፃነት አግኝቶ ስራውን በረጋና በነፃነት መንፈስ እንዲሰራ አስችሎታል ወይም ሊሰራ እንዲችል ምቹ ሁኔታ እየፈጠረለት ነው ባይ ነኝ፡፡
የተፅዕኖዎቹ ዳና በድግግሞሽ፤ አሊያም በመስልቸት፤ “አዲስ” ነገር ለመፈለግ እንዲነሳሳ፣ የተፅዕኖዎቹን ዳና ለማጥፋት የራሱ ብቻ ወደሆነ ዳና እንዲመጣ በማድረግ አቀጣጣይ፣ አነሳሽ ወይም ደግሞ አናዳጅ ሀይል መሆን ሁለተኛው ተፅዕኖቹ የተፈጠሩለት መልካም ጎን ይመስለኛል፡፡ ከላይ ስለዘረዘርኩት የአንደኛው ተፅዕኖ ምክንያታዊነት ሰዓሊው ፍቅሩ ገ/ማርያም ራሱ፣ሌሎች ሠዓሊያንና የሥነ-ጥበብ ባለሙያዎች እንዲሁም አንባቢ ሊስማማበትም ሆነ ላይስማማበትም ይችላል፡፡ እንደው የቀደሙ ሥራዎቹ ከማንኛውም ተፅዕኖ የፀዱ ናቸው ተብሎ ቢካድ እንኳን ለዓመታት የተማረው ትምህርት በሠዓሊነቱ ላይ ተጽዕኖ ከማሳደሩም በላይ አሁንም ከተጽዕኖው ለመላቀቅ የሚያደርገው ጥረት ላይ ማነቆ እየሆነበት እንደሆነ ማየት ይቻላል፡፡
ትርዒቱን ታድሜ ከገጠሙኝና ልጠቅሳቸው ከምፈልጋቸው ሁነቶች መሃል እንካችሁ፡-
“እንትን ያለው ልጅ”፤ ትርዒቱን ታድመው የነበሩ አንድ ትልቅ ሰው ናቸው አሉ “ከእስክንድር በኋላ እንትን ያለው ሰዓሊ ተገኘ” ሲሉ የተደመጡት፡፡
አባባሉ “እንትን” ያላቸው ሠዓሊያንና እንትናቸው የሚያዝና ዘር የሚዘራ፤ እየዘራም ያለ ሠዓሊያን በሞሉባት ሀገር፣ ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም እኔ ብቻ ነኝ “እንትናም” ብሎ እንዲያስብ በር ከፋች ሊሆን ይችላል፡፡ ይሁን ሠዓሊው ፍቅሩ፤እኔ ብቻ ነኝ “እንትናም” ብሎ ያስብ… ግን እሳቸው የሌሎችን ሠዓሊያኖቻችንን እንትን ማየት አልቻሉምና ባለ እንትናም እሱ ብቻ ነው?
የተመልካች አስተያየቶች፡- የብሔራዊ ሙዝየም ታዳሚያን ብዙዎቹ ትርዒቱን ዘልፈውታል፣ ሰድበውታል፣ አነፃፅረውም ዋጋ ቢስ አድርገውታል፡፡ ሥዕል መመልከት፣ ልምምድ ዕውቀት ቢጠይቅም ከሚታየው ሥራ ጋር ስሜታዊና ሃሳባዊ ቁርኝት ይፈልጋል፡፡ የዕይታ ባህሉ ያልዳበረ የማህበረሰብ ክፍል ትርዒቱን ሲመለከት ምንም ስሜት ባይሰጠው፣ ሃሳብ ባይገለጥለትና የሆነ ዘባተሎ ነገር ቢሆንበት ሊገረም ወይም በሰዓሊው ሊናደድ አይገባም፡፡
ጎበዝ የሆነ ተመልካች ራሱን ይጠይቃል-፤ካልሆነም እርዳታ ይጠይቃል- ይህም ካልተሳካ አይተወውም? ምን አስጨነቀው? በእርግጥ አጥብቆ ጠያቂ፣ የእናቱን ሞት ሊረዳ ቢችልም መዳኗንም ሊበሰር ይችላል፡፡

   በዶ/ር ዓለማየሁ አረዳ የተፃፈውና “የሰጐን ፖለቲካ - የኢትዮጵያ ምሁራን ሚና” የተሰኘ መፅሃፍ ሰሞኑን ለገበያ ቀረበ፡፡ “ምሁር ሲባል ምን ማለት ነው? ሚናውስ ምንድን ነው? አፈጣጠሩስ ምን ይመስላል? የኢትዮጵያን ምሁራን ሚና በሌሎች ምሁራን ሚና ተመን ማየት ይቻላል ወይ?” በሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ የሚያጠነጥነው መፅሃፉ፤ ብሄርተኝነትና የኢትዮጵያ የዲሞክራሲ ግንባታ ፈተናዎችንም ይዳስሳል፡፡ በሰባት ምዕራፎች የተከፋፈለውና 154 ገፆች ያሉት መፅሃፉ፤ በ45 ብር ለገበያ ቀርቧል፡

