Saturday, 02 February 2019 15:37

ሳምሰንግ በአለማቀፉ የስማርት ፎን ገበያ ክብሩን አስጠብቋል

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

 አፕል በአይፎን ዋጋ ላይ ቅናሽ ሊያደርግ እንደሚችል ተነግሯል


     ላለፉት ተከታታይ አመታት በአለማቀፉ የስማርት ፎን ገበያ ከፍተኛውን ድርሻ ይዞ የዘለቀው የደቡብ ኮርያው ሳምሰንግ፤ ያለፈውን የፈረንጆች አመት 2018 በቀዳሚነት ማጠናቀቁን ካናሊስ የተባለው የስማርት ፎን ገበያ የጥናት ተቋም አስታውቋል፡፡
ካናሊስ ከሰሞኑ ይፋ ባደረገው ሪፖርት እንዳለው፤ በ2018 የፈረንጆች አመት አለማቀፍ የስማርት ፎን ገበያ ውስጥ የ21.2 በመቶ ድርሻ የያዘው ሳምሰንግ በአመቱ 293.7 ሚሊዮን የተለያዩ ሞዴል ያላቸው የሞባይል ስልኮቹን ለመሸጥ ችሏል፡፡
ተፎካካሪው አፕል ኩባንያ በበኩሉ፤ በአመቱ 212.1 ሚሊዮን የአይፎን ስልክ ምርቶቹን በመሸጥና በአለማቀፉ የስማርት ፎን ገበያ ውስጥ የ15.3 በመቶ ድርሻን በመያዝ በሁለተኛ ደረጃ ላይ መቀመጡን ያስታወቀው ተቋሙ፤ በአመቱ 206 ሚሊዮን የሞባይል ምርቶቹን ለመሸጥ የቻለው የቻይናው ሁዋዌለ፤ በ14.8 በመቶ የገበያ ድርሻ በሶስተኛ ደረጃ ላይ እንደሚገኝም አመልክቷል፡፡
ሳምሰንግ በገበያ ድርሻና በሽያጭ ከአፕል ቢበልጥም የሁለቱም ኩባንያዎች ሽያጭና አመታዊ እድገት ግን ከአምናው መቀነሱን  የጠቆመው ሪፖርቱ፣ ሁዋዌ በበኩሉ በሽያጭና በአመታዊ እድገት ከአምናው ከፍተኛ ጭማሪ ማሳየቱን ገልጧል፡፡ በተያያዘ ዜናም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ገቢው በከፍተኛ ሁኔታ እየቀነሰበት የመጣው አፕል ኩባንያ፤ በአንዳንድ አገራት ለገበያ ባቀረባቸው የአይፎን የስማርት ፎን ምርቶቹ ዋጋ ላይ ቅናሽ ሊያደርግ እንደሚችል ፍንጭ መስጠቱን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
አፕል ከአይፎን ሽያጭ የሚያገኘው ገቢ ባለፉት ሶስት ወራት በ15 በመቶ ያህል እንደቀነሰበት ያስታወሰው ዘገባው፣ የኩባንያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ቲም ኩክ ከሰሞኑ ባደረጉት ንግግር፣ በአንዳንድ አገራት የአይፎን መሸጫ ዋጋ ላይ ቅናሽ ሊደረግ እንደሚችል መረጃ መስጠታቸውን ገልጧል፡፡
የአፕል አጠቃላይ ገቢ ባለፈው አመት ከነበረበት የ5 በመቶ ቅናሽ በማሳየት፣ 84.3 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን የጠቆመው ዘገባው፣ ኩባንያው ለገቢው መቀነስ በምክንያትነት ከጠቀሳቸው ጉዳዮች መካከል በቻይና የኢኮኖሚ መቀዛቀዝ መፈጠሩ ይገኝበታል ብሏል፡፡

Read 1519 times