Monday, 27 May 2013 15:14

ዊል ፋሬል “አትራፊ ያልሆነ ተዋናይ” ተባለ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

በኮሜዲ ፊልሞቹ የሚታወቀው ዊል ፋሬል በሰራቸው ፊልሞች አትራፊ ባለመሆን የአንደኝነት ደረጃን እንደያዘ ፎርብስ መፅሄት አስታወቀ፡፡ ኮሜዲያኑ በሚተወንበት አንድ ፊልም ለተከፈለው 1 ዶላር 3 .30 ዶላር ብቻ በማስገባት ዝቅተኛ ትርፍ ያስመዘገበ ተዋናይ ሊሆን በቅቷል፡፡ በብዙ ፊልሞቹ ላይ ‹የትልቅ ህፃን› ገፀባህርይ እየተጫወተ የሚያሳያቸው ትዕይንቶች እና ንግግሮቹ ተደጋጋሚ እየሆኑ መምጣታቸው እና በአጠቃላይ አሰልቺ መሆናቸው ለተዋናዩ ትርፋማነት መቀነስ ምክንያቶች ናቸው፡፡

ፎርብስ አትራፊ ያልሆኑ 7 የሆሊውድ ተዋናዮችን ደረጃ ይፋ ባደረገበት ወቅት፤ ሁሉም ባለሙያዎች በቅርብ ጊዜ ትርፋማ እና ተፈላጊ በመሆን የማገገም ዕድል ላይኖራቸው እንደሚችል አመልክቷል፡፡ በተወኑባቸው ፊልሞች በተከፈላቸው 1 ዶላር ኢዋን ማክሪጎር 3.75፤ ቢሊ ቦብ ቶርቶን 4 ፤ኤዲ መርፊ 4.43፤ አስ ኪውብ 4.77፤ ቶም ክሩዝ 7.20 እንዲሁ ድሪው ባሪሞር 7.4 ዶላር በማስገባት ከዊል ፋሬል ቀጥሎ እስከ 7 ያለውን ትርፋማ ያለመሆን ደረጃ አግኝተዋል፡፡ በሆሊውድ ትርፋማ ከተባሉ ተዋናች አንዱ የሆነው እና በትራንስፎርመር ፊልሞች የሚታወቀው ሻይ ለበፍ በተከፈለው 1 ዶላር 160 ዶላር ያስገባል፡፡ በሙያ ዘመኑ ከ34 በላይ ፊልሞች ላይ የተወነው ዊል ፋሬል፤ በመላው ዓለም ያስገባው 2.034 ቢሊዮን ዶላር ሲሆን በአንድ ፊልም በአማካይ እስከ 81.62 ሚሊዮን ዶላር በማስገኘት የሚታወቅ ነበር፡፡ ከ100 ሚሊዮን ዶላር በላይ ያስገቡ 7 ፊልሞችን የሰራው ኮሜድያኑ፤ የትወና ብቃቱን በአዲስ መልክ ካልቀየረ ከገበያው መውጣቱ አይቀርም እየተባለ ነው፡፡

Read 2244 times