Saturday, 02 July 2016 12:30

የፀሐፍት ጥግ

(ስለ ሥነ ፅሁፍ)

ግጥም የሥነ - ፅሁፍ ዘውድ ነው
ደብሊው. ሶመርሴት ሙዋም
ሥነ - ፅሁፍ መልሱ የተቀነሰለት ጥያቄ ነው፡፡
ሮላንድ ባርቴስ
ሥነ - ፅሁፍ እጅጉን አባባይ፣ እጅጉን አታላይ፣
እጅጉን አደገኛ ሙያ ነው፡፡
ጆን ሞርሌይ
መፅሃፍ ቅዱስ ሥነ-ፅሁፍ እንጂ ቀኖና አይደለም፡፡
ጆርጅ ሳንታያና
የሥነ-ፅሁፍ ኃይል ከጨቋኝ ኃይል የጠነከረ ነው
ብዬ አምናለሁ፡፡
ማ ጅያን
ሥነ-ፅሁፍ የአንድ ህዝብ ህያው ትዝታ ሆኗል፡፡
አሌክላንዶር ሶልዝሄኒትሲን
የእያንዳንዱ ሰው ትዝታ የየራሱ የግል ሥነ ፅሁፍ
ነው፡፡
አልዶውስ ሂክስሌይ
ታላላቅ የሥነ - ፅሁፍ ስራዎች በሙሉ አንድም
የሆነ ዘውግን ያጠፋሉ አሊያም ሌላ ዘውግ
ይፈጥራሉ፡፡
ቻርለስ ጄ. ሺልድስ
የሥነ-ፅሁፍ ዓላማ ማስተማር፣ ማነቃቃት ወይም
ማዝናናት ነው፡፡
ጆርጅ ሔነሪ ልዊስ
የሁሉም ሥነ-ፅሁፍ መሰረቱ ግለሰባዊ የህይወት
ተመክሮ ነው፡፡
ጆርጅ ሔነሪ ልዊስ
ማንኛውም የረዥም ልብ ወለድ ፀሐፊ፤ የሥነ-
ፅሁፍ ጉዳይ ሊያሳስበው ይገባል ብዬ አላስብም፡፡
ጃኩሊን ሱሳን
ፀሐፊ የሚያጠናው ሥነፅሁፍን እንጂ ዓለምን
አይደለም፡፡
አኒ ዲላርድ
እኔ ሥነ-ፅሁፋዊ እንስሳ ነኝ፡፡ ለእኔ ሁሉ ነገር
የሚቋጨው በሥነ-ፅሁፍ ነው፡፡
ካርሎስ ፉንቴስ
ለእኔ ሥነ-ፅሁፍ፣ እኔን ስለማይመስሉ ሰዎች
በማወቅ፣ ራሴን የማሳደጊያ መንገድ ነው፡፡
አኔ ፋዲማን
በእኔ ሥነ ፅሁፍ ውስጥ ዕድል የሚጫወተው ሚና
አለ ብዬ አላምንም፡፡
ኢታሊ ካልቪኖ
ያለ ሥነ ፅሁፍ ህይወቴ አሰቃቂ ነው፡፡
ናጀብ ማህፉዝ




ፈጠራውን ያገኘሁት ከ24 አመታት በፊት ነው ብሏል
     ቶማስ ኤስ ሮዝ የተባለው አሜሪካዊ አይፎን እ.ኤ.አ በ1992 ያገኘሁት የግሌ የፈጠራ ውጤት ነው፣ አፕል ኩባንያ የፈጠራ ውጤቴን ዘርፎኛልና 10 ቢሊዮን ዶላር ካሳ  ሊሰጠኝ ይገባል ሲል በኩባንያው ላይ ክስ መመስረቱን ዘ ቴሌግራፍ ዘገበ፡፡
አሜሪካዊው እ.ኤ.አ በ1992 ኤሌክትሮኒክ ሪዲንግ ዲቫይስ ለተባለ ባለ አራት ማዕዘንና ስክሪን ያለው በእጅ የሚያዝ የፈጠራ ውጤቱ የባለቤትነት ማረጋገጫ እንዲሰጠው ለሚመለከተው አካል አመልክቶ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤አፕል ኩባንያ ከዚህ የፈጠራ ውጤቴ የወሰዳቸውን ቴክኖሎጂዎች በመጠቀም አይፎን፣ አይፓድና ሌሎች የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎችን አምርቷል በሚል ክስ መመስረቱን ጠቁሟል፡፡
