Print this page
Sunday, 18 February 2018 00:00

ከ357 ሚ. በላይ ህጻናት በጦርነትና ግጭት ቀጠናዎች ውስጥ ይኖራሉ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

በጦርነትና የግጭት ቀጠናዎች ውስጥ አደገኛና አስቸጋሪ ህይወት እየገፉ የሚገኙ የአለማችን ህጻናት ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ በማደግ ከ357 ሚሊዮን በላይ መድረሱን ሴቭ ዘ ችልድረን ከትናንት በስቲያ ባወጣው ዓለማቀፍ ሪፖርት ማስታወቁ ተዘግቧል፡፡
በጦርነትና በግጭት ቀጠናዎች ውስጥ ከሚገኙት የአለማችን ህጻናት፣ ግማሽ ያህሉ ወይም 165 ሚሊዮን የሚደርሱት ከፍተኛ ግጭት በሚከሰቱባቸው አካባቢዎች ውስጥ እንደሚኖሩ የጠቆመው ሪፖርቱ፤ የመካከለኛው ምስራቅ አገራት ህጻናት ለዚህ ችግር በመጋለጥ ረገድ ቀዳሚነቱን እንደሚይዙና አፍሪካውያን ህጻናት እንደሚከተሉ በመግለጽ፣ በመካከለኛው ምስራቅ አገራት ከሚኖሩ አምስት ህጻናት፣ ሁለቱ ግጭት ወይም ጦርነት በሚከናወንበት አካባቢ በ50 ኪሎ ሜትሮች ርቀት ውስጥ እንደሚኖሩ አመልክቷል፡፡
በርካታ ህጻናት በጦርነትና በግጭት ቀጠናዎች ውስጥ እንደሚገኙባቸውና ለህጻናት እጅግ አደገኛ ናቸው ተብለው በሪፖርቱ ከተጠቀሱት የአለማችን አገራት መካከል ሶሪያ ቀዳሚነቱን ስትይዝ፣ አፍጋኒስታንና ሶማሊያ በተከታታይነት ተቀምጠዋል፡፡
በህጻናት ላይ የሚፈጸሙ ግድያዎችና የማቁሰል ጥቃቶች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተበራከቱ እንደመጡ የዘገበው ዘ ኢንዴፔንደንት፤ የተባበሩት መንግስታት በማስረጃ አስደግፎ የሚመዘግባቸው መሰል ጥቃቶች ቁጥር ባለፉት ሰባት አመታት ውስጥ በ3 እጥፍ ማደጉንም አስታውሷል፡፡
በግጭቶችና በጦርነቶች ሳቢያ ከመኖሪያ አካባቢያቸው እየተፈናቀሉ ለተለያዩ ስቃዮችና እንግልቶች የሚዳረጉ የአለማችን ህጻናት ቁጥር እያሻቀበ እንደሚገኝ የጠቆመው ዘገባው፤ ከ65 ሚሊዮን በላይ የዓለማችን ህጻናት ምንም አይነት ቋሚ የመኖሪያ ቤት እንደሌላቸው አመልክቷል፡፡

Read 3285 times
Administrator

Latest from Administrator