ግለሰቡ የእሱን ፈጠራና የአይፎንን ተመሳሳይነት ያረጋግጣሉ ያላቸውን የፈጠራ ውጤት ንድፎች ከክሱ ጋር አያይዞ ያቀረበ ቢሆንም፣ በወቅቱ ያቀረበውን የፈጠራ ባለቤትነት ማረጋገጫ ማመልከቻ ተከታትሎ ዳር ሳያደርሰው በመቅረቱ የባለቤት እውቅና ሳይሰጠው መቅረቱን በመጥቀስ፣በአፕል ላይ የመሰረተውን ክስ በአሸናፊነት ላይወጣው ይችላል መባሉን አስረድቷል፡፡ቶማስ ኤስ ሮዝ አቤቱታውን ለፍሎሪዳ ደቡባዊ አውራጃ ፍርድ ቤት ማቅረቡን የጠቆመው ዘገባው፤ ይሄም ሆኖ ግን አፕል በግለሰቡ የቀረበበትን የፈጠራ መብት ዝርፊያና የተመሰረተበትን ክስ በተመለከተ የሰጠው ምላሽ አለመኖሩን ገልጧል፡፡

ጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት፣ ግብር ተቀንሶላቸዋል ከኪራይ ገቢ ውስጥ፣ ግማሹ ከግብር ነፃ ይሆናል ተብሏል የተቀጣሪ ሰራተኞች የግብር ማሻሻያም ለፓርላማ ቀርቧል

    የስድስት መቶ ብር ደሞዝተኛ፣ ከ40 ብር በላይ ነበር ግብር የሚከፍለው፡፡ በአዲሱ ማሻሻያ አዋጅ፣ የግብር ክፍያው ይቀርለታል፡፡
 የጡረታ መዋጮ ከተቀነሰ በኋላ አንድ ሺ ብር የሚያገኝ ደሞዝተኛ ደግሞ፤ 62 ብር የግብር ቅናሽ ያገኛል፡፡
በተመሳሳይ ስሌት የሶስት ሺ ብር ደሞዝተኛ 208 ብር የግብር ቅናሽ ይኖረዋል፡፡ (ሰንጠረዥ ይመልከቱ)
የቤት ኪራይ ገቢ ላይ የተደረገው ለውጥ ሁለት አይነት ነው፡፡ በ1750 ብር ቤት ያከራየ ሰው፣ በድሮው አሰራር፣ ሃያ በመቶ የጥገና ወጪ ታስቦለት 1400 ብር ገቢ እንዳገኘ ነበር የሚቆጠረው፡፡ ከዚያ ልክ እንደ ወር ደሞዝተኛ ግብር ይከፍላል 160 ብር ገደማ፡፡ አዲስ በተሻሻለው አዋጅ ግን፣ ከ1750 ኪራዩ ውስጥ ሀምሳ በመቶው ወይም ግማሹ ለጥገና እንደሚያወጣ ይታሰብበታል፡፡ እናም 875 ብር ገቢ እንዳገኘ ደሞዝተኛ ይቆጠራል፡፡ ከዚህም ውስጥ 28 ብር ግብር ይከፍላል፡፡ ለምን ቢባል፣ ቤት አከራይ እንደ ደሞዝተኛ፣ በአዲስ የግብር ማስከፈያ ስሌት ቅናሽ ተደርጎለታል፡፡ ትልቁ ለውጥ ግን ሌላ ነው፡፡ ከኪራዩ ገቢ ውስጥ፣ ግማሽ ያህሉ ከግብር ነፃ እንዲሆን ተደርጓል - የጥገና ወጪ ስለሆነ፡፡ ይህም፣ አከራዮች ከሚከፍሉት ግብር፣ ሲሶ ያህል ይቀንስላቸዋል፡፡ ነገር ግን ይሄ ቅናሽ የሚሰራው ለግለሰብ አከራዮች ብቻ ነው፡፡
ህንፃ ገንብተው የሚያከራዩ ድርጅቶች፣ እያንዳንዱን የጥገና ወጪ በሂሳብ መዝገብ ማወራረድ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ከኪራይ ገቢያቸው ላይ የጥገና ወጪ ከተቀነሰ በኋላ፣ 30 በመቶ ግብር ይከፍላሉ ይላል አዲሱ አዋጅ፡፡
ለግለሰብ የቤት አከራይና ለግለሰብ ነጋዴዎች ከደሞዝተኛ ጋር የሚመሳሰል ቅናሽ የተደረገ ቢሆንም፤ ለንግድ ድርጅቶች ግን የግብር ለውጥ አልተደረገም - እንደ ቀድሞው 30% ነው፡፡
ጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማትስ? እንደ ንግድ ድርጅት ግብር መክፈል ይጠበቅባቸው የነበሩ ጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት በአዲሱ አዋጅ እንደ ግለሰብ ነጋዴ ወይም እንደ ደሞዝተኛ ይቆጠራሉ ተብሏል፡፡ “ጥቃቅኖች” ትርፋቸው ትልቅም ይሁን ትንሽ፤ 30% ግብር እንዲከፍሉ ማድረግ ተገቢ እንዳልሆነ የህጉ ማብራሪያ ይገልፃል፡፡
እናም የወር ትርፋቸው እንደ ደሞዝ ተቆሮ፣ በደሞዝተኛ ስሌት ግብር ይከፍላሉ ተብሏል፡፡
 በቀድሞው ስሌት በወር አምስት ሺ ብር ያተረፈ ተቋም፤ 1500 ብር ግብር መክፈል ይጠበቅበት ነበር፡፡ በአዲሱ ስሌት 750 ብር ገደማ ግብር ይከፍላል፡፡
በእርግጥ፣ ለግለሰብ ቤት አከራዮች እና ለ“ጥቃቅን” ተቋማት፣ የግብር ቅናሽ ተደርጓል ቢባልም፤ በተጨባጭ የዚያን ያህል ለውጥ ያመጣል ማለት አይደለም፡፡  ብዙዎቹ ጥቃቅን ተቋማት ግብር የመክፈል አቅም የላቸውም፤ ወይም አይከፍሉም፡፡ በዚህም ምክንያት ግብር ተቀነሰላችሁ ቢባሉ፣ ብዙም ትርጉም ላይሰጣቸው ይችላል፡፡







የአንድ ብስክሌት ዋጋ - 35 ሺ ብር!
    የአዲስ አበባ ነዋሪዎች፣ በታክሲ እጥረት መንገላታታቸውና መማረራቸውን እንርሳው - ሁሉንም ችለውና ተሸክመው ኑሯቸውን ይገፋሉ እንበል፡፡ ግን፣ ከአገሪቱ ኢኮኖሚ ውስጥ ሩብ ያህሉን የምታመነጭ ከተማ፣ በትራንስፖርት እጥረት ስትጨናነቅ ጉዳቱ ቀላል ይሆናል?
የከተማዋ ትራንስፖርት ባለስልጣናት፣ “ነዋሪዎችን ከታክሲ ተፅእኖ ነፃ ለማውጣት ነው አላማችን” ብለው ሲናገሩ፤ ምን ለማለት ፈልገው እንደሆነ ግራ ያገባል፡፡ ከትራንስፖርት እጥረት ነጻ የማውጣት አላማ ሳይሆን “ከታክሲ ነፃ የማውጣት” አላማ መያዝ ምን ማለት ነው?
ጉዳዩ፣ ቀልድና ጨዋታ እንዳልሆነ በቅጡ ባይገባቸው ይሆናል፡፡ ነዋሪዎች በተለያዩ እውነተኛ የኑሮ ችግሮች በቤት እጦት፣ በትራንስፖርት እጥረት፣ በኑሮ ፈተናዎች ተወጥረዋል፡፡ ባለስልጣናት ደግሞ በመግለጫና በፕሮፓጋንዳ፣ ሁሉንም ችግሮች ብን አድርገው ማጥፋት የሚችሉ ይመስላቸዋል፡፡ የምናብ ዓለም ይፈጥራሉ፡፡ ህገ ወጥ ቤቶችን የማፍረስ ዘመቻዎች ላይ እየተፈጠሩ ያሉ ችግሮችን ተመልከቱ፡፡ በአንድ ክፍለ ከተማ ብቻ 20 ሺህ ቤቶችን ለማፍረስ ነው የታቀደው፡፡ በሌሎች ክፍለ ከተማዎችም እንዲሁ፡፡
ቤቶችን ማፍረስ ከመቶ በላይ ሰዎችን እንደሚያፈናቅልና ህይወታቸውን እንደሚያናጋ ለመገንዘብ ይከብዳል? አብዛኞቹ ከአካባቢው ገበሬ ትንንሽ መሬት በመግዛት፣ የአቅማቸውን ያህል አንድ ሁለት ክፍል የጭቃ ቤት የሰሩ ነዋሪዎች ናቸው፡፡
የመንግሥት ባለስልጣናት ግን፣ በደፈናው የመሬት ወረራ በማለት ነገሩን ያጋንኑታል፡፡ መሃል ከተማ ውስጥ ቤት ተከራይተው ለመኖር እንኳ አቅም የሌላቸው ናቸው - ብዙዎቹ፡፡ ለዚህም ነው ከከተማ ዳር ላይ ለመኖር የሚሞክሩት፡፡ እነዚህ ነዋሪዎች፣ በማናለብኝነት፣ በየቦታው ሰፋፊ መሬት እየያዙ አራት አምስት ቦታ፣ የተንጣለለ ቪላና ፎቅ የሚሰሩ እብሪተኞች እንደሆኑ አድርጐ ፕሮፓጋንዳ መንዛት፤… እውነተኛ ያልሆነ ምናባዊ አቋም ለመፍጠር ይጠቅም ይሆናል፡፡ “መንግሥት ደና አደረገ፤ የማፍረስ ዘመቻው መቀጠል አለበት” የሚል ድጋፍ ለማግኘትም ይረዳ ይሆናል፡፡ ነገር ግን፤ በፕሮፓጋንዳ በተፈጠረ ”ምናባዊ አለም” እውነተኛው የነዋሪዎች ችግር ብን ብሎ አይጠፋም፡፡
“ህገ ወጥ ቤቶች” መነካት የለባቸው እያልኩ አይደለም፡፡ ውለው አድረው ችግር ያስከትላሉ፡፡ ነገር ግን፣ እንደዘበት በመቻ ማፍረስ፣ የመቶ ሺ ነዋሪዎችን ኑሮ እንደዘበት ማናጋት ማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ፣ ለነውጠኞችና ለዱርዬዎች እድል ይከፍታል፡፡ የድብድብና የግድያ ሰበብ ይሆንላቸዋል፡፡ የአብዛኛው ሰው ፍላጐት ግን ይሄ አይደለም፡፡ ብጥብጥ፣ ችግርን ያባብሳል እንጂ መፍትሄ አይሆንም፡፡ ጥያቄ ምንድነው? ቤታቸው ፈረሰ፤ ከዚያስ የት ይጠለሉ? የት ይሂዱ? የት ይኑሩ? አብዛኞቹ አማራጭ የላቸውም፡፡ ይህንን እውነተኛ ችግር ለመገንዘብ አለመፈለግ፣ ነገሩን እንደ ቀልድና እንደ ጨዋታ ከመቁጠር አይለይም፡፡ መዘዙም ብዙ ነው፡፡ ራስን በራስ ጠልፎ ለመጣል እንደመሞከር ነው፡፡ ይልቅ፣ በአስተዋይነትና በጥንቃቄ የብዙ ሰዎችን ኑሮ በማያናጋና አማራጭ በማያሳጣ መንገድ መፍትሄ ለማበጀት መትጋት ይሻላል፡፡ የትራንስፖርት እጥረት ላይም ነገሩ እንደ ቀላል ጉዳይ በማየት “ከታክሲ ነፃ ማውጣት” የሚል ቀልድና ጨዋታ ላይ ጊዜ ማጥፋት አያዋጣም፡፡ ይህም ብቻ አይደለም፤ የአየር ብክለትን ለመከላከል የካርቦን ልቀትን ለመቀነስ፣ ታክሲዎችን ማዳከም… የሚባል ጨዋታ አለ፡፡
ወደ ቀልድ!
የአውሮፓ ፖለቲከኞችና ወገኞች “የአየር ብክለት፣ የካርቦን ልቀት” .. እያሉ ይቀናጡ፡፡ እዚህ አዲስ አበባ ሰዎች በኑሮ፣ በትራንስፖርት፣ በቤት ችግር መከራ በሚያዩበት ከተማ ግን፣ እንዲህ አይነት … የመቀናጣት ወገኛ ሙከራ … መጨረሻው አያምርም፡፡ የኑሮ ችግር ተጠራቅሞ ተደራርቦ መቼ እንደሚያፈተልክና እንደሚፈነዳኮ አይታወቅም፡፡ ስለዚህ፣ ከጥፋት በስተቀር ሌላ ትርጉም የሌለውን ወገኛነት በመተው፣ ኢኮኖሚና ተጨባጭ የኑሮ ችግሮች ላይ ማተኮር ይበጃል፡፡
የትራንስፖርት እጥረትን ለመፍታት ከመትጋት ይልቅ፤ የካርቦን ልቀትን የሚቀንሱ ብስክሌቶችን በታክሲ ምትክ እናከፋፍላለን በሚል ወገኛነት መቀናጣት፤ … 300 ብስክሌት ለመግዛት፣ ለብስክሌት ልዩ መንገድ ለመከለል … 21 ሚሊዮን ብር ማባከን … የራስን መቃብር የመቆፈር ሙከራ ከመሆን ያለፈ ትርጉም አይኖረውም፡፡ በርካታ ደርዘን አገራት በቀውስና በነውጥ ውስጥ ተዘፍቀው፣ መውጣት እንዳቃታቸው እያየን … አንዴ ከተንሸራተቱ በኋላ ማጠፊያው እንደሚያጥር እያየን … በራሳችን እጅ ቀውስ እንጠራለን እንዴ?

ከእለታት አንድ ቀን አንድ ገበሬ ላሟን ሊመግብ ወደ በረት ይገባል፡፡ ላሚቱ የምትበላውን ወደ ገንዳዋ እየጨመረ ሳለ በእግሯ የምግቡን እቃ መታችው፡፡ ምግቡ በሙሉ በአካባቢው ተበተነ፡፡
ገበሬው ተናደደና፤
“አንድ ብያለሁ!” አለ፡፡
በሚቀጥለው ቀን ላሚቱን ለማገድ ከበረቷ ያስወጣታል፡፡ ከግቢው እየወጣች ሳለች፣ ገበሬው ሁለት ሳምንት ሙሉ ሲያጥርና ሲጠግን የከረመውን አጥር በቀንዷ ስትመታው ፈረሰና ግማሹ መሬት ላይ ወደቀ፡፡
ገበሬው ብስጭት ብሎ፤
“ሁለት ብያለሁ!” አለ፡፡
በሚቀጥለው ቀን ጠዋት ገበሬው ላሚቱን ለማለብ ጮጮውን ይዞ ወደ እግሯ ቀረብ ብሎ፤ ወደ ጡቶቿ እጁን ሲሰድና ጥቂት ወተት እንዳለበ አሁንም በእግሯ ጮጮውን መታችው፡፡ ወተቱ በአካባቢው ላይ ተረጨ፡፡
ገበሬው ትእግስቱ አለቀና፤
“ይሄ ሶስተኛሽ ነው! አለቀ በቃ!” አለና መሣሪያውን አምጥቶ ግንባሯን ብሎ ገደላት!
ሚስቱ ተኩስ ሰምታ ተኩሱን ወደሰማችበት እየሮጠች መጣች፡፡ ስታይ ላሚቱ ወድቃለች፡፡ ገበሬው እጁ ላይ ገና አዲስ የተተኮሰ ሽጉጥ በአፈ-ሙዙ ጭስ ይተፋል፡፡
ሚስቲቱ በጣም ተበሳጭታ፣
“አሁን ምን ልሁን ብለህ ነው ይቺን ምስኪን እንስሳ በሽጉጥ የምትገላት?” ብላ አምባረቀችበት፡፡
ገበሬውም፤
“አንቺንም አንድ ብያለሁ!” አላት፡፡
***
የማስጠንቀቂያ ደወል አለማዳመጥ አንድም የጆሮ፣ አንድም የልቡና ችግር ሊሆን ይችላል፡፡ የጆሮ ችግር ከሕክምና ያለፈ መፍትሄን አይሻም፡፡ የልቡና ችግር ግን የተለያዩ ግብአቶች ውጤት ነው፡፡ እንዲህ በዋዛ አይፈታም፡፡ ብዙ ናቸው የመፍትሄው አንጓዎች፡፡ የችግሮቹ አንጓዎችም እንደዚያው ሀ/ ልቡና ሊለግም ይችላል፡፡ ለ/ ልቡና አውቆ በድፍረት እምቢ ሊል፣ ሊያምፅ ይችላል፡፡ ሐ/ ልቡና ለአቅመ-መቀበል ያልደረሰ፣ ያልበሰለ ሊሆን ይችላል፡፡ መ/ ልቡና በተአብዮ የተሞላ ሊሆን ይችላል፡፡ በነዚህና በሌሎች ምክንያቶች ልቡና ጥያቄዎችን ላያዳምጥ ይችላል፡፡ አብሮ ግን የማስጠንቀቂያውን ደወል የደወለው ማነው? መስማት የሚጠበቅበትስ ማነው? ደወሉ ወቅታዊ ነው አይደለም? ወይንስ “የጠርሙሱ ውታፍ እንደተነቀለለት ጅኒ” ድንገት የመጣ የማስጠንቀቂያ ደወል ነው? ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡
በንጉሱ ዘመን ለወሎ ረሃብ የማስጠንቀቂያ ደወል ንጉሡ ዕዝነ-ልቦናቸውን ነፈጉ፡፡ ለወታደሩ ጥያቄዎችም እንደዚሁ ዕዝነ-ልቦናቸውን ነፈጉ፡ ለተማሪዎችም ጥያቄዎች ዕዝነ-ልቦናቸውን አልቸሩም… ዋለ አደረና የሆነው ሆነ! በኃይል ለመፍታት ሞከሩ፤በኃይል ወደቁ፡፡
በጃንሆይ እግር የገባው ወታደራዊ መንግሥትም ለዲሞክራሲ ጥያቄዎች፣ ለሰብዓዊ መብት ጥያቄዎች ልቡናውን አልከፍትም አለ፡፡ ለእኩልነት ጥያቄዎችና ለህዝባዊ ሥልጣን ጥያቄዎች ዕዝነ-ልቦናዬን አልሰጥም ሞቼ እገኛለሁ አለ፡፡ ንቀትን፣ ትምክህትን፣ ተዓብዮን “የፍየል ወጠጤን” ምላሹ አደረገ፡፡ በኃይል ኖረ በኃይል ወደቀ፡፡ ከእነዚህ ሁለት መንግሥታት ሁለት ተመሳሳይ ልምድ መማር ያለብንና ተገቢ ትኩረት መስጠት ያለብን፤ ኃይል ጊዜያዊ መፍትሄ እንጂ ዘላቂ እንደማይሆን ነው፡፡ ላልተመለሱ ጥያቄዎች ዕዝነ-ልቦናን መክፈት ቢያንስ ከተለመደ የአወዳደቅ ባህል ይገላግለናል፡፡ ለዘመናት የቆዩ የተሸራረፉ ምላሾችን የማይፈልጉ፣ ሳይፈቱ ከቀጠሉ እንደገና ሌላ ችግር የሚፈለፍሉ፣ መሰረታዊ ጥያቄዎች አያሌ ናቸው፡፡ ሊዘለሉ ደግሞ ከቶ አይችሉም፡፡ የዲሞክራሲ፣ የፍትህ፣ የእኩልነት፣ የነፃነት፣ የኑሮ መሻሻል፣ የመንግሥት አስተዳደር፣ የአገር ሉአላዊነት ቱባ ቱባ ጥያቄዎች ሁሌም እንዳፈጠጡብን አሉ፡፡ ዞሮ ዞሮ የሊበርቲ፣ኢኳሊቲ፣ፍራተርኒቴ ልጆች ናቸው፡፡ (Liberty,equality,fraternity እንዲል መጽሐፈ ፈረንሳይ) በሽርፍርፍና በገደምዳሜ መንገድ ይነካኩ እንጂ በማያሻማ መንገድ በነቢብ - ወገቢር (Both in theory and practice)፤ ግዘፍ ነስተው አልታዩም፡፡ ህይወት አላገኙም፡፡ ነብስ አልዘሩም፡፡
“ለታላቁ ዓላማ፣ ለሰው መልካም እድል
ህይወቴ ትሞላ፣ ትሁን የትግል ድል” ---- ያለውን ማርክስን ሁሌም የሚያስታውሱ ልባም ሰዎችን አለመዘንጋት ነው፡፡ “ዕዝነ ልቡናህን ልቡና ላላቸው ክፈት” ይላል አንድ ፀሐፊ፡፡ ቢያንስ አዳምጠን ስለ መፀፀት ማሰላሰል እንችላለን፡፡ በእርግጥ ብሶቶችንና እሮሮዎችን ብናዳምጥ፣ አዳምጠንም መፍትሄ ለመስጠት ቆም ብለን ማውጠንጠን ብንችል ምን ይጐዳናል? ለማለት ያህል ለጉዳዮች ጊዜ እንስጥ፡፡ “ሁሌ እኛ ነን ልክ፣ ሌሎች ልክ አይደሉም” የሚለው ንድፈ-ሃሳብ የሚመነጨውና የሚገዝፈው የሌሎችን ጥያቄ አንድም ከመናቅና ከናካቴው ካለመስማት፣ አንድም ከማኮሰስና አድቆ ከማየት፣ አንድም ደግሞ “ይሄማ የእነ እገሌ ነው፣ ለነእገሌ መልስ አንሰጥም” ከማለት ነው፡፡  ጥያቄዎቹ ግን አድረው ብቅ ይላሉ፡፡ እንዲያውም ዘርፍ አበጅተው፡፡ መዝገብን ወደ ኋላ አገላብጦ ከወጪ ቀሪ ምን አለብኝ ማለት፣ ከዕዳ ነፃ ማድረጉን ማሰብ እጅግ ብልህነት ነው፡፡ (አራት አመት ታስሮ በነፃ የተለቀቀ አንድ ሰው፤ “መንግሥት የእኔ አራት አመት እዳ አለበት፡፡” አለ ይባላል፡፡) ዜጐች በደል ሲበዛባቸው፣ ኑሮ ሲከብዳቸው፣ አገልግሎታቸው ዋጋ ሲያጣ፣ ባለስልጣናቱን፣ ሹማምንቱን ማማረራቸው አይቀርም፡፡ “አቀማመጥ አበላሽተው ከአሳላፊ ይጣላሉ” እንደሚባለው መሆኑ ነው፡፡ “ሌባ ሌባ” እያለች ታስራ ስትጮህ ተኝተው ለሌባው እድል የሰጡ የተሰረቁ ባለቤቶች፣ ጠዋት ውሻዋን እየደበደቡ፤“ይቺ ውሻ ናት ያሰረቀችን” ሲሉ፤ “ጮኸን ጮኸን እንዳልጮህን ሆንን” አለች አሉ ውሻ፡፡ ይሄም ያስኬደናል፡፡ ውሻ እንደ አሳላፊው መሆኗ ነዋ!!


እንግሊዝ በአውሮፓ ህብረት አባልነቷ ትቀጥል ወይስ አትቀጥል የሚለው አወዛጋቢ ጉዳይ፣ከትናንት በስቲያ በተካሄደው ህዝበ ውሳኔ እልባት አግኝቷል - እንግሊዝ ከህብረቱ አባልነቷ ወጥታለች፡፡ የእንግሊዝ የአውሮፓ ህብረት አባልነት ቀጣይ ዕጣ ፋንታ ጉዳይ፣ የአገሪቱን ብቻ ሳይሆን የሌሎች የዓለማችን አገራትን ታዋቂ ፖለቲከኞች ጭምር ለሁለት ከፍሎ ሲያሟግት ነበር የከረመው፡፡ ጉዳዩ የፖለቲከኞች ብቻም አልነበረም፡፡ በተለያዩ የሙያ መስኮች አለማቀፍ እውቅናን ያተረፉ እንግሊዛውያንና የሌሎች አገራት ዝነኞችም፣የህዝበ ውሳኔው ውጤት እስኪታወቅ ድረስ ትቆይ እና ትውጣ የሚል አቋማቸውን በየአጋጣሚው ሲገልጹ ነበር የሰነበቱት፡፡
ከህብረቱ ጋር ትቀጥል ባዮች
ቢቢሲ እንደዘገበው፤ከ250 በላይ ታዋቂ የአገሪቱ ድምጻውያን፣ የፊልም ተዋንያን፣ ደራሲያንና ሰዓሊያን እንግሊዝ በአውሮፓ ህብረት አባልነቷ ትቀጥል የሚለውን አማራጭ በመደገፍ፣ ፊርማቸውን ከማሰባሰብ አልፈው፣ እንግሊዛውያን ከጎናቸው እንዲቆሙ በተለያዩ ማህበራዊ ድረገጾች ጥሪያቸውን አቅርበው ነበር፡፡ አልተሳካላቸውም እንጂ፡፡  
የጄምስ ቦንዱን ዳኔል ክሬግ ጨምሮ፣ዴቪድ ሞርሲ እና ጁሊየት ስቴቨንሰንም የዚህ አቋም ደጋፊዎች የነበሩ የእንግሊዝ ዝነኛ የፊልም አክተሮች ናቸው፡፡ ዝነኛው ድምጻዊ ኤልተን ጆንም እንግሊዝ በህብረቱ አባልነቷ እንድትቀጥል ነበር ፍላጎቱ፡፡  
እንግሊዝ በአውሮፓ ህብረት አባልነቷ ትቀጥል የሚል አቋማቸውን በይፋ ከገለጹና በህዝበ ውሳኔው ላይ ድምጻቸውን ከሰጡ እንግሊዛውያን ዝነኞች መካከል ታዋቂዋ የሃሪ ፖተር ደራሲ ጄ ኬ ሮውሊንግ ተጠቃሽ ናት፡፡ እንደ እሷ ሁሉ የአገሩን በህብረቱ አባልነቷ መቀጠል የደገፈው ሌላው እንግሊዛዊ ደግሞ ታዋቂው እግር ኳስ ተጫዋች ዴቪድ ቤካም ነበር፡፡ ሞዴልና ድምጻዊት ሚስቱ ቪክቶሪያም፣ የባሏን ሃሳብ ደጋፊ ነበረች፡፡
የአርሴናሉ አሰልጣኝ አርሰን ቬንገር፣ ታዋቂው እንግሊዛዊ ድምጻዊና በጎ አድራጊ ሰር ቦብ ጌልዶፍና የኤክስ ፋክተር ውድድር ዳኛው ሲሞን ኮዌልም፤ ከህብረቱ ጋር ብንቀጥል መልካም ነው ባዮች ነበሩ፡፡
ከህብረቱ ትነጠል ባዮች
ከህዝበ ውሳኔው ውጤት አስቀድሞ ለሃገሬ የሚበጃት ከአውሮፓ ህብረት አባልነቷ ብትወጣ ነው የሚል አቋም የያዙ ዝነኞችም በርካታ ነበሩ፡፡ ታዋቂው እንግሊዛዊ የፊልም ተዋናይ ሰር ማይክል ኬን ተጠቃሽ ነው፡፡
የቀድሞው የእንግሊዝ ብሄራዊ የእግር ኳስ ቡድን ተሰላፊ ሶል ካምቤል እና ሌላው የሙያ አጋሩ የቀድሞው የብሄራዊ ቡድኑ ግብ ጠባቂ ዴቪድ ጄምስም፤ተመሳሳይ አቋም ከነበራቸው መካከል ይጠቀሳሉ፡፡ እንግሊዝ ከአውሮፓ ህብረት አባልነቷ ብትወጣ ይበጃታል ብሎ የነበረው ሌላው ዝነኛ ደግሞ ጁሊያን አሳንጄ ነው፡፡ ይኸው እንግሊዝ ከህብረቱ አባልነቷ ወጥታለች፡፡